2022-08-28 20:31:21
++ ኪነጥበብ - የመስቀል በዓል ድራማ !
( ርዕስ - መስቀሉን ፍለጋ )
#ትዕይንት_አንድ
(ትዕይንቱ ሲጀምር ንጉስ ቆስጠንጢኖስ ከአሽከሮቹ ጋር ይታያል)
ንጉስ ቆስጠንጢኖስ ፦ (ከመቀመጫው ተነስቶ) ተመስገን አምላኬ ተመስገን ያኔ በቤዛንቲን ነግሼ ሳለ የመክስምያኖስንና የዲዮቅልጢያኖስ አረመኔነትና ጭካኔ ስሰማ እጅግ አዝን ነበር። ነገር ግን በእግዚአብሔር እርዳታ እነሱን ድል ገዝቼ እነሆ በቆስጠንጥኒያ ነገስኩ ተመስገን ተመስገን አምላኬ፤ አንተ ማነህ አሽከር.... !
አሽከር ፩ ፦ አቤት ንጉስ ሆይ ሺህ አመት ይንገሱ ! ጠሩኝ ?
ንጉስ ፦ ከእንግዲህ የክርስቲያኖች ደም መፍሰስ ይቅር ፤ የተፋለሰው ስርዓትም ወደነበረበት መልኩን ሳይቀይር ይስተካከል። አብያተ ጣኦታት ተደምስሰው አብያተ ክርስቲያናት ተስፋፍተው የክርስትና እምነት ወደነበረበት ይመለስ። አሁኑኑ አዋጁን ንገር ስራውም ይፋጠን።
አሽከር ፩ ፦ እሺ ንጉስ ሆይ ! አሁኑኑ እንደቃልዎ አደርጋለሁ ስራውም እጀምራለሁ (እጅ ነስቶ ይወጣል)
ንጉስ ፦ አዎ የክርስቲያን መናኞች ደም ልበቀልና ነፃነታቸውን ላውጅ የምችለው አሁን ነው። (ንግስት እሌኒ ትገባለች)
ንግስት እሌኒ ፦ ደህና ዋልክ ልጄ ? (እጅ ትነሳለች)
ንጉስ ፦ እግዚአብሔር ይመስገን፤ ቸርነቱ የበዛ አምላክ ጠብቆኝ እነሆ እዚህ አድርሶኛል። ቁጭ በያ እናቴ
ንግስት እሌኒ ፦ አይ ልጄ ቁጭ በይ አልከኝ… ምን የሚያስቀምጥ ነገር አለ ብለህ ነው ?
ንጉስ ፦ እናቴ ምነው ምን ገጠመሽ ? (ደንገጥ በማለት) እንዲህ ከልክ በላይ የሚያስጨንቅ ነገር ?
ንግስት እሌኒ ፦ ልጄ ነገሩስ ቀላል ነው ፤ እንደው ፈቃድህን ለማግኘት ብዬ እንጂ።
ንጉስ ፦ እኮ ብትነግሪኝ ነገሩን…
ንግስት እሌኒ ፦ ብፅዐትን ለእግዚአብሔር ገብቼ ነበር ፤ ይኸውም አንተ ኃይማኖትህን ጠብቀህ እንደ አላውያን ነገስታት አረመኔነት ሳያጠቃህ ከስጋ ይልቅ ለመንፈሳዊ ህይወትህ እንድታደላ ካደረገልኝ…. የፈረሱ ቤቶችህን አስተካክላለሁ የተዘጉትንም አስከፍታለሁ መስቀሉንም እፈልጋለሁ የሚል ነበር ።
ንጉስ ፦ እና እናቴ ያስጨነቀሽ ይህ ነው? ይሔማ እጅግ የተቀደሰ ሀሳብ ነው። ታዲያ እኔ ምንን እንዳአደርግልሽ ትሻለሽ?
