Get Mystery Box with random crypto!

5. የሽብር ወንጀል እና የሚያስከትለው ተጠያቂነት በኢትዮጵያ ህግ ስርዓት በአገራችን በተለያየ ወቅ | Tsegaye Demeke - Lawyer

5. የሽብር ወንጀል እና የሚያስከትለው ተጠያቂነት በኢትዮጵያ ህግ ስርዓት
በአገራችን በተለያየ ወቅት የሽብር ድርጊቶች የተፈፀሙ ሲሆን በ1970 ዎቹ ሲፈጸም የነበረው የቀይ ሽብርና የነጭ ሽብር ድርጊት በአገራችን በዜጎች ላይ ከፍተኛ ስጋትን ከፈጠሩ ሁኔታዎች ውስጥ የሚመደብ ነዉ፡፡ በአዲስ አበባ ከተማ 1990 ዎቹ በትግራይ ሆቴል፣ በአክሱም ሆቴል፣ በጊዎን ሆቴል እና በድሬ ደዋ በራስ ሆቴል እንዲሁም በ2000 ዓ.ም በታክሲ ላይ በተፈጸመ ጥቃት በሰውና በንብረት ላይ ጉዳት ደርሷል፡፡

በሀገራችን በ1996 ዓ.ም በወጣው የወንጀል ህግ የሽብር ወንጀልን መከላከል እና ለመቅጣት ጥረት የተደረገ ሲሆን ወንጀሉ ካለዉ አስከፊ ባህሪ በ2001ዓ.ም ራሱን የቻለ አዋጅ ቁጥር 652/2001 ሊወጣ ችሏል፡፡ ነገር ግን አዋጅ ቁጥር 652/2001 መሰረታዊ መብቶች እና ነጻነቶችን የሚገድብ ሆኖ በመገኘቱ በአዋጅ ቁጥር 1176/2012 እንዲተካ ተደርጓል፡፡

የሽብር ወንጀልን ለመከላከል እና ለመቆጣጠር የወጣ አዋጅ 1176/2012 አንቀጽ 3 መሰረት የሽብር ድርጊት ማለት፡-
1) ማንኛውም ሰው የፖለቲካ፣ የሃይማኖት ወይም የርዕዮተ ዓለም ዓላማን ለማራመድ በማሰብ ህዝብን ወይም የተወሰነ የህብረተሰብን ክፍል ለማሸበር ወይም መንግስትን፣ የውጭ አገር መንግስትን ወይም ዓለም አቀፍ ድርጅትን ለማስገደድ፡- ሀ) በሰው አካል ላይ ከፍተኛ ጉዳት ያደረሰ፤ ለ) የሰውን ሕይወት ለአደጋ ያጋለጠ፤ ሐ) ሰውን ያገተ ወይም የጠለፈ፤ መ) በንብረት፣ በተፈጥሮ ሐብት ወይም አካባቢ ላይ ከፍተኛ ጉዳት ያደረሰ፤ ወይም ሠ) የሕዝብ ወይም ማህበራዊ አገልግሎት እንዳይሰጥ በከፍተኛ ሁኔታ ያስተጓጎለ እንደሆነ ከአስር ዓመት እስከ አስራ ስምንት ዓመት በሚደርስ ጽኑ እስራት ይቀጣል፡፡

2) በዚህ አንቀጽ ንዑስ አንቀጽ (፩) የተጠቀሰውን አላማ ለማስፈጸም የተፈጸመው ተግባር ሰውን መግደል ወይም በታሪካዊ ወይም የባሕል ቅርስ ወይም የመሰረተ ልማት አውታሮች ላይ ከፍተኛ ጉዳት በማድረስ እንደሆነ ከአስራ አምስት ዓመት እስከ ዕድሜ ልክ በሚደርስ ጽኑ እስራት ወይም በሞት የሚያስቀጣ መሆኑን ደንግጓል፡፡

