2022-07-18 21:04:00
ፈዳኢል...
(በTeam Huda)
(ክፍል ሀያ ስድስት)
.
ዙህርን አልፋሩቅ መስጂድ ከሰገድን በኋላ ወጥተን ቁርዐኖቹን ገዝተን ተመለስን። ለአስተባባሪዎቹ ሰጥተናቸው ዱዐ እንዲያደርጉልን ከጠየኳቸው በኋላ ከመስጂዱ ወጥተን ወደ ምሳ አመራን። ራቢ የላኩላትን መልዕክት አንብባ በጣም ተደስታለች.... መደሰቷ የኔን ደስታ እጥፍ አድርጎታል። ምሳ ከበላን በኋላ ከ2 ቀን በኋላ ትኬት የማገኝበትን ሁኔታ በስልኬ ማፈላለግ ጀመርኩ።
"እሺ.... እና ቀጣይስ ወዴት ነው?" ጋሼ ነበሩ።
"ምኑ?"
"ሃሃህ ዛሬ ቀልብህ የለም.... ጉዞአችን ነዋ።"
"እእእ... ወደ ገርጂ እንሂድ። እዛ አንድ የምንሰጠው ሰው አለ.... በዛውም በጊዜ ወደ ሆቴል ልመለስና እቃዎቼን ላዘገጃጅ፤ ለዛሬ 2 ቀን የአየር ቲኬት አግኝቻለሁ።"
"ላንተ? ቀንህ ደረሰ እንዴ?.... 10 ቀን መች ሞላን?" በእጃቸው ያሳለፍነውን ቀን መቁጠር ጀመሩ።
"አይ ሳይሆን እኔ ስለቸኮልኩ ነው ጋሼ.."
"ጥሩ እሺ ካልክ.... በቃ እንሂድ በጊዜ" ወደ መኪናው ቀደሙኝ።
*
ዐስር ከመድረሱ በፊት ወደ ገርጂ ደረስን፤ ያሰብኩትን ያህል ቅርብ አልነበረም። ወደ አድራሻው ደርሰን ከመኪናው ወረድኩ፤ ጋሼ እዛው እንደሚጠብቁን ነገሩኝ። ቤቷ ትንሽዬ የቀበሌ የመሰለች ቤት ናት።
"ማኑ?" ከቤቱ ውስጥ የሰማነው የትንሽ ልጅ ድምፅ ነበር።
"አሰላሙ ዐለይኩም... ወ/ሮ ኸዲጃን ፈልገን ነበር" መልስኩላቸው። ለዲቃዎች ምንም ድምፅ ሳንሰማ ከቆምን በኋላ አንዲት ትንሽዬ ልጅ በሩን ከፈተችልን። ለንፃት የረበ ቅላትና ፀጉሯ ለስላሳ ከመሆኑ ኢትዮዺያዊ አትመስልም።
"ኡሚ አሊች.... ምን ፈልገህ ኑ?" በሚኮላተፍ አፏ ጠየቀችኝ።
"ጥሪያት አንዴ.... መልዕክት ሊሰጥሽ ነው በያት"
"ምድኑ ምልክት?.... ኡሚ ሰገደች ኑ ዐስር። ለኔ በል..." ባለችነት ቆመች። ምን ብዬ እንደማስረዳት ግራ ገባኝ። እዛው እንደቆምኩ እናቷ ሰግዳ ጨርሳ አንድ አነስ ያለ ፀጉሩ ግምባሩ ላይ የተደፋ ወንድ ልጅ አቅፋ መጣች። ፊቷ በኒቃብ ተሸፍኗል... ቢሆንም የሌላ ሃገር ዜጎች መሆናቸውን ለማረጋገጥ በቂ ነበር።
