በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል 114 ኢንቨስተሮች 2 ቢሊዬን ብር ብድር ወስደው ወደ ስራ ሳይገቡ መቅረታቸው ተገለጸ።
በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል 114 ኢንቨስተሮች ከልማት ባንክ 2 ቢሊዬን ብር ብድር ወስደው ወደ ስራ ሳይገቡ መሸሻቸውን የክልሉ ገጠር መሬት አስተዳደርና ኢንቨስትመንት ቢሮ አስታወቀ፡፡
በክልሉ በአሁኑ ጊዜ 9 መቶ የሚደርሱ ባለሀብቶች በተለያዩ ስራ ዘርፎች ተሰማርተው እንደሚገኙ የገለጹት የቢሮው ኃላፊ አቶ አመንቴ ገሺ ከእነዚህ ባለሀብቶች መካከል 114 የሚደርሱት ከልማት ባንክ ብድር ወስድው ወደ ስራ ሳይገቡ መቆየታቸውን አብራርተዋል፡፡
ባለሀብቶቹ ወደ ስራ ባለመግታቸውና መሬቱ ባለመልማቱ የክልሉ መንግስት በሚሊዩን የሚቆጠር ገንዘብ የመሬት ግብር ማጣቱንም ኃላፊው ተናግረዋል፡፡
በክልሉ ከዚህ ቀደም በኢንቨስትመንት ስራ የተሰማሩ እና መሬት አስይዘው ያላለሙ እና ለተገቢው ዓላማ ላይ ያላዋሉ ባለሀብቶችን የማጥራት ስራ እንደሚሰራም ቢሮው አመልክተዋል፡፡
በሌላ በኩል የጸጥታ ችግር በሌለባቸው የክልሉ ስፍራዎች በማዕድን ዘርፍ የተሻለ ምርት መገኘቱን ገልጸዋል፡፡ 22 ኩንታል ወርቅ እስካሁን ወደ ብሔራዊ ባንክ መግባቱንም አክለዋል፡፡
በክልሉ ወርቅ፣ ድንጋይ ከሰል፣ መዳብ፣ እምነበረድ፣ እጣን ምርትና 12 ዓይነት የማዕድነት ሀብቶች እንደሚገኙ የገለጹት ኃላፊው በማዕድኑ ዘርፍ በርካታ ወጣቶች መሰማራታቸውን ገልጸው 10 የተደራጁ ማህበራት ደግሞ በቅርብ በክልሉ በእርሻ ኢንቨስትመንት መሰማራታቸውን ጠቅሰዋል።
የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አሻድሊ ሐሰን በክልሉ ምክር ቤት 13ኛ መደበኛ ጉባኤ ላይ በሰጡት ማብራሪያ በባህላዊ የወርቅ አምራቾች በኩል ከ1ሺ ኪ.ግ በላይ ወደ ብሔራዊ ባንክ መግባቱን መግለጻቸው ይታወሳል። (DW Amharic)
@tikvahethmagazine