Get Mystery Box with random crypto!

#Wolaita ' መምህራኑ በተራበ አንጀት አንሰራም በማለት ስራ አቁመዋል ' -  የደቡብ ኢት | TIKVAH-ETHIOPIA

#Wolaita

" መምህራኑ በተራበ አንጀት አንሰራም በማለት ስራ አቁመዋል " -  የደቡብ ኢትዮጵያ መምህራን ማህበር

" መምህራኑ ወደስራ ያለተመለሱት የሙያ ማረጋገጫ ፈተና ላይ በመሆናቸዉ ነው " - የወላይታ ዞን ትምህርት መምሪያ

ከሰሞኑ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ወላይታ ዞን በተለያዩ ወረዳዎች መምህራን ከደሞዝ ጋር በተያያዘ ስራ ማቆማቸው ተነግሯል።

መምህራኑ በተለያየ ጊዜ ደሞዝ ሲዘገይና ሲቆራረጥ መቆየቱ ለስራቸው እንቅፋት ለህይወታቸውም አደጋ መሆኑን በመግለጽ ለሚመለከታቸዉ አካላት በተለያየ መልኩ ለመግለጽ ሲሞክሩ መቆየታቸውን ይገልፃሉ።

ከነዚህ መምህራን ውስጥ አንዱ የሆኑት መምህር አሸብር ፤ እርሳቸዉና በዳሞት ገሌ ወረዳ ያሉ መምህራን በደሞዝ መቆራረጥና የእርከን ጭማሪ እጦት ምክኒያት ምሬት ውስጥ እንደገቡ ለቲክቫህ ኢትዮጵያ ተናግረዋል።

በተደጋጋሚ የግማሽ ወር ደሞዝ ሲወስዱ መቆየታቸዉን የሚገልጹት መምህር አሸብር አሁን ላይ ጉዳዩ ለመምህራን በህይወት የመኖርና ያለመኖር መሆኑን ገልጸዋል።

የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የመምህራን ማህበር ፕሬዚዳንቱ አቶ አማኑኤል ጳውሎስ ለቲክቫህ ኢትዮጵያ በሰጡት ቃል በተደጋጋሚ " ችግሩ ይቀረፍ " በማለት በደብዳቤም ሆነ በውይይት ባለስልጣናትን ስናናግር ቆይተናል ብለዋል።

ጉዳዩ ስር የሰደደና የቆየ መሆኑን ገልጸው አሁን ላይ መምህራኑ " በተራበ አንጀታችን መስራት አልችልም " በሚል ስራ ማቆማቸዉን ገልጸዋል።

መምህራን በፐርሰንት እየተቆራረጠ የሚከፈላቸዉ ደሞዝ በዚህ ወር ለ16 ቀን መዘግየቱን ተከትሎ ስራ እንዳቆሙ አስረድተዋል።

" ችግሩ ከደሞዝም በላይ የሌሎች ጥቅማጥቅሞች ማለትም የወዝፍ ደሞዝ ፣ ከደረጃ እድገት ጋር ተያይዞ የሚመጣ የደሞዝ ጭማሪና የእርከን እድገት መቅረት ፈተና ሆኖባቸዋል " ብለዋል።

በሌላ በኩል አሁን ላይ እንደ ሶዶ ባሉ ከተሞች ብቻ ደሞዝ መከፈሉ ወረዳ ላይ ካሉ መምህራን በላይ የገጠር ተማሪ ወላጆችን ልጆቻችን በዚህ ምክኒያት ከትምህርት ራቁ በሚል እያናደደ መሆኑን በመግለጽ ይህን አሳሳቢ ችግር የዞኑም ሆነ የክልሉ መንግስት በአፋጣኝ ሊቀርፈዉ እንደሚገባ አቶ አማኑኤል ጳውሎስ አሳስበዋል።

ቲክቫህ ኢትዮጵያ የመምህራኑን ቅሬታ ተከትሎ ምላሽ እንዲሰጡ የወላይታ ዞን ትምህርት መምሪያ ሀላፊዉ አቶ ታደሰ ኩማን አነጋግሯል።

እሳቸውም ፤ " ነገሩ እንደሚባለዉ ሳይሆን ክፍያዉ የዘገየዉ በ8 መዋቅሮች ብቻ ነው " ብለዋል።

" አሁን ላይ ደሞዙ በመከፈሉ ችግሩ ተቀርፏል " ሲሉ ገልጸዋል።

ለቀናት የዘገየዉ ደሞዝ ከተከፈለ በኋላ መምህራን በአመጽ ሳይሆን በነበረባቸዉ የሙያ ማረጋገጫ ፈተና ምክኒያት ወደስራ አለመግባታቸውን አስረድተዋል።

ከዚህ ዉጭ አንዴ ብቻ በተፈጠረ የደሞዝ እጥረት ለአንድ ወረዳ ብቻ ስልሳ ፐርሰንት እንደተከፈለ በመግለጽ ከዛ ውጭ ምንም አይነት የደሞዝም ሆነ የጥቅማጥቅም ችግር እንደሌለ ምላሽ ሰጥተዋል።

#TikvahEthiopiaFamilyHawassa

@tikvahethiopia