2022-07-09 11:58:27
በመጠለያው ከመቆየታችን የተነሳ የተመዘገበንበትን 'ኬዝ' ረስተናል’- ኢትዮጵያውያን ስደተኞች በካኩማ
4 ሀምሌ 2022, 07:07 EAT
ተሻሽሏል ከ 1 ሰአት በፊት
በተባበሩት መንግሥታት የስደተኞች ጉዳይ ከፍተኛ ኮሚሽን (ዩኤንኤችሲአር) መረጃ መሰረት እስከ የካቲት 2021 (እአአ) ድረስ በዳደብ ስደተኞች መጠለያ ውስጥ ብቻ 224,642 እንዲሁም በካኩማ ደግሞ 206, 458 ስደተኞች ይገኛሉ።
ይህ አጠቃላይ በኬንያ የተለያዩ ከተሞች ከሚኖሩ ስደተኞች ጋር ሲደመር ከ500 ሺህ በላይ የተለያዩ አገራት ስደተኞች አሉ።
እነዚህ ስደተኞች ደግሞ ከኢትዮጵያ፣ ከሶማሊያ፣ ከደቡብ ሱዳን፣ ከዲሞክራቲክ ኮንጎ፣ ከቡሩንዲ፣ ከኤርትራ፣ ከሱዳን፣ ከኡጋንዳ፣ ከሩዋንዳ እና ከሌሎች አገራት የመጡ ናቸው።
ከግማሽ በላይ የሚሆኑት ደግሞ ከሶማሊያ የመጡ ስደተኞች ሲሆኑ፣ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች ከ29 ሺህ በላይ መሆናቸውን የድርጅቱ ሰነድ ያስረዳል።
በኬንያ ቱርካና ግዛት የሚገኘው ካኩማ የስደተኞች መጠለያ ጣቢያ የሚኖሩት አቶ ጀማል አደም እና አቶ አልዩ ኡስማን በየጊዜው በርካታ ስደተኞች ወደ ጣቢያው እንደሚመጡ ይናገራሉ።
ሁለቱ ስደተኞች ኢትዮጵያን ጥለው ከወጡ ሁለት አስርታት ሊቆጠሩ የቀራቸው ጥቂት ጊዜ ነው።
“በልጅነቴ ካኩማ ገብቼ አሁን የስድስት ልጆች አባት ነኝ” የሚሉት አቶ ጀማል የመጡት ከምሥራቅ ሐረርጌ ደደር ከተማ ነው።
በ1997 ዓ.ም ምሥራቅ ሐረርጌ ደደር ከተማ ትምህርታቸውን ከስምንተኛ ክፍል አቋርጠው ወደ ኬንያ የተሰደዱት አቶ ጀማል፣ ካኩማ የስደተኞች መጠለያ የገቡት ገና ታዳጊ እያሉ መሆኑን ያስታውሳሉ።
ከአገር የወጡበትን ምክንያትም ሲያስረዱ ‘ረብሻ አስነስታችኋል’ በሚል በመንግሥት ታጣቂዎች የተለያዩ እንግልቶች ከደረሰባቸው በኋላ፣ ያንን በመሸሽ ወደ ኬንያ መሰደዳቸውን አቶ ጀማል ይናገራሉ።
በ1995 ዓ.ም ከአገራቸው የወጡት አቶ አልዩ ኡስማን በበኩላቸው፣ ረዥም ጊዜ ከመቆየታቸው የተነሳ ለስደተኞች ድርጅት ያስመዘገቡት ጉዳይ ራሱ ምን እንደሆነ መርሳታቸውን ይናገራሉ።
አቶ ጀማል ላለፉት 17 ዓመታት በኢትዮጵያ ውስጥ ያሉ ቤተሰቦቻቸውን ሳያገኙ መቆየታቸው ያንገበግባቸዋል።
“ለረዥም ዓመታት ቤተሰቦቼ ያሉበትን ሁኔታ አላወቅም። በቅርቡ ሰዎች እዚያ አካባቢ ያለውን ሁኔታ ፌስቡክ ላይ ስለሚለጥፉ ከእነርሱ ጋር ተጻጽፌ ስለቤተሰቦቼ አንዳንድ ነገር መስማት ጀመርኩ” በማለት የቤተሰቦቻቸው ሁኔታ አሁንም እንደሚያሳስባቸው ይናገራሉ።
አክለውም “እኔ እንኳ በጥቂትም ቢሆን ቤተሰቦቼን አገኛለሁ። ሌሎች ደግሞ በጭራሽ ቤተሰቦቻቸውን ያላገኙ አሉ። እኔ አሁን እዚሁ የልጆች አባት ሆኜ ቀርቻለሁ።”
በስደተኝነት ከተመዘገቡ ከ15 ዓመት በላይ እንደሆናቸው የሚናገሩት አቶ ጀማል እስካሁን ድረስ ግን ምንም ዓይነት ነገር አለማግኘታቸውን ይናገራሉ።
“እንዲያውም የተመዘገብኩበትን ኬዝ ራሱ ረስቻለሁ። አሁን እርሱን ትቼ የግል ሥራ ጀምሬያለሁ፤ ኑሮዬን ለማስኬድ የንግድ ሥራ ውስጥ ገብቻለሁ። በራሴ ጥረት ልጆቼን እያሳደግኩ እያስተማርኳቸው ነው።”
አቶ አልዩም የተመዘገቡበትን ጉዳያቸውን [ኬዝ] መዘንጋtኣቸውን በመግለጽ፣ “የኬንያ መንግሥት ይህ ካምፕ ይዘጋል እያለ ይዝታል፤ እኛ ከፈጣሪ ውጪ ምንም የለንም፤ ጉዳያችንን የያዙ አካላትም ከእኛ ርቀዋል” ሲሉ በሐዘን ስሜት ስላሉበት የስጋት ኑሮ ይናገራሉ።
አቶ ጀማል በስደት ሕይወታቸው ያፈሯቸው ሦስት ልጆቻቸው አምስተኛ እና ስድስተኛ ክፍል ደርሰዋል “እስከቻልኩ ድረስ እኔን የገጠመኝ ዕድል ልጆቼ እንዲገጥማቸው አልፈልግም። ለዚህ ብዬ ነው ተፍ ተፍ የምለው” ይላሉ።
እርሳቸው ወደ ኬንያ ሲመጡ ባዶ እጃቸው በመሆኑ ትምህርታቸው መቀጠል አለመቻላቸውን በማስታወስ፣ “እኔ ያመለጠኝን ዕድል ልጆቼን በማስተማር ማካካስ አለብኝ” ብለው ልጆቻቸውን በርትተው ማስተማር ላይ ማተኮራቸውን ለቢቢሲ ገልፀዋል።
ሁለቱ ኢትዮጵያውያን በሚገኙበት የስደተኞች መጠለያ ጣቢያ ውስጥ ከገቡ 20 እና 30 ዓመታት የሞላቸው እንዳሉ ይነገራል።
በየጊዜው ወደ ሦስተኛ አገር እንሻገራለን የሚል ተስፋ ቢኖራቸውም ይህ ሳይሆን እዚያው ወልደው ቤተሰብ መስርተው ኑሮን ቀጥለዋል።
199 views08:58