Get Mystery Box with random crypto!

በዋናው ነገር ላይ ማተኮር! (“ትኩረት” ከተሰኘው የዶ/ር ኢዮብ ማሞ መጽሐፍ የተወሰደ) አንድን | የስብዕና ልህቀት

በዋናው ነገር ላይ ማተኮር!
(“ትኩረት” ከተሰኘው የዶ/ር ኢዮብ ማሞ መጽሐፍ የተወሰደ)

አንድን እጅግ በጥበብ የላቀን ሰው አገኘሁትና ባለችኝ የጋዜጠኝነት ሙያ ተጠቅሜ መጠየቅ የምችለውን ያህል ለመጠየቅ ሞከርኩ፡፡

ጠቢቡ - “ና ጠጋ በል … ጥያቄ ልትጠይቀኝ እንደፈለግህ ታስታውቃለህ” አለኝ፣ የልቤን ፍላጎት ገምቶ፡፡

እኔ - “ጊዜ ካለህ” አልኩት፡፡

ጠቢቡ (ልብን በሚሰርቅ ፈገግታ) - “ለማወቅ ለሚፈልጉ ሰዎች ሁሉ ጊዜ አለኝ” ብሎ መለሰልኝ፡፡

ይህ ጥበበኛ እንዴት ለሰው ሁሉ ጊዜ ሊኖረው ቻለ? እያልኩ ሳወጣና ሳወርድ በፈገግታና በትእግስት ይጠብቀኝ ነበር፡፡

እኔ፡- “ስለ ሰው ፍጥረት ከሚያስገርሙህ ነገሮች መካከል ጥቂቱን ንገረኝ” አልኩት፡፡

ጠቢቡ -

•  “ልጆች ሳሉ መሰልቸታቸውና ትልቅ ለመሆን መሮጣቸው … ካደጉ በኋላ ደግሞ ልጅ መስሎ ለመታየት መሯሯጣቸው ያስገርመኛል …

•  ገንዘብ ለማካበት ጤንነታቸውን ማጣታቸው … ጤናቸውን ለመመለስ ደግሞ እንደገና ያንኑ ገንዘብ ማፍሰሳቸው ያስደንቀኛል …

•  ስለ ነገ በመጨነቅ ዛሬን ለመኖር አለመቻላቸውና ከዛሬም ሆነ ከነገ ሳይሆኑ መንከራተታቸው ያስገርመኛል …

•  ልክ እንደማይሞት ሰው መኖራቸውና ልክ እንዳልኖረ ሰው ተጽእኖ ቢስ ሆነው መሞታቸው ያስገርመኛል፡፡

ይህን ጠቢብ ዝም ብለው ሌሎች ሃሳቦች እንደሚጨምር እየተሰማኝ በማቋረጥ፣ “ሌላ ጥያቄ ልጠይቅህ?” አልኩት፡፡

ጠቢቡ፡-
ደስ በሚያሰኝ ፈገግታ ፈቃደኝነቱን ገለጠልኝ፡፡

እኔ፡- “የሰው ልጅ ሁሉ አባት ብትሆን ለሰው ልጆች እንዲያደርጉ ከምትመክራቸው ነገሮች መካከል ጥቂቶቹን ንገረኝ” አልኩት፡፡ 

ጠቢቡ (ረዥም ጺሙን ዳበስ ዳበስ በማድረግ ካሰበ በኋላ)፡-

•  ማንም ሰው እንዲወዳቸው ማስገደድ እንደማይችሉ፣ ነገር ግን ማድረግ የሚችሉት የሚወደድ ማንነትን ማሳደግ ብቻ እንደሆነ እንዲያወቁ እመክራቸው ነበር፡፡

•  መልካም ማንነትንና የተመሰከረለት ማህበራዊ ሕይወት ለመገንባት አመታት እንደሚፈጅ፣ ለማፍረስ ግን አንድ ደቂቃ እንደሚፈጅ እንዲያውቁ አስተምራቸው ነበር፡፡

•  የሕይወታችቸውን አቅጣጫ የሚወስነው ያላቸው ንብረትና ሃብት ሳይሆን በሕይወታቸው ያስጠጓቸው የወዳጆች አይነት እንደሆነ እንዲገነዘቡ አሳስባቸው ነበር፡፡

•  ታላላቅ ሕልሞችን ለማለምና ከግባቸው ለማድረስ የሚያስፈልገው ታላቅ ሰው መሆን ሳይሆን ከግብ ለመድረስ የቆረጠ ማንነት እንደሆነ እንዲያውቁ የተቻለኝን አደርግ ነበር፡፡

•  ሃብታም ሰው ብዙ ገንዘብና ቁሳቁስ ያለው ሰው ሳይሆን የሚያስፈልገውን ነገር ያወቀ ሰው እንደሆነ እንዲያውቁልኝ እጥር ነበር፡፡

•  ራሳቸውን ከሌላው ጋር ማነጻጸርና ማወዳደር እንደማይገባቸውና ከእነርሱ የሚያንስ ሰው እንዳለ ሁሉ የሚበልጥም ሰው የመኖሩን እውነታ እንዲቀበሉት አስረዳቸው ነበር፡፡

•  አመለካከታቸውን መቆጣጠር እንዳለባቸው አለዚያ አመለካከታቸው እነሱን እንደሚቆጣጠራቸው እንዲማሩ እሞክር ነበር፡፡

•  እጅግ በጣም የሚወዷቸውና የሚያከብሯቸው ነገር ግን ያንን በቅጡ ለመግለጽ የማይሆንላቸው ብዙ ወዳጆች እንዳሏቸው አስረዳቸው ነበር፡፡ 

•  እውነተኛ ጓደኛ ማግኘት እጅግ ከባድ እንደሆነ፣ ያንን ያገኘ ግን የሕይወቱን አብዛኛውን ችግሩን እንዳቃለለ እንዲያውቁ እመክራቸው ነበር፡፡

•  የቅርብ ወዳጆቻቸውን ለማቁሰል ሰከንድ እንደሚበቃ ለመፈወስ ግን አመታት እንደሚፈጅ እንዲገባቸው እጣጣር ነበር፡፡

•  ሰዎችን ለመቆጣጠር በመሞከር እንደሚያጧቸው፣ ምርጫቸውን በማክበር ነጻነታቸውን በመስጠት ግን ለዘለቄታው ወዳጆች እንደሚያደርጓቸው እንዲገነዘቡ ለማድረግ እሞክር ነበር፡፡

•  የውስጥ ሰላም ለማግኘት ከሰዎች ይቅርታን ማግኘት ብቻ ሳይሆን ራሳቸውንም ይቅር ማለት እንደሚገባቸው እንዲያስታውሱ አሳስባቸው ነበር፡፡

•  ከመናገር በሚቆጠቡበት ነገር ላይ ጌታ፣ በልቅነት ለሚናገሩት ንግግር ደግሞ ባሪያ ሆነው እንደሚኖሩ አሳውቃቸው ነበር፡፡

•  እውነተኛ ደስታ የውሳኔ ጉዳይ እንደሆነ፣ በማንነታቸውና ባላቸው ነገር ደስተኛ መሆን፣ አለዚያ በቅንአትና በፉክክር ወጥመድ ውስጥ እንደሚገቡ አስገነዝባቸው ነበር፡፡

•  በአጭሩ በዋናው የሕይወት ነገር ላይ ያተኮረ ዝንባሌ ቢኖራቸው እመክራቸዋለሁ፡፡

@Human_Intelligence
@Human_Intelligence