በአዋጁ ከአንቀጽ 3 ውጭ ያሉ የሽብር ወንጀሎች፡-
1. መዛት፡- በአዋጅ ቁጥር 1176/2012 አንቀጽ 5 መሰረት ከላይ በአንቀፅ 3 ስር የተገለፀውን የሽብር ወንጀል ለመፈፀም መዛት ከአንድ ዓመት እስከ አምስት ሊደርስ በሚችል ፅኑ እስራት የሚያስቀጣ ተግባር ተደርጎ ተደንግጓል፡፡ ዛቻ የፈጸመው ሰው አደርገዋለሁ ያለውን ድርጊት ለማድረግ ለመፈጸም ያለው አቅም፣ ዕድል ወይም በሌላ ሰው የሚያስደርግ ከሆነ ይህንን ለማድረግ አቅም ያለው መሆኑ ወይም በመዛቱ ምክንያት ህብረተሰቡ ወይም የተወሰነ የህብረተሰብ ክፍል የተሸበረ ወይም ሽብር ሊፈጥር የሚችል መሆኑን በመመዘን ነው፡፡
2. ማቀድና መሰናዳት- የሽብር ድርጊትን ለመፈጸም ማቀድና ማሰናዳት በራሱ የሚያስቀጣ ተግባር ሲሆን በሁለቱ መካከል ግልጽ ወሰን ማስቀመጥ ያስቸግራል፡፡ የአዋጅ ቁጥር 1176 አንቀጽ 6 በአዋጁ አንቀጽ 3 የተመለከተውን ድርጊት ለመፈጸም ማቀድና መሰናዳት የሚያስቀጣ እንደሆነ ይደነግጋል፡፡ ድንጋጌው ለማቀድ ከሶስት እስከ ሰባት ዓመት እንዲሁም ለመሰናዳት ከአምስት እስከ አስራ ሁለት ዓመት የሚያስቀጣ ስለመሆኑ ያስቀምጣል፡፡ በአዋጁ አንቀጽ 2 ንኡስ አንቀጽ 6 ማቀድ ማለት በአዋጁ አንቀጽ 3 የተመለከተውን የሽብር ድርጊት ለመፈጸም ከሀሳብ ባለፈ ወንጀሉን ለመፈጸም የሚፈጸምበትን ሁኔታ፣ ቦታ፣ ጊዜ ወይም መሰል ጉዳዮችን የመለየት ወይም የመወሰን ጉዳይ እንደሆነ ትርጉም ያስቀምጣል፡፡ ኢትዮጵያ የፈረመችው የአፍሪካ ህብረት የሽብር መከላከልና መቆጣጠር ኮንቬንሽን ማቀድ የሚያስቀጣ ተግባር ሆኖ እንዲካተት የሚያስቀምጥ ከመሆኑ አንጻር ማቀድ በአዋጁ ውስጥ ተካቷል፡፡

3. ማደም ማለት ሁለትና ከዛ በላይ የሆኑ ሰዎች የወንጀል ድርጊት ለመፈጸም የተስማሙ እንደሆነ ስለመሆኑ ከወንጀል ህጉ አንቀጽ 38 ይዘት ለመረዳት ይቻላል፡፡ በአዋጁ የሽብር ወንጀልን ለመፈጸም ማደም ከአምስት ዓመት እስከ አስራ ሁለት ዓመት ድረስ ሊያስቀጣ እንደሚችል ተደንግጓል፡፡ ማደም ከማቀድ እና መሰናዳት ለየት የሚያደርገው የድርጊቱ ፈጻሚዎች ሁለትና ከዛ በላይ መሆናቸው ብቻ ሳይሆን እነዚህ ሰዎች ድርጊቱን ለመፈጸም የተስማሙ መሆኑን የሚጠይቅ ነው፡፡ ስምምነት መኖሩ በማስረጃ መረጋገጥ ያለበት ሲሆን በግልጽ ወይም በተዘዋዋሪ በሰዎቹ መካከል ስምምነት ለመኖሩ የሚያስረዳ ሁኔታ ካለ አድማ ስለመኖሩ ለማረጋገጥ በቂ ይሆናል፡፡

