2022-06-10 23:31:18
ጋሽ ግርማ ከበደ ልክ የዛሬ ሃያ ዓመት ገደማ ያረፈ ታላቅ መምህር ነበረ:: ሲያስተምር እኔ ባልደርስበትም በእርሱ የተማሩ መምህራን ግን እኔን አስተምረውኝ ነበርና ስለዚህ ታላቅ መንፈሳዊ ሰው ብዙ ሰምቼአለሁ::
ከሁሉም ከልቤ የቀረው ግን ጋብቻውን ሊፈጽም ሲል ያደረገው ነው:: የሰርጉን ወረቀት ለታዳሚዎቹ ሲበትን ለአቶ እገሌ እገሌ ብሎ ይጽፍና ከ ጋር ብሎ እንደሚጽፍ የታወቀ ነው:: እርሱ ግን ለመጀመሪያ የጻፈለት ተጠሪ ልዩ ነበር::
ለጌታዬ ለአምላኬ ለመድኃኒቴ ኢየሱስ ክርስቶስ
ከእናትህ ከድንግል ማርያም ጋር እና ከመላእክትህ ጋር በሰርጋችን ላይ እንድትገኝልን በማክበር ጠርተንሃል የሚል ነበር:: ይህንን ጥሪም በመንበሩ ፊት እንዲያስቀምጡለት ለካህናት ሠጣቸው::
ይህንን የመምህሩን ነገር የሰማ አንድ ወንድም ሃሳቡን ወደ መዝሙር ቀይሮ እንዲህ ብሎ ግጥም አደረገው::
በሰርጋችን ዕለት እንድትባርከን
ጌታ ጠርተንሃል በእምነት ሆነን
ከእናትህ ጋራ ከእመቤታችን
ከመላእክትህ ጋር ና በሰርጋችን
ከሐዋርያት ጋር ና በሰርጋችን
በገሊላ መንደር እንደተገኘህ
ና በእኛ ድንኳንም ጌታ ስንጠራህ
የጥሪ ወረቀት ልከናል እንዳትቀር
አንተ ነህ ክብራችን የቤታችን ፍቅር
በነገው ዕለት እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ ባሳደገችኝ ደብር በአፍሪካ ኅብረት ደብረ ምሕረት ቅዱስ ሚካኤል ካቴድራል ጋብቻችንን እንፈጽማለን:: እኔ የጋሽ ግርማ ከበደ ዓይነት ሕይወት ቅድስና ባይኖረኝም እሱ ያገለገላት ቤተ ክርስቲያን ልጅ እንደመሆኔ እርሱ የጠራውን መሐሪ አምላክ ጠርቼአለሁ:: አምላክና ሰው በሆድዋ ውስጥ የተሞሸሩባት ወላዲተ አምላክ ወደ እኔ ብትመጣ ከቃና በላይ ብዙ የጎደለ ነገር ታገኛለችና እርስዋም አደራ ብያለሁ::
380 views20:31