Get Mystery Box with random crypto!

#ስለማስመሰል_ርኅራኄው_ሰይጣንን_ተጠንቀቀው አምላካችን እግዚአብሔር አዳምን ሲፈጥረው ብቻውን ይሆ | 💠አምደ ሐይማኖት💠ዘ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ⛪️

#ስለማስመሰል_ርኅራኄው_ሰይጣንን_ተጠንቀቀው

አምላካችን እግዚአብሔር አዳምን ሲፈጥረው ብቻውን ይሆን ዘንድ መልካም እንዳልሆነ በማየቱ ከጎኑ አንዲት አጥንትን ወስዶ ሔዋንን ፈጠረለት፡፡ በገነት እንዲኖሩም አደረጋቸው፤ ከአንዲት ዕፅ (የሞት ዛፍ) በቀር ሁሉን እንዲበሉም አዘዛችው፤ ‹‹ከገነት ዛፍ ሁሉ ትበላለህ፤ ነገር ግን መልካምና ክፉን ከሚያሳውቀው ዛፍ አትብላ፤ ከርሱ በበላህ ቀን ሞትን ትሞታለህና››፡፡ (ዘፍ. ፪፥፲፮) ነገር ግን ዲያብሎስ ወደ እነርሱ ቀርቦ ለእነርሱ ያዘነ በማስመሰል ክፉ ምክርን መከራቸው፡፡ ‹‹ሞትን አትሞቱም፤ ከእርስዋ በበላችሁ ቀን፥ ዐይኖቻችሁ እንዲከፈቱ፥ እንደ እግዚአብሔር እንደምትሆኑ፥ መልካምንና ክፉን እንደምታውቁ እግዚአብሔር ስለሚያውቅ ነው›› (ዘፍ ፫፥፬) አላቸው፡፡ እነርሱም ዲያብሎስ ለእነርሱ አስቦና ራርቶ የመከራቸው ስለመሰላቸው ክፉ ምክሩን ተቀብለው የእግዚአብሔርን ትእዛዝ አፈረሱ፡፡ አስቀድሞ ፈጣሪያቸው ለእነርሱ ያደረገላቸውን ነገር ረስተው በዲያብሎስ የሐሰትና የማስመሰል ምክር ተታለሉ፡፡ ከዚያም ከፍሬው ቆርጠው በሉ፤ ሞትንም ሞቱ፤ ገነትን ያህል ቅዱስ ሥፍራ፤ እግዚአብሔርን ያህል ኃያል ፈጣሪ አስከፉ፡፡

ከዚያ ጊዜ ጀምሮ ሰይጣን በማስመሰል ርኅራኄው ሰዎችን እያባበለ ኃጢአት ሲያሠራ እና ከአምልኮተ እግዚአብሔር ሲለይ ኖረ፡፡ ሰይጣን ሰዎችን የሚያስትበት መንገድ ረቂቅ፣ እንደየዘመኑ ሁኔታም ተለዋዋጭ ነው፡፡ ሰይጣን ሰውን ሊያስት ሲመጣ እኔ ሰይጣን ነኝ፣ እነሆ ላስታችሁ መጥቻለሁ ተዘጋጅታችኋልን? ብሎ አይመጣም፡፡ ሰዎችን፣ ጊዜን፣ ሁኔታንና ቦታን ምክንያት እያደረገ በማታለያ ንግግሩ ቀርቦ በማስመሰል ሰዎችን ሸንግሎ ያስታል፡፡ የሰይጣን የማስመሰል ርኅራኄው የቱን ያህል አሳሳች እንደሆነ እንኳን አንረዳውም፡፡ ካሳተን በኋላም ያሳተን እርሱ መሆኑን መረዳት እየተሳነን ለውድቀታችን ሰዎችን፣ ዕድልን፣ ሁኔታዎችን እና ጊዜን ሰበብ እንድናደርግ ያደርገናል፡፡ ለዚህ ማሳያ የሚሆነው በተለይ በየጠበሉ ‹‹እከሊት ናት መድኃኒት ያደረገችብሽ፤ እከሌ ነው መድኃኒት ያደረገብህ›› እያለ ራሱን ሲያጋልጥ የምንሰማው የሰዎች ታሪክ እማኝ ነው፡፡ ‹‹ሐሰተኛ ነውና፤ የሐሰት አባትም ነው›› እንደተባለው፡፡ (ዮሐ. ፰፥፵፬) በዚህ ሐሰተኛነቱም አንዳንዶችን የአጋንንቱን ምስክርነት አምነው እንዲካሰሱ ባስ ሲል ወደከፋ ነገር እንዲደርሱ ያደርጋቸዋል፡፡