"አፍወን.... ኸዲጃ ነሽ? ራቢያ ሱልጣን ልካኝ ነበር የመጣሁት..." ትረዳኝ አትረዳኝ ባላውቅም ዝም ብዬ ነገርኳት። ወደ ልጇ ጎምበስ አለች.... በአረብኛ ታዋራት ጀመር፤ ሲመስለኝ እየተረጎመችላት ነው። ሃዲሶችና ቁርዐንን ለመረዳትና መፅሃፎችን ለማንበብ የሚያበቃ የአረብኛ እውቀት ቢኖረኝም የነሱን ፈጣን ንግግር መልቀም ግን ከባድ ነበር።
" 'ማኑ ራቢያ?' አለችህ ኡሚ" ልጅቷ መለሰችለኝ። በዚህ አይነት እንዴት እንደምንግባባ ግራ ስለገባኝ ለራቢ ደወልኩላት። ኢሞ እንድገባ ነገረችኝና በቪድዮ ኮል አገናኘኋቸው። ራቢ ስታዋራት የኸዲጃ ድምድ የለቅሶ ሲቃ ይዞ ሲቀየር ይደመጥ ነበር። ምን እየተባባሉ እንደሆነ ለማወቅ ብችል ተመኘሁ። ራቢ አዋርታት ስትጨርስ ፖስታውን እንድሰጣት አዘዘችኝ፤ ስልኩን ወደ ኪሴ ከመለስኩ በኋላ አውጥቼ ሰጠኋት። ከኒቃቧ ስር እንባዋን እየጠረገች ተቀበለችኝ። ቀጥላም እየመረቀችን ልጇን ወደኔ ስትጠቁማት አየኋት።
" 'ጀዛከላህ በሊው' አለች ኻሎ.... 'ምንም አልንብረም... ብዙ ማታ አልቅስኩ... አንተ መጣህ... አልሃምዱሊላህ' ትላሊች" ልጅቷ በሚሰባበር አማርኛ የእናቷን ንግግር ልታስረዳኝ እየጣረች። " 'አላህ ሀብታም አያርግህ... ደሞ በኋላ ምንም የሌለው አያርግህ...' " መተርጎሟን ቀጠለች።
"ከየት ሀገር ናቹ?" ስትጨርስ ጠብቄ ጠየኳት።
"ሱሪያ.... ባለፈው ለት 2 አመት መጣን እዚ። ባባ አላይርሃሙ ቀረ ሱሪያ" ክፍት ሲላት ተመለከትኳት፤ አሳዘነችኝ። የተቀረውን ታሪክ ሳልጠይቃት በራሴ ግምት ሞላሁት።
"ደብዳቤ ታውቂያለሽ?.... ወረቀት? ኦ ሪሳላ! ብሩ ጋር ሪሳላ አለው በያት..." ንግግሬን እንደሰማች ነገረቻት። ፖስታውን ከፍታ መመልከት ስትጀምር እንደተረዳችኝ ገባኝ። ከፍታው አውጥታ ማንበብ ጀመረች.... በድጋሚ አስለቀሳት። በድጋሚ ለልጇ ወደኔ ጠቆመቻት...
" 'አላህ ሀገራቹ ያቁያቹ.... ሰላም ያርጋቹ። ኢንሻአላህ ለይል ቁሚ ዱዐ አረጋሉ... እምም... ረመዳንም ሸዋልም ሶም አላ-ይባሪክፊህ አሊች' "
"ሃሃህ አሚን። ኡሚን አንዴ ስጪኝ በያት..."
"ሪሳላ?"
"አዎ...ሃሃህ" ወደ እናቷ መለስ ብላ ከጇ ተቀበልላ ሰጠችኝ። በአረብኛ ነበር የተፃፈው.... በአማርኛ እንደተረዳሁት ከሆነ እንዲህ ይላል...
.