4. በሐሰት ማስፈራራት- በሽብር ድርጊት በሀሰት ማስፈራራት በቀላል እስራት ወይም ጉዳት ያስከተለ እንደሆነ ከሶስት ዓመት እስከ አስር ዓመት በሚደርስ ጽኑ እስራት የሚያስቀጣ ስለመሆኑ በአዋጁ አንቀጽ 8 ላይ ተደንግጓል፡፡ በሀሰት ማስፈራራት በሽብር ህግ ውስጥ እንዲካተት የተደረገበት ዋና ምክንያት ሰዎች በዘፈቀደ የሽብር ጥቃት እንደሚያደርሱ በመግለጽም ሆነ በማስመሰል ዜጎችን ለአደጋ እንዳያጋልጡ ማድረግ ነው፡፡
5. ድጋፍ ማድረግ፡- ወንጀሉን የሚፈፅም ሰው መርዳት ከሰባት እስከ አስራ አምስት ዓመት በሚደርስ ጽኑ እስራት የሚያስቀጣ ድርጊት ሆኖ በአዋጁ አንቀጽ 9 ስር ተደንግጎ ይገኛል፡፡ የድጋፍ ዓይነቶችን ስንመለከት የሽብር ወንጀል አፈጻጸምን ለመርዳት በማሰብ ሰነድ ወይም መረጃ ማዘጋጀት፣ ማቅረብ፣ መስጠት፣ የምክር አገልግሎት፣ የሙያ ድጋፍ፣ ጉዳት ማድረስ የሚችሉ መሳሪያ፣ ኬሚካሎች ወይም ንጥረ-ነገሮች ያዘጋጀ፣ ያቀረበ የሰጠ ወይም የሸጠ ድጋፍ እንዳደረገ ይወሰዳል፡፡

6. ማነሳሳት፡- አንድ ሰው ሌላው ሰው የሽብር ድርጊት እንዲፈጽም ለማድረግ በመጎትጎት፣ ተስፋ በመስጠት፣ በገንዘብ፣ በስጦታ፣ በማስፈራራት ወይም በማናቸውም ሌላ መሰል ዘዴ ያነሳሳ እንደሆነ ለድርጊቱ በአንቀጽ 3 ላይ በተቀመጠው ቅጣት እንደሚቀጣ በአንቀጽ 10(1) ተደንግጓል፡፡ ይህ ድንጋጌ ድጋፍ ከማድረግ የሚለየው ድርጊቱን የሚፈጽመው ሰው በራሱ ፍላጎት የሚፈጽመው ሳይሆን ማነሳሳት በፈጸመው ሰው ምክንያት ሲሆን ድጋፍ ማድረግ ደግሞ ወንጀል አድራጊው ሀሳብ ያለው ሆኖ ድጋፍ የሚያደርገው ሰው የድርጊቱ ፈጻሚ ሀሳቡን እንዲያሳካ ማመቻቸት ወይም አስተዋጽዎ ማበርከትን የሚመለከት ነው፡፡

በአጠቃላይ የሽብር ወንጀል ከፍተኛ ጉዳት የሚያስከትል አስከፊነት ድርጊት ነው፡፡ ድርጊቱን ለመከላከልና ለመቆጣጠር በሀገራችን ጨምሮ የተለያዩ እርምጃዎች ተወስደዋል፣ በመወሰድ ላይ ይገኛሉ፡፡ ይበልጥ ወንጀሉን ለመከላከልና ሊደርስ የሚችለውን ጉዳት ለመቀነስ እንዲሁም ወንጀሉ ተፈፅሞ ከተገኘ ተጠያቂነትን ለማረጋገጥ በተለይ የህግ አስፈፃሚ የተቋማትና የባለሙያዎችን አቅም ማጎልበት ወሳኝ ጉዳይ ነዉ፡፡ ህብረተሰቡም ወንጀልን በመከላከልና ወንጀል ፈጻሚዎችን ለህግ እንዲቀርቡ ከማድረግ አንፃር እገዛ በማድረግ የበኩሉን ድርሻ ሊወጣ ይገባል፡፡
Ministry of Justice