Get Mystery Box with random crypto!

​​❖ ሚያዝያ ፴ ❖ ❖ እንኳን አደረሳችሁ ❖ እንዲህ ኃጢአታችን ጽዋዑን ሞልቶ በተረፈበት በዚህ | ቤተ_ዜማ

​​❖ ሚያዝያ ፴ ❖
❖ እንኳን አደረሳችሁ ❖

እንዲህ ኃጢአታችን ጽዋዑን ሞልቶ በተረፈበት በዚህ ዘመን አንዲት ሰዓትም ውድ የሆነች የንስሃ ዕድሜ ናት:: እግዚአብሔር ግን ደግ ነውና ይሔው ሚያዝያን አስፈጸመን::

+ ባይገባን ነው እንጂ በዚሕች ወር ውስጥ:-
- ሚሊየኖች በደዌ የአልጋ ቁራኛ ሁነዋል::
- ሚሊየኖችም ለንስሃ ሳይበቁ እንዲሁ አንቀላፍተዋል (ሙተዋል)::

+ እስኪ እርሱ አምላካችን ቀሪዋን ዘመን ደግሞ ለንስሃና ለመልካም ሥራ ባርኮ ይስጠን::

" ቅዱስ ማርቆስ ወንጌላዊ "

በዚሕች ዕለት ከ72ቱ አርድእት አንዱ የሆነ: ወንጌላዊ: ሐዋርያ: ሰማዕት: ዘአንበሳና ርዕሰ ሊቃነ ዻዻሳት የተባለ ቅዱስ ማርቆስ በሰማዕትነት ግብፅ ውስጥ ዐርፏል::

+ ቅዱስ ማርቆስ እናቱ ማርያም: አባቱ አርስጥቦሎስ ይባላሉ:: በልጅነቱ ኦሪትንና የዘመኑን ጥበብ ሥጋዊ በሚገባ ተምሮ ክርስቶስን ከቤተሰቦቹ ጋር ተከትሏል::

+ የመጀመሪያ ስሙ ዮሐንስ ሲሆን ከ120ው ቤተሰብ በእድሜ በጣም ትንሹ (20 ዓመት) እርሱ ነበር:: ለ3 ዓመታት ከጌታ እግር ሥር ተምሮ: በበዓለ ሃምሳ ጸጋ መንፈስ ቅዱስን ተቀብሎ ለሐዋርያዊ አገልግሎት ብዙ ደክሟል::

በተለይ የግብፅና የኢትዮዽያ ቤተ ክርስቲያን አባት ነው:: ክህነትን ያገኘን ከርሱ ነውና:: ቅዱስ ማርቆስ 16 ምዕራፍ ያለውን ወንጌሉን ሲጽፍ ኪሩብ ገጸ አንበሳ በቀኙ: ሊቀ ሐዋርያት በግራው ሆነው ይራዱት ነበር::

ቅዱሱ ክቅዱስ ዻውሎስ: ከበርናባስና ዼጥሮስ ጋር ተጉዟል:: ከብዙ ስቃይና መከራ በኋላ ሰሜን አፍሪካ አካባቢ በዚህ ቀን በ60 ዓ/ም አካባቢ አረማውያን ገድለውታል::

ዳግመኛ በዚህ ቀን የቅዱስ ማርቆስን ወላጆችን እናስባቸው ዘንድ ይገባል::

❖ ቅዱስ አርስጥቦሎስ (አባቱ) የጌታ ቅን አገልጋይ የነበረ፡፡

❖ ቅድስት ማርያም (እናቱ)
- ከ36ቱ ቅዱሳት አንስት አንዷ:
- ጌታችንን ያገለገለች:
-  ቤቷን ለሐዋርያትና ለጌታ በስጦታ ያበረከተች ቅድስት ናት::

+ ቤቷም (ጽርሐ ጽዮን) የመጀመሪያዋ ቤተ ክርስቲያን ስትሆን ይህች ቤት መንፈስ ቅዱስ ወርዶባታል:: የእመቤታችን ግንዘትም ተከናውኖባታል::

❖ እግዚአብሔር ከሐዋርያዊው ቅዱስ ቤተሰብ በረከትን ያድለን::

ሚያዝያ 30 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት
1.ቅዱስ ማርቆስ ሐዋርያ
2.ቅዱስ አርስጥቦሎስ (አባቱ)
3.ቅድስት ማርያም (እናቱ)

ወርኀዊ በዓላት
1.ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቀ መለኮት
2.አባ ሣሉሲ ክቡር
3.ቅዱስ ጐርጐርዮስ ነባቤ መለኮት
4.ቅድስት ሶፍያ ሰማዕት

"+ . . . እጅግ ሰዎች ተከማችተው ይጸልዩበት ወደ ነበረው ማርቆስ ወደ ተባለው ወደ ዮሐንስ እናት ወደ ማርያም ቤት መጣ:: ዼጥሮስም የደጁን መዝጊያ ባንኩዋኩዋ ጊዜ ሮዴ የሚሏት አንዲት አገልጋይ ትሰማ ዘንድ ቀረበች:: የዼጥሮስ ድምጽ መሆኑንም ባወቀች ጊዜ ከደስታዋ የተነሳ ደጁን አልከፈተችም:: ነገር ግን ወደ ውስጥ ሮጣ ዼጥሮስ በደጅ ፊት ቆሞ እንዳለ አወራች::
+" (ሐዋ. 12:12-15)

ዝክረ ቅዱሳን
ወስብሐት ለእግዚአብሔር
https://t.me/bete_zemas
https://t.me/bete_zemas
https://t.me/bete_zemas