Get Mystery Box with random crypto!

የሽብር ወንጀልና የሚያስከትለው ተጠያቂነት 1. መግቢያ የሽብር ድርጊት በዓለም አቀፍ ደረጃ ተቀባ | Tsegaye Demeke - Lawyer

የሽብር ወንጀልና የሚያስከትለው ተጠያቂነት

1. መግቢያ
የሽብር ድርጊት በዓለም አቀፍ ደረጃ ተቀባይነት ያገኘ አንድ ወጥ ትርጉም የሌለው በመሆኑ በተለያዩ ሀገራት የድርጊቱ አረዳድ ላይ ልዩነት ይስተዋላል፡፡ በአንዱ አገር የሽብር ተግባር የሆነው ድርጊት በሌላው እንደ የነፃነት ትግል ሆኖ ይቆጠራል፤ በአንዱ የነፃነት ትግል ተደርጎ የሚታየው ተግባር በሌላው የሽብር ተግባር ሆኖ ይታያል፡፡ ይህ እንደተጠበቀ ሆኖ በዓለም ሰላም እና ደኅንነት ላይ ከፍተኛ ስጋት ከሆኑ እና ከፍተኛ ጉዳት በማድረስ ላይ ከሚገኙ ወንጀሎች ውስጥ አንዱ ስለመሆኑ ተቀባይነት ያገኘ ጉዳይ ነው፡፡ ከዚህ የተነሳ ወንጀሉን ለመከላከል እና ለመቆጣጠር ሀገራት በተናጠል እና በጋራ የተለያዩ ስትራቴጂዎችን በመንደፍ ተግባራዊ በማድረግ ላይ ይገኛሉ፡፡

ሀገራችንም በተለያዩ ጊዜያት የወንጀሉ ሰለባ የነበረች ሲሆን ወንጀሉን ለመከላከል ህግ ማዕቀፍ ጨምሮ የተለያዩ እርምጃዎችን ወስዳለች፡፡ ከዚህ አንፃር የፀረ-ሽብርተኝነት አዋጅ ቁጥር 652/2001 ማውጣት አንዱ እርምጃ ሲሆን በአዋጁ የሚስተዋለውን ክፍተት ለመቅረፍ አዋጁ የሽብር ወንጀልን ለመከላከልና ለመቆጣጠር የወጣ አዋጅ ቁጥር 1176/2012 ሆኖ ተሻሽሎ ወጥቷል፡፡ በዚህ ጽሁፍ ስለ ሽብር ምንነት፣ የሚያስከትለዉ ጉዳት፣ ወንጀሉን ለመከላከል ያለዉ ዓለም ዐቀፍና ሀገር አቀፍ ህጎች እና የወንጀሉ የሚያስከትለው ተጠያቂነት ለመዳሰስ ተሞክሯል፡፡

