2021-11-05 10:39:35
የአርማሽ መንታ ስሜት
በኤርምያስ ደባሱ
" እኔማ አለሁ እስከ አሁን ተስፋ ሰንቄ ፣
በወንዜ ባገሬ እያለሁ ሀገር ናፍቄ "
እያለ በሚያዜማት ስንኙ የሀገሬን ሰዉ ባይተዋር ሀገር ናፋቂ ልብ ይነካካል ። ሀገር እያለ ወንድማማችነት እንደ ዘሐ ክር እየቀጠነ መጥቷል ፤ ከብረት የጠነከረዉ ኢትዮጵያዊ አንድነት ዉኃ እንዳራሰዉ ልጥ ተዉሸክሽኳል "በወንዜ ባገሬ እያለሁ ሀገር ናፍቄ "የማይል ኢትዮጵያዊ የለም ። ሀገር ኖሮን ሀገር የለንም ባይተዋር ሆነናል ።
የኢትዮጵያዊነት ኩራት የሆነዉ መተሳሰብ ፣ አብሮነቱ ፣ ስንት የተወራለት እንግዳ ተቀባይ ባህላችን እንደ ማለዳ ጤዛ ተኗል ። በኗል ! አሁን ላይ እንግዳ መቀበሉ ቀርቶብናል እንግዳ ተቀባይ የነበርነዉም ዛሬ ለራሳችን ስደተኛ ሆነናል ።
" እኔስ እስካይሽ ጨነቀኝ ፣
ሀገሬ መምጫሽ ናፈቀኝ ።"
ያች የፍትሕ ና የርዕት ሀገር የተባለላት ኢትዮጵያ መምጫዋን ናፋቂወች ሆነናል ።
ጥበብ ገሀዱ አለም ናት ! ቴወድሮስ ካሳሁን (ቴዲ አፍሮ ) ይህንን ገሀድ የወጣ አለማችንን በጥበበኛ ብዕሩ ከትቦ በስል አንደበቱ አዚሞ
" ቀን እየሔደ ቀን መጣ ፣
ልቤ ከሀሳብ ሳይወጣ ።
መጥታ ታብሰዉ እንባየን፣
ሀገሬን ጥሯት አርማዬን ። " እያለ ልብ ድረስ ዘልቆ ይደመጣል ።
በያሬድ ተፈራ የሳክስፎን ረቂቅ ዜማ እያዋዛ ከዉሃ በጠራ ድምፁ
"መቼም ከዚህ ምድር ላይ
ሔዶ ነዉ ሁሉም ቀሪ ፣
አገር ናት ቋሚ ሰንደቅ ለዘላለም ኗሪ ። "ሲል በሚስብ ዜማዉ አቆነጃጅቶ የሁሉንም አላፊ ጠፊነት ምስጢር ይገልፅበታል ።
እኔማማማማ....!!! እያለ በረጅሙ እስትንፋሱን ሳብ አድርጎ ከረጅሙ የሀገር ፍቅር የመነጨዉን ምኞት ያወሳበታል ።
"እኔማ ላይሽ በቶሎ ምኞት ነበረኝ ፣
ግን ባባሁ ናፈኩሽና እንባ ቀደመኝ ።" ቴዲ አፍሮ እንዳለዉም የናፈቃትን ሀገሩ ሲያስታዉስ በሰቀቀን እንባዉ የማይቀድመዉ የለም ። የሀገር ፍቅሩ በእንባ የሚተናነቀዉ ሰዉ የሚመሰክረዉ ሃቅ መሆኑ ነዉ ።
"ወጥተሽ በምስራቅ አንች የአለም ጀምበር ፣
አንድ አርጊንና ጠላትሽ ይፈር ።"በሚላት ስንኙ የምስራቅ አፍሪካዋ ኢትዮጵያ በድል አድራጊነቷን ጠላት አሳፋሪ መሆኗንም ያወሳልበታል ።
ያሬድ ተፈራ በሚራቀቅበት ሳክስፎን በረከት ተስፋዚንም በሊድ ጊታሩ እየተጠበበ በሚያጅበዉ የቴወድሮስ ካሳሁን አሸወይ ድምፅ
"ሀገር ለክብሩ ሲጣራ
ከፍ ያደረግነዉ ባንዲራ
ዘመም ሳይል ቀን ጎድሎ
ባክሽ ኢትዮጵያ ነይ ቶሎ "እያለ ኢትዩጵያን ዉዷን ሀገሩ በሰዉኛ ዘይቤ ያናግራታል ። ዉዷ ሀገሩ ግን አልመለሰችም አሁን ገናናት ቀን ጎድሎባታል ባንዲራዋም ዘመም ብሏልና !