ንግስት እሌኒ ፦ ምንም አታደርግልኝም ብቻ መልካም ፈቃድህንና በቆይታዬ የሚያገለግሉኝ ሎሌዎችህን ትሰጠኝ ዘንድ እሻለሁ።
ንጉስ ፦ እንግዲያማ በሰላም ሂጂ እናቴ፤ ዓለም ሁሉ የዳነበትን መስቀል ፈልጊ እነሆም እኔ በስራሽ ሁሉ ከጎንሽ ነኝ። እግዚአብሔር ካንቺ ጋር ይሁን። (አሽከር ይጠራል የሆነ ነገር ያመጣል እንደ አገልግል ምናምን /ሰላምታ ተሰጣተንው ትወጣለች)
#ትረካ ፦ ንጉሱም ብዙ ጊዜ ሳይወስድ የሚከተሏትን ሰራዊትና በኢየሩሳሌም ስንቆይ ለተለያየ ነገር የሚሆናትን አያሌ ብርና ወርቅ አሲዟት በሰላም ሸኛት። የሀገሩ መሳፍንትና መኳንንትም ከእርሷ ጋር አብረው ጉዟቸውን አደረጉ።
(መዝሙር ፦እሌኒ ንግስት ሀሠሠት መስቀሉ)
#ትረካ ፦ ንግስት እሌኒ ኢየሩሳሌም እንደደረሰች ፈጣሪዋ የልቧን መሸት ይፈፅምላት ዘንድ ሱባኤ ገባች። ሱባኤውን እንደፈፀመችም መስቀሉን ፍለጋ አንድ ብላ ጀመረች ።
(በመሀል ፦ እሌኒ ንግስት ድጋሚ ይዘመራል)
#ትዕይንት_ሁለት
(ንግስት እሌኒ ትመጣለች፤ ሁለት ሰዎችን መንገድ ላይ ታገኛለች)
ንግስት እሌኒ ፦ ሠላም እንደምን ዋላችሁ ?
ሁለቱም ሰዎች ፦ ደህና
ንግስት እሌኒ ፦ ይቅርታ እንደው የክርስቶስ መስቀል ያለበትን ቦታ ታሳዩኝ ?
ሰውዬው ፩ ፦ ኸረ እኛ አናውቅም፤ የሰማነው ነገርም የለ (እየተኮፈሰ)
ንግስት እሌኒ ፦ እሺ እግዚአብሔር ይስጥልኝ።
(እነሱም ዞር እያሉ እያላገጡ ይሄዳሉ ሁለቱ ቀዎች ፤ ንግስት እሌኒ እጅግ ሰው የመፈለግ ስራ ትሰራለች ከውስጥ መዝሙር ይዘመራል።
መዝሙር :- አቤቱ አንተን እጠራለሁ
ነፍሴን ወደ አንተ አነሳለሁ
ዝም አትበለኝ እጮኻለሁ /፪/
ንግስት እሌኒ ፦ በቃ እንግዲህ ተስፋዬ ተሟጧል አንድ ሰው እንኳን ስለመስቀሉ የሚነግረኝ አጣሁ። እንግዲህ ምን አደርጋለሁ ወደ ሀገሬ ልመለስ (አሽከሮቹን ደሞ በሉ እናንተ ጓዛችንን ሁሉ ሰብስቡ እና ወደ ሀገራችን እንመለስ /እንግዲህ እያለች ኪራኮስ ይመጣል / እህ ….. ያ ….. እኛ አዛውንት ተመለከታችሁ። ተመስገን አምላኬ ምን አለ እውነቱን ቢነግሩኝ)
ንግስት እሌኒ ፦ (ጠጋ ብላ) ደህና ዋሉ አባቴ ?
ኪራኮስ ፦ እግዚአብሔር ይመስገን
ንግስት እሌኒ ፦ እንደው የክርስቶስ መስቀል ያለበት ቦታ ቢያሳዩኝ ?
ኪራኮስ ፦ እግዚአብሔር ይመስገን
ንግስት እሌኒ ፦ እንደው የክርስቶስ መስቀል ያለበትን ቦታ ቢያሳዩኝ ?