2. የሽብር ወንጀል ምንነት፣ የሚፈፀምበት ዓላማ እና የሚያስከትለው ጉዳት
ሽብር የሚለው ቃል የተሰጠ ወጥ ትርጉም ባይኖርም ከብዙ ሀገራት ህጎች መረዳት የሚቻለዉ አንድን ርዕዮት ዓለም፣ የፖለቲካ ወይም የሃይማኖት አስተሳሰብ በሕዝብ ወይም በመንግሥት ዘንድ ተቀባይነት እንዲኖረው ለማድረግ ወይም ለማሳካት ኃይልን በመጠቀም በዜጎች ላይ ፍርሃትን በመፍጠር የማይፈልጉትን እንዲቀበሉ የማድረግ ተግባር ነዉ፡፡ ከዚህ የምንረዳው ከሌሎቹ ወንጀሎች በተለየ መልኩ የድርጊቱ ፈጻሚ ድርጊቱን ከጉዳዩ ጋር ቀጥተኛ ግንኙነት በሌላቸው ንጹሃን ሰዎች፣ የመንግሥት ተቋማት፣ ባለሥልጣኖች፣ ጦርነት በሌለበት ሁኔታ ወታደራዊ ተቋማት ወዘተ ላይ በመፈጸም ሌላኛው ወገን መንግሥትና ሕዝብ እንዲገደድና ሃሳቡን ወይም አስተሳሰቡን እንዲቀበል ለማድረግ የሚፈጸም ተግባር መሆኑን ነው፡፡ ሌሎች ወንጀሎች ግን የሚፈፀሙት ቀጥታ ግንኙነት ባለው አካል ላይ ነው፡፡
የሽብር ወንጀል መሠረታዊ ዓላማ ሲታይ ወንጀሉ የሚፈፀመው የፖለቲካ፤ የሐይማኖት ወይም የአይዲዮሎጂ ጉዳዮችን መነሻ በማድረግ ነው። ከዚህ አንፃር በሀገራችን ህግ መሰረት የሽብር ድርጊት ማንኛውም ግለሰብ ወይም ቡድን የፖለቲካ፣ የሃይማኖት ወይም የርዕዮተ ዓለም ዓላማን ለማራመድ በማሰብ ህዝብን ወይም የተወሰነ የህብረተሰብን ክፍል ለማሸበር ወይም መንግስትን፣ የውጭ አገር መንግስትን ወይም ዓለም አቀፍ ድርጅትን ለማስገደድ በሚል በሰው ወይም በንብረት ላይ ጉዳት ማድረስ መሆኑ ተገልፆል፡፡ ይህም በአዋጅ ቁጥር 1176/2012 በአንቀፅ 3 ላይ እንደተገለጸው ለሁለት ዓላማ ማለትም የፖለቲካ፣ የሃይማኖት ወይም የርዕዮተ ዓለም ዓላማን ለማራመድ በማሰብ እና ህዝብን ወይም የተወሰነ የህብረተሰብን ክፍል ለማሸበር ወይም መንግስትን፣ የውጭ አገር መንግስትን ወይም ዓለም አቀፍ ድርጅትን የማስገደድ አላማ ነው።

የሽብር ወንጀል የተለያዩ ጉዳቶችን የሚያስከትል ሲሆን በአብዛኛዉ በንብረት ወይም አገልግሎት ጉዳት የሚያድርስ፣ የሰውን ህይወትን የሚያጠፋ፣ በታሪካዊ ወይም የባሕል ቅርስ ወይም የመሰረተ ልማት አውታሮች ላይ ከፍተኛ ጉዳት የሚያደርስ ነው፡፡ እንዲሁም የህዝብ አገልግሎትን ያስተጓጉላል፡፡

3. የሽብር ወንጀል ታሪካዊ ዳራ
የሽብር ወንጀል ጽንሰ ሃሳቡ ሲታይ በአብዛኛዉ ቃሉ ሽብርተኝነት (terrorism) በሚለው ቃል ቢገለፅ ይታያል፡፡ ይህ ቃል ለመጀመሪያ ጊዜ በ18ኛው ክፍለ ዘመን በፈረንሳይ አብዮት ወቅት (እ.ኤ.አ መስከረም 1793- ሐምሌ 1794) የተገኘ ቃል እንደሆነ ድርሳናት ያስረዳሉ፡፡ በዚህ ወቅት የፈረንሳይ የአብዮታዊ አስተዳደሩ የአብዮቱ ጠላት ናቸው በሚል በሚጠረጠሩ ዜጎች ላይ ጠንካራ እርምጃ እንዲወሰድ ማዘዙን እና ንጉስ ናፖሊዮን የስፔንን መውረር ተከትሎ ሕዝባዊ አመጽ መቀስቀሱንና የሽምቅ ተዋጊዎች መስፋፋትን መሰረት በማድረግ ሽብርተኝነት የ18ኛው ክፍለ ዘመን ክስተት አድርገው ያስቀምጣሉ፡፡