የሰይጣንን የማስመሰል ርኅራኄው አለማወቃችን ለጊዜ ከሚደርስብን ውድቀት በተጨማሪ በተደጋጋሚና በተመሳሳይ በኀጢአት እንድንወድቅ ያደርገናል፡፡ እርሱ ዘወትር እኛን በድካማችን ለማሳት አይሰለችምና እኛም እርሱ በእንዴት ያለ የማስመሰል ርኅራኄ ቀርቦ እንደሚያስተን ልናውቅበት እና ልንጠነቀቅ ይገባል፡፡

#ዛሬ_ላይ_ሰይጣን_እንዴት_ባለ_የማስመሰል_ርኅራኄው_ሰውን_እየጣለ_ነው?

ሀ/ ለራሳችን በምንሰጠው የተሳሳተ ግምት የተነሣ

ዲያብሎስ ትሕትናን ስለሚፈራ ሰዎች ለራሳቸው ከፍ ያለ የተሳሳተ ግምት እንዲኖራቸው ለማድረግ የሰዎችን አንደበት እየተጠቀመ ‹‹አንተ እንዲህ ነህ፤ አንች እንዲህ ነሽ›› እያለ በተሳሳተ መንገድ ይመራል፡፡ ዲያብሎስ ወጣቶችን ለማሳት ‹‹አንተ ወጣት አይደለህ?፤ በዕድሜህ ተዝናና›› በማለት በመዝናናት ውስጥ ያለውን ድቀት በመሸሸግ ለእነርሱ የራራ መስሎ ይመክራል፡፡ እኅቶቻችንን ‹‹አንቺ ወጣት አይደለሽ በዕድሜሽ አጊጪ››፤ ‹‹እግዚአብሔር ልብን ነው የሚያየው›› በማለት የምንዝር ጌጥ እንዲያጌጡ እና ከሥርዓተ ቤተክርስቲያን ውጪ እንዲሆኑ በማድረግ ባላሰቡትና ባልገመቱት መንገድ በፈተና እንዲወድቁ ያዳርጋቸዋል፡፡

የአንዳንድ ሰዎችን አንደበት እየተጠቀመ ዲያብሎስ መንፈሳውያንን ‹‹አንተ የእግዚአብሔር ሰው፣ አንቺ የእግዚአብሔር ሰው፣ ቅን ሰው፣ የዋህ ሰው፣ ጸሎተኛ ነህ፤ ጸሎተኛ ነሽ፤ ጾመኛ ነው፤ ጾመኛ ናት›› በማለት ልባችን ውስጥ ትዕቢት እንዲፈጠር ያደርጋል፤ እያታለለም የሌለንን ቅድስና ያለን እንዲመስለን ያደርገናል፤ በፍጻሜያችንም መንፈሳዊ ተጋድሎዋችን ላይ ድል ይነሣናል፤ ከዚያም በኋላ በቀላሉ በኃጢአት ይጥለናል፡፡ አንዳንድ ጊዜ ደግሞ ጌታችንን መድኃኒታችንን ኢየሱስ ክርስቶስን የመጽሐፍ ቅዱስ ቃል ጠቅሶ ሊፈትነው እንደሞከረው መንፈሳውያንንም ‹‹እነሆ፥ ጊንጦችንና እባቦችን፥ የጠላትንም ኃይል ሁሉ ትረግጡ ዘንድ ሥልጣንን ሰጠኋችሁ፤ የሚጎዳችሁም ምንም የለም›› (ሉቃ. ፲፥፲፱) በማለት ራሳቸውን ከአደጋና ከወረርስኝ እንዳይጠብቁ፣ በሕይወታቸው ላይ ያላቸውን ድርሻ አስረስቶ ሳያውቁት እግዚአብሔርን እንዲፈታተኑ ያደርጋቸዋል፡፡ ጌታችን በዲያብሎስ በተፈተነ ጊዜ ዲያብሎስ ወደ ቅድስቲቱ ከተማ ወሰደውና በመቅደስ ጫፍ ላይ አቁሞ ‹‹ስለ አንተ መላእክቱን ያዝልሃል፤ እግርህንም በድንጋይ እንዳትሰነካከል በእጃቸው ያነሡሃል፤ ተብሎ ተጽፎአልና የእግዚአብሔር ልጅስ ከሆንህ ወደታች ራስህን ወርውር አለው፡፡ ኢየሱስም ጌታ አምላክህን አትፈታተነው ተብሎ ደግሞ ተጽፎአል አለው፡፡›› (ማቴ ፬፥፮-፰) ዲያብሎስ በእምነታችን የጸናን እንዲመስለን በማድረግ የእግዚአብሔርን ጠብቆት እንድንፈታተን ያደርገናል፡፡