ኪራኮስ ፦ (ትንሽ እንደማሰብ ይልና) በመሰረቱ እርግጠኛ ልሆን አልችልም ነገር ግን ከዛሬ ፪፺፪ ዓመት በፊት ይህ ጌታችን የተሰቀለበት መስቀል ብዙ ህሙማንን ይፈውስ ሙታንን ያስነሳና ሌሎች ታላላቅ ተአምራትን ያደርግ ስለነበረ ክርስቶስ ለዓለም ቤዛ ሊሆን ቢመጣ የሰውን ልጅ ከዲያቢሎስ አስራት ነፃ ሊያወጣው ሞትን በሞቱ ሊሽር ከሰማየ ሠማያት ቢወርድ ይቃወሙት የነበሩትና በኋላም ወንጅለው አሰቃይተው ለሞት ያበቁት አይሁድ መስቀሉ ያደረጋቸውን ታምራት ማየት ውርደት ስለመሰላቸው ደበቁት።
ንግስት እሌኒ ፦ (ፈጠን በማለት) ወደየት ደበቁት ?
ኪራኮስ ፦ ያ……. ያ……. ያ ይታይሻል ? (ወደ ሩቅ እያሳያት)
ንግስት እሌኒ ፦ (በአዎንታ እራሷን ትነቀንቃለች) አዎ !
ኪራኮስ ፦ ጎላጎል ይባላል ፤ የራስ ቅል ማለት ነው በዚህ ውሉ በማይታወቅ ሰፊ ቦታ እንደተቀበረና ህዝቡም ሁሉ ቆሻሻ ማጠራቀሚያ እንደሆነ አያቴ በታሪክ አጫውተውኛል (ይሉና በለሆሳስ ያወራሉ)
(መዝሙር ፦ ትቤሎ እሌኒ ለኪራኮስ)
ንግስት እሌኒ ፦ ተመስገን አምላኬ ይህንን ነገር ያመለከትከኝ ፤ አሁን አንተ ከእኔ ጋር ሁሉ፤ እረዳትም ሁነኝ። እንደው ባላስቸግሮት መልካም ፈቃድህ ከሆነ መስቀሉን አብረን ብንፈልግ ?
ኪራኮስ ፦ እ…… (ጥቂት አሰብ ያደርግና) በጄ እንዳልሽ ነገር ግን ከስራችን አስቀድመን በቶሎ እንዲሳካልንና ፈጣሪያችን እንዲያመለክተን ሱባኤ መግባት አለብን ።
ንግስት እሌኒ ፦ እርሱንማ እኔም አስቀድሜ አስቤው ነበር።
ኪራኮስ ፦ እንዲያማ እንሂድ ፤ ዛሬ ነገ ሳንል ስራችንን መጀመር አለብን።
ንግስት እሌኒ ፦ (ፈጣሪን የማመስገን ነገር እያሳየች ወደ ውስጥ ይገባሉ፤ መስቀሉ ያለበት መሬት መሰል ነገር ይገባል፤ እየተስተካከለ ከውስጥ የእግዚአብሔር ድምፅ ይሰማል)
እግዚኦ መሀረነ ክርስቶስ /፪/
በእንተ ማርያም መሀረነ ክርስቶስ /፪/
በእንተ መስቀልከ ርድአነ ክርስቶስ /፪/
#ትረካ ፦ ንግስት እሌኒ የመስቀሉ ፍቅር እንደእሳት ያቃጠላት መሆኑን የተረዳለት ሁሉን የሚያውቅ የሁሉ ገዢ የሁሉ ፈጣሪ እግዚአብሔር በቅዱስ ሚካኤል መሪነት በአረጋዊ ኪራኮስ አማካኝነት ደመራ ደመራ እጣን እንድትጨምርበትና እጣኑም ወደ ሰማይ ደርሶ ሲመለስ የሚያፍርበትን ስፍራ አስቆፍራ መስቀሉን እንድታወጣ አመልክቷት ሱባኤዋንም በሰላም ፈፀመች። ንግስቲቱም መልአኩ የነገራትን መሰረት አድርጋ ደመራ ይደመር ዘንድ ትዕዛዝ አስተላለፈች።
775 viewsብርሃኑ መለሠ, 17:31