ወንጀሉ በተለያዩ ሀገራት ቅርጽና ይዘቱን እየቀያየረ በዜጎች ላይ ከፍተኛ ቁሳዊ፤ ማህበራዊ እንዲሁም ሀይማኖታዊ ጉዳቶችን እያስከተለ እስካሁን የቀጠለ ጉዳይ ነዉ፡፡ በቅርቡ እንኳ እ.ኤ.አ ከ1990 ጀምሮ የተባበሩት መንግስታት የጸጥታው ምክር ቤት የተለያዩ የውሳኔ ሀሳቦችን ከማሳለፍ ባለፈ፤ ሊብያ፣ ሱዳን እና አፍጋንስታንን ሽብረተኛን ይደግፋሉ በሚል የውሳኔ ሀሳብ በማስተላለፍ የኢኮኖሚ ማዕቀብ ጥሎባቸዋል፡፡

ሌላዉ በዓለም ላይ አስደንጋጭ ክስተት የነበረው የአሜሪክ መንትዮች ህንጻ ላይ ከተፈጸመበት ከ2001 ጀምሮ ያለው ጊዜን ይመለከታል፡፡ በ2001 ዓ.ም በአሜሪካው ላይ የተፈጸመው ጥቃት ዓለም አቀፍ ተቋማትም ሆኑ አገራት በሽብርተኝነት ላይ ያላቸውን አቋም እንዲፈትሹ ከማድረጉ ባለፈ ጠንካራ የህግ ማስፈጸም ስራ እንዲያከናውኑ አድርጓቸዋል፡፡ ይህ ክስተት አገራት ድርጊቱን ለመቆጣጠር ቀድሞ የነበራቸውን አጠፋዊ ምላሽ ስትራቴጂ ወደ ቀድሞ መከላከል እንዲቀይሩ አስገድዷቸዋል፡፡ የጸጥታው ምክር ቤትም አልቃይዳን ትኩረት ያደረገ የሽብር መከላከል ትኩረትን በመተው ሁሉን አቀፍ የሽብር ወንጀል መካለከል ላይ እንዲያተኮር፣ ሽብር የዓለም አቀፍ ደህንነትና ሰላምና ደህንነት ስጋት እንደሆነ በመቀበል ሁሉም አባል አገራት ድርጊቱን ወንጀል በማድረግ እንዲደነግጉ እና የህግ ማስፈጸም ስርዓታቸውን እንዲያጠናክሩ አቅጣጫ በማስቀመጡ በተለይ አባል ሀገራት ሽብር ህግ እንዲያወጡ አስገድዷቸዋል፡፡

4. ወንጀሉን ለመከላከል የሚያስችል አለም አቀፍ የህግ ማዕቀፍ
የሽብር ወንጀል በየትኛዉም ሀገርና ዜጎች ላይ ሊፈጸም የሚችል ወይም የሚፈጸም ዉስብስብንና አስከፊ ወንጀል ነው፡፡ ይህ ማለት የሽብር ወንጀል ድንበር ተሻጋሪ ወንጀሎች (Transnational Organized Crime) ከሚባሉት ዉስጥ አንዱ ነዉ፡፡ በዓለም አቀፍ ደረጃ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት (ተመድ) የሽብር ድርጊትን ለመከላከል እና ለመቆጣጠር በተለያዩ ጊዜ የውሳኔ ሃሳብን አስተላልፏል፡፡ ድርጅቱ እራሱን የቻለ ሁሉን አቀፍ የሽብር ድርጊት መከላከልና መቆጣጠር የሚያስችል ዓለም አቀፍ ስምምነት ከማውጣት ይልቅ በጉዳይ የተነጣጠለ የውሳኔ ሃሳብ ሲያስተላልፍና ስምምነቶች እንዲወጡ ሲያደርግ ቆይቷል፡፡ ይህ ወጥ የሆነ የህግ ማዕቀፍ አለመኖር በወንጀሉ ዙሪያ ያለው አረዳድ የተለያየ እንዲሆን አድርጎታል፡፡ እነዚህ ስምምነቶች ሀገራት የሽብር ድርጊትን ለመከላከልና ለመቅጣት ህግ ማውጣት እንዳለባቸዉ፣ ለአፈጻጸሙም ትብብር ሊኖር እንደሚገባ እና ልዩ ትኩረት የመስጠት ግዴታ እንደተጣለባቸው ያስረዳሉ፡፡