2022-07-27 08:13:21
ያበደው ፍቅሬ
ክፍል
ትቼው ልሄድ ነው። በቃ ልሄድ ነው የመጨረሻ ውሳኔዬን ወስኛለሁ የምሄደው እንደ ሌላው ጊዜ ጥላቻንና ክህደትን ሽሽት አይደለም... ፍቅርን እንጂ።
እናም በሀሳብ እየዋዠኩ ደብዳቤ ልፅፍለት ወሰንኩ ቢያንስ ምክንያቴን ማሳወቅ አለብኝ አይደል... ደግሞ ጠፋች ብሎ ሀገር ምድሩን ነው የሚያምሰው...
መፃፍ ጀመርኩ
አንዳንዴ ልቋቋመው ከምችለው በላይ ይሆንብኛል። ፍቅርህ፣ ስስትህ፣ እንክብካቤህ፣ አንተን ትተህ ለኔ ደስታ መድከምህ፣ ከቃላት ጋጋታ ይልቅ በተግባር የምታሳየኝ መውደድህ በአጠቃላይ ሁሉም ነገርህን መቋቋም ያቅተኛል።
ሰው እንዴት ይህን ያክል ሰውን ሊወድ ይችላል እንዴትስ ሁሉ ነገሩ ፍቅር ብቻ ይሆናል ፍቅር... ፍቅር... አሁንም ፍቅር.... አንተጋ ያለው ፍቅር ብቻ ነው እኔጋ ደግሞ....
ከዚህ በላይ መቀጠል አልቻልኩም በሀሳብ ወደ ተገናኘንበት ጊዜ ጋለብኩ....
ከምናምን አመት በፊት በክህደት የተሰበረ ልቤ ላይ ትኩስ ሀዘን ተደምሮበት ግራ ቀኜን ሳላይ እግሬ ወደመራኝ ስጓዝ ሲጥጥ ብሎ እግሬ ስር የቆመ መኪና ከሀሳቤ አነቃኝ... አልደነገጥኩም እንደውም ተናደድኩ ለምን ፍሬኑን ያዘው? ለምን አልገጨኝም? ብሽቅ... የማይገኝ እድል አስመለጠኝ.... ይህን ሁሉ የማስበው ከመኪናው ወርዶ በአካባቢው ከነበሩ ሰዎች ጋር የስድብ ናዳ ሲያወርድብኝ ነው። "ያምሻል.... እያዬሽ አትሄጂም..... መሀል አስፓልት ላይ ምን ትሰሪያለሽ...... እብድ ነሽ..... ጦስ ውስጥ ከታው ነበር........." አይገርምም አንድ እንኳን ችግሬን ለማወቅ የፈለገ ምን ሆና መሀል አስፓልት ላይ ተገኘች ያለ ሰው የለም.... አስመሳይ ብቻ።
እጄን ይዘው ወደዳር ወስደውኝ የጀመሩትን ስድብ ያዘንቡብኝ ጀመር... ለትንሽ ሰከንድ አየሁዋቸው... ሳላስበው ቃል ከአፌ ወጣ 'ዞር በሉልኝ አስመሳዮች' ያልኳቸው አላስደነገጠኝም ምክንያቱም ይሉኝታም ሆነ ሀፍረት ከኔ በእጥፍ እርቀዋል... ይሉኝታ የተሰጠው ለሰው ነው እኔ ደግሞ ከሰውነት ደረጃ በትንሹ ወርጃለው..... ምናልባትም እንደማስበው አልወረድኩ ይሆናል ግን በቃ ለኔ የሚሰማኝ ያ ነው......
በበረሀ ላይ ያለ እህል ውሀ የተጣልኩ..... ሙቀት ሀሩሩ ያነደደኝ..... ከአካላቴ አብዛኛውን በከሀዲዎች የተነጠኩ.... ለመኖር ተስፋ ለመሞት አቅምና ወኔ የሌላት ፍጡር እንደሆንኩ ይሰማኛል። አዎ ለመሞትም እኮ አቅም እና ወኔ ያስፈልጋል.... ወኔ ቢኖረኝማ ይህን ጊዜ ሙት አመቴ አልፎ ነበር።
ስልችት፣ ድክም፣ ልፍስፍስ እላለሁ...
ማሰብ ያደክመኛል...
መብላት መጠጣት ይሰለቸኛል...
ስሜን ጠርተውኝ እንኳን 'አቤት' ማለት ትልቅ ተራራን የመግፋት ያክል ይሆንብኛል።
የልብ ስብራት ብቻ ሳይሆን ከአካል ክፍሎቼ እያንዳንዳቸው ስብርብር እንክትክት እንዳሉ ይሰማኛል። በቃ ዝምምምም ብሎ መኖር ከነኝህ ጊዜያቶች በአንዱ ነው እንግዲህ ከዚህ ሰው ጋር የተገናኘሁት....
በቆሙበት ትቻቸው እየሄድኩ ነው ከኋላዬ የራቀ ድምፃቸው ይሰማኛል..." ያማታል መ ሰ ለ ኝ..." እኔ ግን እየሄድኩ ነው... ከቤት ስወጣ ማንም ያየኝ የለም ለነገሩ ማን ሊያየኝ ይችላል... እንደሚሰበር እንቁላል የሚንከባከቡኝን ሁሉ አጥቻለው..... እየሄድኩ ነው....መነሻዬን አስታውሳለሁ መድረሻዬን ግን እንጃ.....
ይቀጥላል....
✎ ክፍል 2 ይቀጥላል.... ቶሎ እንዲቀጥል አንብበው ሲጨርሱ Like ማድረግ አይርሱ።
━━━━━━━━ ✦
@amharicquets
@amharicquets
68 views05:13