"........ አገር የሞተ 'ለት ወዴት ይዴት ይደረሳል ?"እንዲል ባለ ሀገር ቴዲም
"የአርበኞች የድል ችቦ ለትዉልድ እንዳበራ
መኖር ላገር ሲሆን ሞትም አያስፈራ "ይላል ።
ሰርጌና ሞቴ በሀገሬ ይሏል ይህ ነዉ በአገር ሲኖር ሰላም በንግስናዉ ማማ ሲከብር ሞትም ሰርግነዉ ። ቴዲ ይህንኑ በዜማ እያዳወረ ይነግረናል ።
" አመት አወደ አመት ድገመን ሲሉ
ልጆች በቀየዉ ችቦ እያበሩ
መስቀል ፋሲካዉ ዒድ እንቁጣጣሽ
አዉደ አመት አይሆን አንች ካልመጣሽ " የሚልላትን በእናት የምትመሰል ሀገሩ በተመጠነ ግጥምና ዜማዉ እያሽሞናሞነ ሁኚ መስከረም ያሰኘናል ።
ወርኀ መስከረም አዲሱን ዘመን በተስፋ ብርሀን እንደምታፈካዉ ሁሉ ቴዲም
" ዘመን አድሰሽ በፍቅር ቀለም
ብቅ በይ ኢትዮጵያ ሁኝና መስከረም " በሚል ጣፋጭ ስንኙ ያዋቀራት ለጆሮ በሚጣፍጥ ቃና ሲዜም የመስከረምን ፅዱልነት ያጎናፅፋል ።
ሙዚቃ ከተባለ አይቀር ይሔ ነዉ !!
"እንበል አሲዮ ....አሲዮ
ናና ቤሌማ .....ቤሌማ
ብቅ በይና ሆነሽ ሙሽራ
ይብቃን ስደቱ ይብቃን መከራ "
እያሰኘ አጥንት የሚሰረስር ብሶትን በሚነካካ ዜማዉ
"እኛስ ከመንገድ ላይ ጠፍተን መች አወቅነዉ
ብንሔድ ብንሔድ አንደርስም ገና ነዉ በማባረኪያችን ከመንገድ ላይ ዝለን
አይበቃም ወይ ማሳል በዘር ጉንፋን ታመን "
ሲልም ያክልበታል ፤ በል ሲለዉ ግን አዬደለም
" የጀግኖቹ ልጅ አንተ ነህና
ከገር ወዲያ ሞት ሞት የለምና " ብሎ ማለቱ
" ሰዉ በሀገሩ ወይራ ነዉ " ነገር ግን ከሀገር ወዲያ ሞት ሞት የለም እንኳንስ ወይራ ይቅርና ልጥም ሲደላ ነዉ "ባገሬ እያለሁ ሀገር ናፍቄ !!"ይሆናልና ነገሩ ።
ሆኖም ግን
"ዝም ያለ መስሎ ኢትዮጵያዊነት
ማንም አይገታዉ የተነሳ ለት " ያለዉም ሌላዉ እዉነታ ነዉ ። የተነሳለት የማይገታዉ ኢትዮጵያዊነት ቀና ማለቱም የማይዘነጋ ነዉ
" ቀና በል አሁን
ቀና በል ቀና " መባሉም ለዚህ ነዉ ።
" ብዙ ነሽ አንች ሀገሬ የሞላብሽ ታምራት
ምኩራብሽ የተፈራ የነፃነት ቤት " የሚላት ሀገሩን ታሪኳን ከዜማ ጋር ድርና ማግ አድርጎ
"ትናንት እንደ ጀምበር እያዩት ከአይን ይርቃል
ኢትዮጵያ እንድትመጭ ስንት ቀን ይበቃል ?"
