የታየህን ያህል ተንቀሳቀስ አንድ ምሽት ላይ አባት ልጁን ወደ ሲኒማ ቤት ሊወስደው ውጪ መንገድ ላይ መኪና ውስጥ እየጠበቀው ነው፡፡ ልጅ ከቤት እንደወጣ በጣም ስለጨለመበት ስልኩን አውጥቶ አባቱ ጋር ደወለ፡፡ • ልጅ፡- “አባዬ እንዴት ልምጣ? ጨለማ ስለሆነ አይታይም”፡፡ • አባት፡- “ምን ያህል ይታይሃል?” • ልጅ፡- “አምስት እርምጃ ያህል ብቻ ነው የሚታየኝ” • አባት፡- “አምስት እርምጃ ተራመድ” • ልጅ፡- “እሺ” (አምስት እርምጃ ተራመደ) • አባት፡- “አሁንስ ምን ያህል ይታይሃል?” • ልጅ፡- “አሁንም ሌላ አምስት እርምጃ ያህል ርቀት ይታየኛል” • አባት፡- “በፊትህ የሚታይህን አምስት አምስት እርምጃ እያልክ ከመጣህ እኔ ጋ ትደርሳለህና የታየህን ያህል ተንቀሳቀስ” ልጅ ብዙም ሳይቆይ አባቱ ጋር ደረሰ፡፡ ሁሉም ነገር ጥጉ ድረስ እስኪታይህ አትጠብቅ፡፡ በሚታይህ መጠን ተራመድ፡፡ የሚታይህን ያህል ስትራመድ፣ ከመራመድህ በፊት ያልታየህን ማየት ትጀምራለህ፡፡ ሁሉንም ነገር እስከምታውቅ አትጠብቅ፡፡ በምታውቀው ልክ ስራን ጀምር፡፡ በምታውቀው እውቀት መጠን ስራን ስትጀምር፣ ያንን ከመጀመርህ በፊት ያልነበረህ ልምድና እውቀት ወደ አንተ ይመጣል፡፡ ሁሉም ሰው እስኪቀበልህ አትጠብቅ፡፡ የሚቀበሉህ ላይ በማተኮር ተሰማራ፡፡ በሚቀበሉህ ላይ ስታተኩርና ደስተኛ ስትሆን፣ ቀድሞ የማይቀበሉህ ሁሉ አንተን ከመቀበል ውጪ ምርጫ አይኖራቸውም፡፡ የጠየከው ነገር ሙሉ በሙሉ እስኪሰጥህ አትጠብቅ፡፡ የተሰጠህን ተቀበልና በዚያ በመጀመር የምትችለውን አድርግ፡፡ በተሰጠህ በጥቂቱ የምታደርገው ጥረትና የምታከናውነው ነገር የቀረው እንዲለቀቅልህ መንገድ መክፈቱ አይቀርም፡፡ አትቀመጥ! የታየህን ያህል ተንቀሳቀስ! ስራ! 64 viewsKasse, 11:28