Get Mystery Box with random crypto!

#መርህ አንድ:- ፍላጎት (Desire) የመጀመሪያው የስኬት መርህ ፍላጎት ነው። ከልብ የመነጨ | Addis Eyita

#መርህ አንድ:- ፍላጎት (Desire)

የመጀመሪያው የስኬት መርህ ፍላጎት ነው። ከልብ የመነጨ ፍላጎት። ፍላጎታችንን እንደ ዘር ልናየው እንችላለን። ፍሬ እንደሚያፈራ አምነን የምንዘራው ዘር። ነገር ግን ዛሬ ዘርተነው ዛሬውኑ ፍሬ የሚሰጠን ተክል የለም።

ፍላጎታችንም ልክ እንደ በቆሎ ወይም ማንኛውም ዘር ዛሬ ተዘርቶ በቂ ውሃ፤ በቂ ጸሃይ፤ በቂ እንክብካቤ ፤ካገኘ በኋላ በግዜው የሚያሽት ነው።

የምንፈልገውን ነገር ጥርት ባለ መልኩ ማወቁ ይጠቅመናል። ለመረጥነው ነገር ምን ያህል ፍላጎት እንዳለን ለማወቅ የምናደርጋቸውን ነገሮች መቃኘት ያስፈልገናል። ከምንም በላይ በውስጣችን ያለው የትዕግስት መጠን ፍላጎታችን ምን ያህል እንደሆነ ያስረዳናል።

ለምሳሌ ሰዓሊነት ፍላጎቱ የሆነ ሰው ባይከፈለው እንኳን ስዕል መሳሉን አያቆምም። አላማ ብለን ለመረጥነው ነገር በቀላሉ ሊገደብ የማይችል ፍላጎት ሊኖረን ይገባል። ጥልቅ ፍላጎት ማለት ወደኋላ እንዳናፈገፍግ የመመለሻውን ድልድይ እንደማቃጠል ያህል ነው።

#መርህ ሁለት:- እምነት (Faith)

እምነት አላማችን የሚገነባበት መሰረት ነው። የምንፈልገው ነገር ምንም ይሁን ምን እምነት ከሌለን ነዳጅ የሌለው መኪናን ለመንዳት እንደመሞከር ይሆንብናል። ደግነቱ እምነት በመጀመሪያ ባይኖረንም፤ በሂደት ልንገነባው የምንችለው ጥበብ ነው።

ለአእምሮአችን ቀና የሆኑ ነገሮችን በመመገብ እምነትን በሂደት ማዳበር ይቻላል። የምንፈልገውን ነገር ለማግኘት እምነት እጅግ ወሳኝ ነገር መሆኑን መዘንጋት የለብንም። ማርቲን ሉተር ኪንግ ስለ እምነት ደስ የሚል አባባል አለው ” እምነት ማለት ሙሉውን ደረጃ እስከየት እንደሚያደርሰን ባናውቅም እንኳ የመጀመሪያውን ደረጃ መውጣት ነው” ይላል።

#መርህ 3:- እራስን ማሳመን (Auto Suggestion-አውቶ ሰጀሽን)

አእምሮአችን እውነት ብሎ የሚቀበለው ነገር ደጋግመን የምንመግበውን ነው። እዚህ ላይ ይህንን በደንብ የሚያስረዳ አንድ ታሪክ ትዝ አለኝ። ታሪኩ እንዲህ ነው

ሁለት ውሾች የነበሩት አንድ ሰው ነበር። አዘውትሮ እኒህን ውሾች አደባባይ እየወሰደ እንዲደባደቡ ያደርግ ነበር። ታዲያ ተመልካቾቹ የትኛው ውሻ በእለቱ እንደሚያሸንፍ ሲጠይቁት “በደንብ የምመግበው ውሻ ነው” ሲል መለሰላቸው። ሁላችንም ውስጥ ሁለት ዉሾች አሉ የመልካም እና የክፋት፤ የልማት እና የጥፋት፤ የእውቀት እና የድንቁርና፤ የውድቀት እና የድል ውሾች። የበላይ ሆኖ የሚመራን ውሻ ዘወትር የምንመግበው ነው።

ለዚህ ነው ናፖሊዮን ሂል “አውቶ ሰጀሽን” ወይም ለራስ መልካም ነገሮችን ደጋግሞ በመንገር አእምሮአችንን ወደፈለግነው መንገድ መምራት እንደምንችል የሚነግረን። መንገር ብቻም ሳይሆን የሚያሳስበን!

#መርህ አራት:- በአንድ ነገር ላይ እራስን የተካኑ ማድረግ (ስፔሻላይዝድ ኖውሌጅ)-

ልንሰማራበት በመረጥነው ወይም ፍላጎት ባለን ሙያ ላይ የተሰማሩ ሰዎችን መተዋወቁ እና ቅርርብ መፍጠሩ ወሳኝ ነገር ነው። ጊዜያችንን የምናሳልፈው ከነማን ጋር ነው? የምናውቃቸው ሰዎች ወይም ጓደኞቻችን ለምንፈልገው ሙያ የሚያግዙን ናቸው?