ሲልም ይጠይቃል ።
" ኢትዮጵያ እንድትመጭ ስንት ቀን ይበቃል " ግን የኢትዮጵያ መምጫ መቼ ይሆን ? ከመፅሐፍ ቅዱስ እስከ ቁርዓን ስሟ የሚጠራዉ "ኢትዮጵያ " መምጫዋ የራቀ አይመስልም ።
"ኢትዮጵያዊነት ቀን አለዉ ገና
ስምሽን በክፋ ያነሳሽ ጠፍቶ
አርማሽ ከፍ ሲል ሰማይ ላይ ወጥቶ
እኛ ልጆችሽ ልናይ ቆመናል
አንድ ቀን መጥቶ አንድ ያደርገናል "ሲል ሃቁን ነዉ አንድ ቀን የኢትዮጵያ ትንሳኤ የማይቀርበት ቀን አለ !!
ስንቱ ተሰደደ ይብቃን ሐዘን ለቅሶ
አንድ ሆነሽ ኢትዮጵያ ባየን ፍቅር ነግሦ " ሲል የተመኘዉ ፍቅርም መንገሱ የማይቀር ነዉ ።
ቴወድሮስ ካሳሁን "አርማሽ ከፍ !!ይበል " ያላት ኢትዮጵያ ከፍፍፍ ብላ የምትታይበት ቀን የራቀ ቢመስልም ቅርብ ነዉ
"ዘር ያበቀለዉ ታጭዷል መከራዉ የኢትዮጵያዊነት አሁን ነዉ ተራዉ "ማለቱም ለዚህ ይመስላል ።
በቅዱሱ መፅሐፍ "ነብር ዥንጉርጉርነቱን ኢትዮጵያዊ ኢትዮጵያዊነቱን አይለዉጥም "እንደተባለዉ ኢትዮጵዊነት ትናንትም ዛሬም ነገም የማይቀየር ነዉ ለዚህም ደግሞ
"ጥንት አባቶችህ ያቆዩህን
ከፍ አርገህ ይዘህ ባንዲራህን
ቀና በል አሁን !" ሲል ያስታዉሳል ፤ ያነሳሳል ፤
እንደ አድናቆት ይቆጠርልኝ ዘንድ እንዲህ ስል ስንኝ ልቋጥርለት
" እንደ ማር ወለላ ምላስ ላይ ይጥማል ፣
እንደ ቀዝቃዛ ዉሃ ጉሮሮን ያርሳል ፣
እንደ ወዳጅ ከንፈር ልብ ያረሰርሳል ፣
ልብ ድረስ ዘልቆ እንደ ደም ይረጫል ፣
ጆሯችንንማ መቼም አክሞታል ።
ለዛሬ ፅሁፌን በዚህ ቋጨሁ !!!
የምትሉኝን ለመቀበል @Ermiasdebassu የሚለዉን መስመር ከወራሪ ሀይል ነፃ አድርጌ አጥብቃችሁ አለሁ ።
ሌላም ሰፊ መንገድ ከሻታችሁ ወደ እዚህ ቤት አባወራ ዝለቁ ፦ በጓዳ @GazetawBot ላይ
ለእኔ ለአባወራው @Tamen1234 እያላችሁ ላኩልኝ።
የቤታችንን በር @Gazetaw አንኳኩ፤ክፍት ናት
114 viewsErmias Debasu, 07:39