2021-11-26 12:41:30
ይህ ወቅት ልዩነቶቻችንን ለአፍታም ቢሆን ሸሸት አድርገን በአንድ የምንሰለፍበት ጊዜ ነው። በመጎሻሸም ድል አይመጣም። በመወቃቀስ ድል አይገኝም። ለመተቻቸት፣ ለመወነጃጀል መቆምያ ያስፈልጋል። የምንቆመውም የምንኖረውም በኢትዮጵያ ነው። ሃገር ህልውናዋን እያጣች ጣት መጠቋቆም መወቃቀስ ምንድነው? ከሁሉ በፊት ሃገር ትቁም!
አድዋ ላይ ነጭን ድል ያደረግነው የውስጥ ሽኩቻዎች ሳይኖሩ ቀርተው አይደለም። በየቦታው የርስ በርስ ግጭቶች ነበሩ። የጋራ ጠላት ሲመጣ ግን ሁሉን ትተው በአንድ ቆሙ። በአንድነት ድል ነሱ! እስከዛሬ ድረስ አድዋ እያልን የምንኮራበትን፣ በነጭ ፊት የምናቀረቅርበትን ሳይሆን በክብር ቀና የምንልበትን የድል ቀን ጽፈውልን አለፉ።
ታሪክ ራሱን ይደግማል!
ከየቦታው ጦር ወደኛ እየተሰበቀ ነው። እንዴት ነው ይህን ጦር ልንጋፈጠው የምንችለው? እንዴት ነው ኢትዮጵያን እንድትቆምና የአርብ ስቃይዋን በትንሳኤዋ ልናፈካው የምንችለው? በመወቃቀስ? ጣት በመጠቋቆም? በፌዝ?
ሁሉም ልክ የሆነ ጊዜ አለው። ሁሉም በጊዜው ይጠየቅበታል። ከሁሉ በፊት ግን የሃገር ህልውና ይቀድማል!
ወደሞት እየሄድክ ስለውርስ፣ ስለገንዘብ አታነሳም። እግርህ እየተቆረጠ ስለጫማ አታስብም። ጫማ ለማድረግ እግርህ እንዳይጎዳ ከእንቅፋቶች መከላከል አለብህ! ወደድክም ጠላህም ያለሃገር መቆምያም መኖርያም የለህም!
በአንድ ሆነው መኖርያ ሃገራችንን፣ የክብር ጌጣችንን፣ ኢትዮጵያችንን ሊያጠፏት ሲመጡ በአንድ ሆነን እንመክታቸው። በመጎሻሸም ድል አይመጣም። በመወቃቀስ ድል አይገኝም።
እኛ ያለ ኢትዮጵያ ምንም ነን። ሁሉ ነገራችን የተሰፋው፣ ማንነታችንን የተሳሰረው ከኢትዮጵያ ጋር ነው። ስንቱን የጊዜ ማዕበል ተሻግራ መጥታ እኛ ጋር ስትደርስ አትፈርስም!
እኛ ኢትዮጵያዊያን ነን!
መላኩ ደምሴ!
264 viewsቢንያም ፀጋዬ 21, 09:41