Get Mystery Box with random crypto!

' ኢትዮጵያዊ ነኝ' ኑሮ ቢገፋኝ ፥ የማልወድቅለት እንዳክሱም ድንጋይ ፥ እንደ ሮሐ አለት የግዜ | ቅዱስ ድልድይ/kidus bridge

" ኢትዮጵያዊ ነኝ"

ኑሮ ቢገፋኝ ፥ የማልወድቅለት
እንዳክሱም ድንጋይ ፥ እንደ ሮሐ አለት
የግዜ ሞገድ ፥ ያላደቀቀኝ
የመከራ ዶፍ ፥ ያልነቀነቀኝ
ለሙሾ ሲያጩኝ ፥ ቅኔ የምቀኝ
በግራ ሲሉኝ ፥ የምገኝ በቀኝ
ኢትዮጵያዊ ነኝ፤

ከዋርካ ባጥር ፥ ከምቧይ ተልቄ
ከፀሐይ ባንስም ፥ ከኩራዝ ልቄ
ተምድረ በዳ ፥ ጅረት አፍልቄ
ጥሜን የምቆርጥ ፥ በፍኝ ጠልቄ
ኢትዮጵያዊ ነኝ፤

ግትር ጠላቴን ፥ ባጭር አንካሴ
ራስ ምታቴን ፥ በዳማከሴ
ነቅየ ምጥል
ነገር በነገር ፥ የማብጠለጥል
ለወዳጆቼ ፥ ዓደይ ምነቅል
በጠላቴ ፊት ፥ ቀንድ የማበቅል
ልክ እንደዋልያ ፥ ተራራ መራጭ
ልክ እንዳሞራ ፥ ብርንዶ ቆራጭ
ኢትዮጵያዊ ነኝ

እንደመሀረብ ፥ ቤቴን በኪሴ
እንደንቅሳት ፥ ተስፋን በጥርሴ
ይዤ የምዞር ከቦታ ቦታ
በዘብ በኬላ የማልገታ
ኢትዮጵያዊ ነኝ።

ገጣሚ:-በውቀቱ ስዩም