2024-04-13 21:19:28
የዐቢይ ጾም ስድስተኛ ሳምንት ገብርኄር
የዐብይ ጾም ስድስተኛ ሳምንት ገብርኄር ይባላል፡፡
ገብርኄር ማለት ታማኝ አገልጋይ ማለት ነው፡፡ ስለ ታማኝ አገልጋይ አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ ዓለም ስንኖር ለፈጣሪያችን ያለንን ታማኝነትና የምናገኘውን ዋጋ በመዋዕለ ሥጋዌው
አስተምሯል፡፡
ቅዱስ ያሬድ ለዜማ መክፈያነት የዐብይ ጾምን ሳምንታትን ሲከፍል ገብርኄርን ተጠቅሟልና እኛም ስለ ገብር ሄር ጥቂት እንበል፡፡ ልዑል እግዚአብሔር አምላካችን በነቢዩ አንደበት አድሮ፤ “እከሥት በምሳሌ አፉየ፤ ወእነግር አምሳለ ዘእምትካት፤ አንደበቴን /ነገሬን/ በምሳሌ እገልጣለሁ፤ ከቀድሞ ጀምሮ የነበረ
ታሪክና ምሳሌ እናገራለሁ” አለ፡፡
ይህም ማለት ወንጌልን በምሳሌ አስተምራለሁ፤ በመልከ ጼዴቅ ዘመን አስቀድማ የተሠራችና ታይታ የጠፋችውን ወንጌልን እናገራለሁ፡፡ ይህን ታላቅ ምሥጢር ሐዋርያው ሲያብራራ “ከመ በአሚን ያጸድቆሙ እግዚአብሔር ለአሕዛብ አቅደመ አሰፍዎቶ ለአብርሃም ከመ ቦቱ ይትባረኩ ኲሎሙ አሕዛብ ፤ በአንተ አሕዛብ ሁሉ ይባረካሉ ብሎ ወንጌልን ለአብርሃም አስቀድሞ ሰበከ” ብሏል፡፡ /ገላ. ፫፥፰፣ መዝ. ፸፯፥፪
በዚሁ መሠረት ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወንጌለ መንግሥተ ሰማያትን ለልዩ ልዩ ወገኖች በልዩ ልዩ ምሳሌ አስተምሯል፤ ከላይ በተገለጠው ኃይለ ቃል መነሻነት ሁለት ምሳሌያትና አንድ ቃለ ትንቢት ቀርበዋል፡፡ ከምሳሌያቱ
የመጀመሪያው በዐሥሩ ደናግል አንጻር የቀረበው ምሥጢር ሲሆን፤ ሌላኛው ደግሞ ወጥተው ወርደው ነግደው ያተርፉበት ዘንድ ገንዘቡን ስለሰጠ አንድ ነጋዴ የሚናገረው ነው፡፡
የትንቢቱ ምሥጢራዊ ይዘት የሚያስረዳውም ስለ ኅልቀተ ዓለም አይቀሬነት ነው፡፡ ስለሆነም በዚህ ዕትማችን ወጥተው ወርደው ነግደው እንዲያተርፉበት ከጌታቸው የተሰጣቸውን መክሊት ስለተቀበሉት አገልጋዮች ሕይወት እንመለከታለን፡፡ ፈጣሪያችን አእምሮውን ለብዎውን /ማስተዋሉን/ ያድለን፡፡
ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለደቀ መዛሙርቱ ያስተማራቸው ምሳሌያዊ ትምህርቶች በቅዱስ መጽሐፋችን በሰፊው ተጽፈው እናገኛለን፡፡ የእነዚህ ትምህርታዊ ምሳሌዎች መሠረታዊ ሀሳብና ዓላማም የእግዚአብሔርን መንግሥት የምናገኝበትን የታማኝነትን ሥራ እንዴት መሥራት እንደሚገባንና መሥራትም እንደምንችል ማስተማር ነው፡፡
ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለመንግሥተ ሰማያት ምሥጢር ያስተማራቸው ብዙ ምሳሌዎች ያሉ ሲሆን ከእነዚህ ብዙ ምሳሌያዊ ትምህርቶች መካከልም እንዲያተርፉበት መክሊት ስለተሰጣቸውና ስለተመሰገኑት መልካም አገልጋዮች፣ እንዲሁም መክሊቱን በመቅበሩ ምክንያት በጌታው ስለተወቀሰውና ፍርድን ስለተቀበለው ሰነፍ ሰው ታሪክ፣ የታሪኩም ምሥጢር ምን እንደሚመስል የተጻፈው ትምህርት ነው።
ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ይህንን ምሳሌ የተናገረው /ያስተማረው/ በሚከተለው መልኩ ነበር፤ ‹‹ወደ ሌላ ሀገር የሚሔድ ሰው ባሮቹን ጠርቶ ያለውን ገንዘብ እንደሰጣቸው እንዲሁ ይሆናልና ለእያንዳንዱ እንደ ዓቅሙ ለአንዱ አምስት መክሊት ለአንዱ ሁለት ለአንዱም አንድ ሰጠና ወደ ሌላ ሀገር ወዲያውኑ ሔደ፡፡