ባለጸጎችን ሀብትን የሰጠ እግዚአብሔር መሆኑን፤ በተገቢውም ሥርዓት ሊያስተዳድሩ እንደሚገባና በሀብት በንብረታቸው ላይ በእግዚአብሔር የተሾሙ መሆናቸውን ያስረሳቸዋል፡፡ ለድሆች ጥቂት ነገር ሲመጸውቱ፣ ለቤተክርስቲያን ሲረዱ፣ መመስገንን አጥብቀው እንዲሹ የማይገባቸውን ክብር እንዲመኑ ያደርጋቸዋል፡፡ የሰዎችን አንደበት እየተጠቀመ ‹‹የአንተ ቤት የአብርሃም ቤት ነው፤ እስኪ ሌሎችን ባለጸጎች ተመልከት! ንፉጎች ናቸው›› እያለ ራሱን ከአብርሃም ጋር እያነጻጸረ ለራሱ ያልተገባ ክብር እንዲሰጥ እያደረገ በከንቱ ውዳሴ ይጥላቸዋል፡፡

አገልጋዮችን ‹‹አንተ ስትቀድስ፣ አንተ ስትሰብክ፣ አንተ ስትዘምር ይደምቃልና ጠጠር መጣያ ይጠፋል›› እያስባለ አገልጋዮች እያገለገሉ የሚገለገሉ መሆናቸውን ያዘናጋቸዋል፡፡ አንዳንዴ ከንቱ ውዳሴን ሳያውቁት እንዲሹ ያደርጋቸዋል፡፡

ለ/ ወቅታዊ የሀገር ሁኔታዎችን በመጠቀም

ዲያብሎስ አጥብቆ ከሚጠላው አንዱና ዋነኛው ነገር የሰውን በአንድ ልብ በአንድ ሀሳብ ሆኖ እግዚአብሔርን ማምለክ ነው፡፡ ስለዚህም ሰዎችን የሚለያዩ ልዩ ልዩ መንገዶችን ይጠቀማል፡፡ መገኛችን አባታችን አዳም መሆኑን አስዘንግቶ ሰዎች በብሔር በመከፋፈል በሰዎች መካከል ልዩነትን እንዲፈጠር አድርጎ የባላጋራነት ስሜትን ይፈጥራል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ሰዎች በሚሰሙትና በሚናገሩት ቋንቋ መገልገልና ማገልገል የተከለከለ አስመስሎ ‹‹ለምን በቋንቋዬ አይሰበክም እና አይቀደስም›› በሚሉ ሀሳቦች ነገር ግን በውስጣቸው ምእመናን ከመንጋውና ከእረኛ አባቶች የመለየት ሥውር ተልዕኮውን ይፈጽማል፡፡
,,,,,,,,,

ይቀጥላል

ሐ/ #ዓለማዊ_አስተሳሰቦችን_መንፈሳዊ_በማስመሰል,,,,,,,,,
#ከዲያብሎስ_የማስመሰል_ርህራሔው_እንዴት_እንጠንቀቅ?,,,,,,,
ብጹዕ ወቅዱስ አቡነ ሺኖዳ ሣልሳዊ