2022-02-07 22:33:23
ባዶ ምናምኖች☆•••
ርስቅ ቢልከሰከስ ኦና ልብ ላይሞላ
ባዶ ብለሽኛል እሽ በምን ልሙላ
ምናምንቴ መክሊት የአዱኒያ ሽራፊ
እጄ ላይ ካላየሽ በደጄ ላታልፊ
ብትሚ ገረመኝ
ብትቀሪ አመመኝ
ጅል ልቤ ሲያልምሽ ምናምኑን ጠላ ምንትሱን ናቀ
ከምናምንቴ አለም ባንቺው ተደበቀ
ደሞ በገሀዱ ምናምን ሳይጨምር በቃ እንዲሁ እንዳለሽ
ከምናምን በላይ ሁሉ ነገሬ ነሽ
ብሎ ሲያሞካሽሽ ልቤ በገናውን እየደረደረ
መልስሽ ምን ነበረ
"ምንም ስለሌለህ ባዶ ምናምን ነህ
የፍቅር ከተማ ከባዶ ነገር ላይ አይቆረቆርም
የፍቅር ምሶሶ ከባዶ አፍቃሪ ላይ እንደፀና አይኖርም"
ያልሽኝ ቀን አዝኜ
እጄ ኪሴ ገባ ባዶነት አገኘ
አዕምሮዬን ፈተሽኩ በየጥጋጥጉ አንቺው ከትመሻል
ፀሀይን ረስቶት ስትመጪ ይነጋል ስትሄጂ ይመሻል።
እውነት ነው ባዶ ነኝ ምናምን የለኝም
ኪሴ ቢበረበር ከአንቺው ፎቶ ሌላ አንዳች አይገኝም
ለኔ ግን ምናምን ሳይጨምር በቃ እንዲሁ እንዳለሽ
ከምናምን በላይ ሁሉ ነገሬ ነሽ
ደሞ መስሎሽ እንጂ ባዶነት ውል አልባ
በባዶ በር ነው ሙላት የሚገባ
ንፋስ የሚያጠፋው ኩራዝ ከማሳደድ
በእግዜሩ መሪነት በፍቅር ጨለማ ይሻላል መራመድ
ስልሽ ስብከት አልሽኝ
ካልሽማ ልንገርሽ
ምድር ባዶ ነበር ብሎ ሚጀምረው
የእግዜሩ መፅሐፍ እንደሚናገረው
ዳዊት በባዶ እጁ ድብ አንበሳ ጣለ
ሳምሶን በባዶ እጁ እልፍ አላፍ ገደለ
ባዶን የሚሞላ ለጨለመባቸው ብርሃን ይሁን አለ
ደግሞም ባዶ ማድጋ በእድሜ አመሻሽ ላይ በዘይት የሞላ
ማንም አልነበረም ከፍቅር አምላክ ሌላ።
ባዶነትን ጠልተው ጠብ ባለበት ሁሉ ለሚንዠቀዠቁ
ከሙላት የሚሻል ባዶነት እንዳለ መርምረው ባያውቁ
ከራስ በላይ ንፋስ በሚል ቢህላቸው በንፋስ አለቁ።
እንዲያው ነገሩ እንጂ እንኳንም ባዶ ሆንኩ
አልሙላ ዘላለም
በሀበሻነት ደሜ ከባዶነት በላይ ትልቅ ኩራት የለም
የኔዋ ኢትዮጵያ በባዶ ምድሮ ላይ በግዮን ምንጭ ውሃ አፈሮ ተቦክቶ ሰው ተፈጠረባት
በባዶ መሬት ላይ ድንጋይ ተፈልፍሎ ጥበብ ነገሰባት
በባዶ እግር ሩጠን ባለጫማወቹን አጀብ አስባልናቸው
በባዶ እጅ ተዋግተን ባለ ብረቶችን ብረት ቀማናቸው
ጊዜ ሸርተት ሲል በባዶ ሆዳችን እህል ለመናቸው።
የዘመን ሰላቢ በባዶ ሆዳችን መውደድ መዋደድን ሳናውቀው ነጥቆብን
ግማሽ ቁንፅል ሙላት ስለለቀቀብን
አኛም ሲሉ ሰምተን ባዶ ተባባልን አፋችንን ሞልተን
ልክ ነሽ!ልክ ነሽ! ባዶ ነኝ ሙሉ ነኝ ክርክር ከከንፈር አይወጣም
ሙሉ ነን ስላሉ ሙሉነት አይመጣም
ባዶም አይደለሁም
በማላውቀው ሀገር፣ በማላውቀው ቦታ፣ በማላውቀው ጊዜ፣ በነፍሴ ስርጣስርጥ በስጋና ደሜ
አለሁ እኖራለሁ ማደሪያ ሳይኖረኝ አንቺን ተሸክሜ
ደግሞም ባዶ ብሆን በባዶነቴ ውስጥ አንቺን ሳደላድል
አለሁ እኖራለሁ ሳልሞላ ሳልጎድል
ባማረ ቅላፄሽ በሚያስጨፍር ዜማሽ
ደረት የሚያስደቃ መርዶሽ ይሰማኛል
ልቤ ግን ሞኝ ነው መርቃት ይለኛል
በቃ ልመርቅሽ
ስለ ፍቅር ፅፈሽ ለፍቅር ደስኩረሽ ሙሉ ከምትሆኚ በአለም እንቶፈንቶ
ሙሉነትን ይንሳሽ ባዶ ፍቅር ሰጦ።
@cherekayechereka
@cherekayechereka
@cherekayechereka
332 views19:33