ለምሳሌ:- ፕሮፌሰር ለመሆን ፍላጎት ያለው ሰው በተቻለው መጠን ዩንቨርሲቲ አካባቢ ካሉ ሰዎች ጋር ግንኙነቱን ቢያዳብር ይጠቅመዋል። ተዋናይ መሆን የሚመኝ ሰው እራሱን ከቲያትር መድረክ አካባቢ ማራቅ የለበትም። ሁላችንም የምንማረው ቀድመውን ካወቁት ነውና፤ የምንፈልገውን ነገር በቅጡ የሚያውቁ ሰዎችን ማወቁ ይጠቅመናል።

#መርህ አምስት:- ነገሮችን በህሊናችን መሳል- (Imagination)
ሁሉም ነገር ሃሳብ ነበር። ምንም ነገር እውን ሆኖ ከማየታችን በፊት በአንድ ሰው አይምሮ ውስጥ የተጠነሰሰ ሃሳብ ነበር። የምንፈልገውን ነገር እውን ሆኖ ከማየታችን በፊት በህሊናችን መሳል ትልቁ የስኬት ሚስጥር እንደሆነ ብዙዎች የተስማሙበት ነው። አላማችን ቁልጭ ብሉ በህሊናችን ከታየን ለጉዟችን ትልቅ ጉልበት አገኘን ማለት ነው። ምክንያቱም የጊዜ ጉዳይ ነው እንጂ እንደሚሳካ አእምሮአችን እየነገረን ነው።

#መርህ ስድስት:- እቅድ ማውጣት- (Organized planning)

እቅድ ማውጣት ጊዜን በአግባቡ እንድንጠቀም ከማድረጉም በላይ፤ በአንድ ጊዜ አንድ ደረጃ እየወጣን ጉዟችን አድካሚ እንዳይሆን ያደርግልናል። እቅድ ስናውጣ ነገሮች ሳይደራረቡብን ቀስ በቀስ ወደ ግባችን እንደርሳለን።

እቅድ ስናወጣ ግን እራሳችንን በሚያጨናንቅ እና ካልፈጸምነው የጥፋተኝነት ስሜት እንዲሰማን በሚያደርግ ሁኔታ ሳይሆን፤ ከጊዜያችን ፤ ከባህሪያችን እንዲሁም ከማንነታችን ጋር የሚስማማ እቅድ ነው ማውጣት አለብን። ምክንያቱም ሌላው ያቀደበት መንገድ ለኛ ላይስማማ እና ከግባችን ላያደርሰን ስለሚችል ነው።

#መርህ ሰባት:- ውሳኔ (Decision)

የሰው ልጅ ውድቀት አንደኛው መንስዔ የውሳኔ ማጣት ነው። አንድ ሰው ምንም ያህል እምቅ እውቀት ቢኖረው፤ ምንም ያህል የሚያስደንቅ ሃሳቦችን ማመንጨት ቢችልም ውሳኔ መወሰን ካልቻለ ግን አቅሙ ሁሉ ከውስጡ አይወጣም።

ውሳኔ በማጣት የተነሳ ብዙ ሙዚቃዎች ሳይሰሙ፤ ብዙ መጽሐፎች ሳይጻፉ፤ ብዙ ግኝቶች ሳይገኙ፤ ወደ መቃብር ይወርዳሉ።.በሁላችንም ውስጥ ለኛ ብቻ የተሰጠ ስጦታ አለ፤ ይህን ስጦታ ግን አውጠን ሌሎች እንዲያዩት ማድረግ የምንችለው ውሳኔ መወሰን ስንችል ብቻ ነው። የምንወስነው ምንድን ነው ካላችሁ፤ መልሱ የምንወስነው መሆን የምንፈልገውን ነው።

#መርህ ስምንት:- ጽናት (Persistence)

ውሳኔ ብቻውን አቅም የለውም። ውሳኔያችን ባህሩን አቋርጦ ከአላማችን ዳርቻ እንዲደርስ የሚያደርገው ሃይል ጽናት ነው። ብዙዎቻችን የተለያዩ ውሳኔዎችን እዚህና እዚህ እንወስናለን ነገር ግን ጽናት ኖሮን አንገፋበትም።

ለዚህ ነው ናፖሊዮን ሂል የውድቀት እና የስኬት ዋናው መለያ ጽናት ነው ያለው። ለምሳሌ ከመጠጥ ሱስ መላቀቅ የሚፈልግ ሰው መቶ ጊዜ ለማቆም ቢወስንም ከውሳኔው ጋር ጽናት ካልተደመረበት በቀር ውሳኔው ብቻውን ምንም ዋጋ የለውም። ስለዚህ በውስጣችን ያለውን የጽናት መጠን መፈተሹ እጅግ ወሳኝ ነገር ነው።

#መርህ ዘጠኝ:- ጥምር ሃይል (Power of the master mind)

“ሁለት ጭንቅላቶች አንድ ላይ ሲሆኑ ሶስተኛ ጭንቅላት ይወለዳል”። አንድ ሰው የራሱ የሆነ ሃሳብ ወይም ግኝት ሊኖረው ይችላል፤ ከሌሎች ሰዎች ሃሳብ ጋር ሲደመር ደግሞ ይበልጥ ይሰምራል።

በጋራ የመስራትን ልምድ ማዳበር መቻል አለብን። አብሮ መስራት መቻል ትልቅ ክህሎትም ጭምር ነው።

#መርህ አስር:- የምታደርገው ነገር ደስታን ሊስጠህ ይገባል– (Enthusiasm)

ስቲቭ ጆብስ በህይወት በነበረበት ወቅት እንዲህ ብሎ ነበር “የምንሰራውን ነገር የማንወደው ከሆነ እስከመጨረሻው ለመሄድ አንችልም፤ የሚሰራውን የማይወድ ማንኛውም ሰው ተስፋ ቢቆርጥ አይፈረድበትም”።

እውነት ነው የምንወደውን ነገር ስናደርግ በቀላሉ ተስፋ አንቆርጥም። ሙያችን እንዲሆን የምንመርጠው ነገር የምንወደው ነገር ከሆነ በዛ ነገር ላይ እውቀታችንን ለማዳበርም ሆነ ልምድ ለማግኘት ፍላጎት ይኖረናል።