2022-07-29 17:23:13
ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ ሊቀጳጳስ /1932 1982/
ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ በ1933 ዓ.ም በያኔው የወሎ ጠቅላይ ግዛት ደሴ ከተማ ከአባታቸው አቶ ገበየሁ እና ከእናታቸው ወ/ሮ አሰለፈች ተወለዱ። ብፁዕነታቸው መዓርገ ጵጵስናን ከመቀበላቸው በፊት አባ መዝገበሥላሴ ይባሉ ነበር።
ዕድሜያቸው ለትምህርት እንደደረሰም በደሴ መድኃኔአለም ቤተክርስቲያን የመጀመሪያ እና ሁለተኛ ደረጃ መንፈሳዊ ትምህርታቸውን አጠናቀቁ። ከዚያም ትምህርታቸውን ለማስፋፋት ወደ ወሎ ላስታ ነአኩቶለአብ በመሔድ ከአባ ክፍሌ ዘንድ የውዳሴ ማርያም እና ቅዳሴ ማርያም ትርጓሜ አዕማደ ምሥጢርና ባሕረ ሐሳብ ተማሩ።
ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ በወቅቱ የወሎ ሀገረስብከት ሊቀጳጳስ ከነበሩት ብፁዕ አቡነ ይስሐቅ መዓርገ ዲቁናን ተቀበሉ። ከዚያም ወደ አዲስ አበባ መጥተው በመታሰቢያ ቤት ታዕካ ነገስት በኣታ ለማርያም ገዳም ገብተው ሐዲሳትን ተማሩ።ከዚያም ወደ ደብረሊባኖስ በመውረድ ምንኩስናን ተቀበሉ። በመቀጠል ወደአዲስዓለም በመሔድ አፈወርቅ መንገሻ ከተባሉ ሊቅ ቅኔን ከነአገባቡ ተማሩ።እንደገና ወደ ደብረሊባኖስ ተመልሰው መምህር ፍሥሐ ከተባሉ ሊቅ የሐዲሳት ትርጓሜ እና ትምህርተ ሃይማኖትን፣ መምህር ቢረሳው ከተባሉ ሊቅ ደግሞ መጽሐፈ ሊቃውንትን እንዲሁም ከመምህር ገብረ ሕይወት የሐዲሳት ትርጓሜን አደላድለው ተመረቁ።በዚሁ ደብርም ቅዳሴን ከነሥርዓቱ አጠናቀው ተመርቀዋል።ከብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ባስልዮስ መዓርገ ቅስናን ተቀበሉ።
ከዚህ በኋላ ብፁዕነታቸው የቁልቢ ቅዱስ ገብርኤል ገዳምን ለሁለት ዓመታት ካስተዳደሩ በኋላ በ1963ዓ.ም ወደ ግሪክ ተላኩ።በዚያም ፍጥሞ በተባለችው ደሴት ከሚገኘው ነገረሃይማኖት ትምህርት ቤት ተምረው በዲፕሎማ ተመረቁ ትምህርቱን በመቀጠልም ወደ አቴና ዩኒቨርሲቲ በማቅናት ለአራት ዓመታት የነገረ መለኮት ትምህርታቸውን በመከታተል በማስተርስ ተመርቀዋል። ወደ ስዊዘርላንድ በማቅናትም የፈረንሰኛ ቋንቋ አጥንተዋል።
ብፁዕነታቸው ወደኢትዮጵያ ከተመለሱ በኋላ ጥር ወር 1971 ዓ.ም በብፁዕ አቡነ ተክለሃይማኖት አንብሮተ ዕድ ከተሾሙት አባቶች አንዱ በመሆን መዓርገ ጵጵስና ተቀበሉ። የቅዱስ ፓትርያሪኩና የቅዱስ ሲኖዶስ ጸሐፊ ሆነው አገልግለዋል።በነበራቸው ኃላፊነትም ምቅዋመ ሕግ/ሕገ ቤተክርስቲያን/ አርቅቀዋል። ዘመን የማይሽራቸው "የቤተ ክርስቲያን ታሪክ በዓለም መድረክና የቤተ ክርስቲያን ታሪክ በኢትዮጵያ" የሚሉት መጻሕፍቶቻቸው ግሩም ሥራዎቻቸው ናቸው።
ከዚያም ሙሉ ትኩረታቸውን ብዙ ሥራ ወደሠሩበት የዝዋይ ገዳም አድርገዋል። ብፁዕነታቸው በዚያም ገዳሙንና መንፈሳዊ ትምህርት ቤቱን በማስፋፋት ታላቅ ሥራ ሰርተዋል። በነበራቸው ወጣቱን ትውልድ የመያዝ ፍላጎትና ችሎታ በወቅቱ በከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ይማሩ የነበሩ ተማሪዎችን በክረምት ወደ ገዳሙ እንዲገቡ በማድረግ የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ትምህርት በመማር ዘመኑን እንዲዋጁ አድርገዋል ። እርሳቸው ለሁለት ለሦስት ክረምቶች ሰብስበው ያስተማሯቸውና የመከሯቸው ተማሪዎች ዛሬ ቊጥራቸውን አበራክተው በማኅበረ ቅዱሳን ደረጃ በመሰባሰብ በዕውቀታቸውና በገንዘባቸው ቤተ ክርስቲያንን እና አባቶችን እያገለገሉ ይገኛሉ።
ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ለዐሥራ አንድ ዓመታት በዚህ ዓይነት ከፍተኛ እና አርአያነት ያለው አገልግሎት ካበረከቱ በኋላ ሐምሌ 22 ቀን 1982 ዓ.ም በመቂ ቅዱስ ሚካኤል ለሚገኙ ምእመናን አባታዊ ትምህርታቸውን ለመሠጠት ሲገሰግሱ በድንገት በደረሰባቸው የመኪና አደጋ በተወለዱ በኀምሳ ዓመታቸው ዐርፈዋል። የብፁዕነታቸው በረከት አይለየን።
255 viewszagol, 14:23