አምስት መክሊትም የተቀበለው ሔዶ ነገደበት ሌላም አምስት አተረፈ፣ እንዲሁም ሁለት የተቀበለው ሌላ ሁለት አተረፈ፣ አንድ የተቀበለው ግን ሔዶ ምድርን ቆፈረና የጌታውን ገንዘብ ቀበረ፡፡
ከብዙ ዘመንም በኋላ የእነዚያ ባሮች ጌታ መጣና ተቆጣጠራቸው፡፡ አምስት መክሊት የተቀበለውም ቀረበና ሌላ አምስት መክሊት አስረክቦ፡- ጌታ ሆይ አምስት መክሊት ሰጥተኸኝ ነበር፤ እነሆ ሌላ አምስት መክሊት አተረፍሁበት አለ፡፡
ጌታውም፡- መልካም አንተ በጎ ታማኝ ባሪያ በጥቂቱ ታምነሃል በብዙ እሾምሃለሁ፤ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ አለው፡፡
ሁለት መክሊት የተቀበለው ደግሞ ቀርቦ፡- ጌታ ሆይ ሁለት መክሊት ሰጥተኸኝ ነበር፡፡ እነሆ ሌላ ሁለት መክሊት አተረፍሁበት አለ፡፡
ጌታውም፡- መልካም አንተ በጎ ታማኝ ባሪያ በጥቂቱ ታምነሃልና በብዙ እሾምሃለሁ፤ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ አለው።
አንድ መክሊትም የተቀበለው ደግሞ ቀርቦ፡- ጌታ ሆይ ካልዘራህበት የምታጭድ ካልበተንህበትም የምትሰበስብ ጨካኝ ሰው መሆንህን አውቃለሁ፤ ፈራሁም ሔጄም መክሊትህን በምድር ቀበርሁት ፤ እነሆ መክሊትህ አለልህ አለው፡፡
ጌታውም መልሶ እንዲህ አለው፡- አንተ ክፉና ሐሰተኛ ባሪያ ካልዘራሁበት እንዳጭድ ካልበተንሁበትም እንድሰበስብ ታውቃለህን? ስለዚህ ገንዘቤን ለለዋጮች አደራ ልትሰጠው በተገባህ ነበር።
እኔም መጥቼ ያለኝን ከትርፉ ጋር እወስደው ነበር፡፡ ስለዚህ መክሊቱን ውሰዱበት ዐሥር መክሊትም ላለው ስጡት። ላለው ሁሉ ይሰጠዋልና ይበዛለትማል። ከሌለው ግን ያው ያለው እንኳ ይወሰድበታል፡፡
የማይጠቅመውንም ባሪያ በውጭ ወዳለው ጨለማ አውጡት፤ በዚያ ልቅሶና ጥርስ ማፋጨት ይሆናል የሚል ነው፡፡
መክሊት ጥንት የክብደት መለኪያ ነበር:: አንድ መክሊት 30 ኪሎ ግራም ያህል ነው፡፡ በዚህ ምሳሌ ላይ እንደተገለጸውም መክሊት የሚለው ቃል ገንዘብን ያመለክታል፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ ምሳሌ ውስጥ እርሱን የምናገለግል ሁላችን እንደየዓቅማችን ማድረግ የሚገባንን መንፈሳዊ የአገልግሎት ሥራንና በአገልግሎታችን ውጤታማ በመሆናችንም ከእርሱ የምናገኘውን ዘለዓለማዊ ክብርና ዋጋን እንዲሁም መሥራት የሚገባንን ባለማድረጋችንም ምክንያት የሚገጥመንን መለኮታዊ ቅጣትን አመልክቶናል፡፡
በዚህ ምሳሌ ውስጥ ባለ አምስት የተባለው በቂና ፍጹም ትምህርት ተምሮ ሌላውን መክሮ አስተምሮ ራሱን አስመስሎ የተካ ያወጣ ነው፡፡
በተመሳሳይም ባለ ሁለት የተባለው እንደ መጀመሪያው ሁሉ ተምሮ ሌላውን መክሮ አስተምሮ ራሱን አስመስሎ ያወጣ ሲሆን ባለ አንድ የተባለው ደግሞ ተምሮ ሳያስተምር የቀረ በስንፍና በቸልተኝነት በማን አለብኝነት ሕይወት ተገድቦ የቀረ ሰው ነው፡፡
ሙሉውን ለማንበብ ከታች INSTANT VIEW የሚለውን በመጫን ያንብቡ
https://telegra.ph/የየዐቢይ-ጾም-ስድስተኛው-ሳምንት-ገብርኄር-ታማኝ-አገልጋይ-04-13
አቅራቢ ፦ ✞ኦርቶዶክሳዊ መጽሐፍት
የግእዝ ትምህርት በyoutube
https://youtube.com/channel/UCbuXpsXU7hDaFWELjzHlxdg
➮ከወደዱት ያጋሩ
share & join
𝒔𝒖𝒃𝒔𝒄𝒓𝒊𝒃𝒆
@Orthodox_Addis_mezmur
@orthodox_spiritual_poems
@Eotc_Books_By_Pdf
@Lesangeez128
𝒔𝒖𝒃𝒔𝒄𝒓𝒊𝒃𝒆
5.2K viewsዲያቆን አቤኔዘር ሙሉ, 18:19