<<አሰላሙ ዐለይኪ እህቴ ኸዲጃ.... መናልና ዐምር እንዴት ናቸው? ወላህ ናፍቀቹኛል። አይዞሽ ሶብሪ የአላህ ፈረጃ ቅርብ ነው.... ወደ ሃገራቹ በሰላም የምትመለሱበት ያድርግላቹ። ረመዳን በሰው ሃገር የራስን ሃገር ያህል እንደማይሞላ ይገባኛል፤ ቢሆንም ከዒባዳ ሳትዘናጊ ታትረሽ ጨርሺው። ከቻልሽ የሸዋልንም 6 ቀናት ጨምረሽ ፁሚው። የአላህ መልዕክተኛ {ሰ.ዐ.ወ} እንዲህ ብለዋል:- <ረመዷንን የፆመና እርሱን አስከትሎም ከሸዋል ወር ውስጥ ስድስት ቀናትን ያከለ ዓመቱን ሙሉ እንደ ፆመ ይቆጠርለታል>። አቡ ዐምር በጀነት እንዲጠብቅሽ ዱዐ አደርጊለት፤ አላህ ከሷሊህና ዐቢድ ባሪያዎቹ ይሰማል። በቻልሽው መጠን ቋንቋ ለመልመድ ሞክሪ፤ እነመናልም እንዲለምዱ አድርጊያቸው። በዚህ ረመዳን ከሙስሊሞች ጋር ይበልጥ ተቀላቀይ፤ ሙስሊም የሙስሊም ወንድሙ አይደል? ከየትም ሃገር ቢሆን አይተዉሽም። በማብሰል ሙያሽ ስራ የምታገኚበት እንዲሆን ዱዐ አድርጊ፤ ሰበቡን አድርሺ። ልመናሽን ወደ አላህ ብቻ መልሺው.... ምላሹ ቅርብ ይሆናል ኢንሻአላህ። መጥቼ እስካያቹ ድረስ ለኔም ለሙስዐብም ዱዐ አድርጊልን። ወሰላሙ ዐለይኪ ወራህመቱላሂ ወበረካቱህ።>> የመልክቱ ማብቂያ ነበር። ወረቀቱን መለስኩላት፤ በድጋሚ ከመረቀችን በኋላ ወንዱን ልጇን እንዳቀፈች ወደ ውስጥ ገባች። ልንሄድ ስንል መናል ከኋላዬ ተከትላኝ ስትጠራኝ ሰማኋት፤ ተመልሼ በሷ ቁመት በርከክ ብዬ አዳምጣት ጀመር።
"ኻሎ.... ንዳንተ መሆን ፈልጋሉ.... ባባ ሰደቃት ይሰጣል... አንተም ይሰጣል... ኒም መስጠት ፈልጋሉ ረቡናስ ወ ኡሚ ደስ እንዲሉ" ጥያቄዋ አንጀት የሚበላ ነበር። ምን እንደምላት ግራ ገብቶኝ ጥቂት ካሰብኩ በኋላ ባለፈው ከዳዕዋዎቹ አንዱ ላይ የሰማሁት ሃዲስ ትዝ አለኝ።
"ትቺያለሽ.... ዚክር አድርጊ። ዚክር ታውቂያለሽ?... ተስቢሕ (ሱብሐነላህ)፣ ተሕሚድ (አልሃምዱሊላህ)፣ ተሕሊል (ላ ኢላሀ ኢለ ላህ)ና ተክቢር (አላሁ አክበር).... ሁሉም ሰደቃ ናቸው ብለዋል ነቢና ሙሃመድ {ሰ.ዐ.ወ}። እንደ ኡሚ ሁኚ.... እሷ ተህሚድ ስታደርግ ሰማሻት አይደል? አላህ በጣም ይወዳታል! በጣም ብዙ ብዙ ዚክር ስትዪ ጀነት ውስጥ ብዙ ብዙ ዛፍ ይኖርሻል። ዛፍ ታውቂያለሽ?"
"አዉ.." ጭንቅላቷን ላይና ታች እየነቀነች።
"ማሻአላህ ጀነት ውስጥ ትልቅ ቡስታን ያለሽ ልዕልት ትሆኛለሽ። ጀነት የሚገባው ደግሞ ኡሚን የማያናድድ ነው። ተስማማን?" በድጋሚ ጭቅላቷን ነቀነቀችለኝ። "እምም... አሁን ኡሚን አስፈቅጃትና እሺ ካለች ብስኩት ገዝተን እንመጣለን ጠይብ?" እጄን ዘረጋሁላት።
"ጠይብ" መስማማቷን ለመግለፅ እየሳቀች እጄን መትታኝ ወደ ቤቷ ሮጠች። እስክተመለስ ቦታው ላይ ያሉትን ዛፎች እየተመለከትኩ መጠበቅ ጀመርኩ፤ ሳይታወቀኝ በሰደቀችኝ ፈገግታ እኔም ፈገግ እያልኩ ነበር።
.
.
ይቀጥላል...
@wub_Tarikoch
@wub_Tarikoch
601 views18:04