2022-08-28 09:51:58
" ሰሞነኛ ትኩሳቶቼ "
ከምን እና እንዴት ብዬ መጻፍ እንዳለብኝ ባላውቅም ...መጻፌን ግን እቀጥላለሁ ፦....አንዳንድ ጊዜ እኔ ያልኩትን ካልሆንክልኝ ከሚል እሳቤ ከተላቀቅሁ ሳልሰነብት አልቀርም በማህበራዊ ሚድያ ሐሳቦቼ ላይ ከእኔ ጋር በእምነት በዶግማ በቀኖና ጭምር የማይስማሙ አንዳንድ የሌላ ቤተ እምነት ሰዎች ክርስቶስን ከእኛ በላይ አታውቀውም የእውነቱ ቱንቢ እኛ ጋር ነው ያለው የሚመስል ተመሳሳይ ትችቶችን ሲሰነዝሩ አስተውላለሁ እግዚአብሔር ፈልጎአገኘኝ በማያልቀው ምህረቱ አዳነኝ እንጂ በፍለጋ አላገኘሁትም በፍቅሩ እንዲው የወደኝ ጌታ ዝም ብሎ አይተወኝም የሲኦም ማስገቢያውና ማስወጫው ቁልፍ እጃችሁ ላይ ያለ ይመስል ዳግም ወደ ጨለማ ዳግም ወደ ትፋት ዳግሞ ወደ ጥልቁ እምደገና ወደ ኋላ የሚሉ ያላዋቂ ሰው ሐሳብ የምትሰነዝሩ ሰዎች ከእንግዲህ በስርዓቱ ቃሉን መሰረት በማድረግ ብቻ ሀሳብ እንድትሰጡ አሳስባችኋለሁ ።
ወዲህ ደግሞ አይናችሁ ደም ለሚቀላ
እኔ በፊቴ ያለኝን አክሊል እየተመለከትኩ ሩጫዬን በትእግስት በመሮጥ ላይ እገኛለሁ ቤተ ክርስቲያንን መውደዴ በይበልጥ ጨምሯል አባቶቼን የማከብርበት ክብርም ከፍ ያለ ነው ። እኔ አሁን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን አማኝ ነኝ ። ለእኔ ትልቁና ዋናው ነገር ይህ ነው ። በተሰጠኝ የአገልግሎት መስክ ደግሞ አገለግላለሁ በከዚህ ቀደሙ አገልግሎት ኢትዮጵያን ከዳር እስከ ዳር ዞሬ አገልግያለሁ ከ5 ብር የአበል አገልግሎት እስከ እግዚአብሔር ይስጥልን አገልግያለሁ አምላኬ አገልግሎቴን አይረሳም አሁን በባለፈው ዘመን ትዝታ እየዋኘን በማህበራዊ ሚድያ በምችላትና በተሰጠችኝ ጸጋ በማገልገል ላይ እገኛለሁ አምላኬ ይንህንንም አገልግሎት ስለሰጠኝ ክብሩን ይውሰድ ።
ምናልባትም ፦
በሕይወቴ ዘመን ምናልባትም ትልቁና አስቸጋሪው ተግዳሮት ላይ ሳልሆን አልቀርም ግና ይህም ያልፋል ። ቀስቱ የአንድ ወገን አይደለም በሁለት ወገን የተሳለ ሰይፍ እንጂ በአባቴ ያለው የታላቅ ወንድሜ ግልምጫ ከግልምጫ አልፎ ቁንጥጫና እርግጫ ቢጨመርበትም እንኳን ከእሪያዎች ጋር ልመገብ እንደገና አልመኝም ። ብዙ አገልጋዮች የእኛን ቤት ታውቀዋለሁ ሰው ሲመጣ አንወድም የሚል ድግግሞሽ ያለበት ንግርትን ከመናገር ውጪ ምንም ሲፈይዱ አለማየቴ ከመገረም በቀር ምን እላለሁ ። በቅርቡ እንኳን አንድ ወዳጄ ወደ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ተመልሶ ቀኖናውን ጨርሶ ተጠምቆ ቢመጣም እንደገና ወደ ኋላ መመለሱን ስሰማ በእጅጉ አዝኛለሁ ወደ ቤቱ የመጣን ሰው በአይነ ቁራኛ 3 ዓመት ሙሉ ማየት አምስት አመት ሙሉ እጅ መንሳት የተመላሹንም አእምሮ ያዝላል ብዙ ዋጋ ያስከፍላል ቤተ ክርስቲያንም ልታስብበት ይገባል እላለሁ ።
ግና ፦
ለምን ይሆን መከፋፋታችን እላለሁ ቤተ ከርስቲያን ደጇ ሰፍቶ እያለ ስንዱ እመቤት እያልን እየጠራናት ለምን ይሆን መጠላለፋችን ብዬ በማሰብ እብሰለሰላለሁ ሌላው ቤተ እምነት እንኳን መጥተህ የመምጣት ሽውታውን ሰምተው እንኳን በተለየ ሁኔታ ያቀርቡሃል ሰላምታም ይሰጡሃል ። በጣም የሚያስደንቀኝ እውነታ ደግሞ በግል ተነጥፈው ሰላም የሚሉህ በጀምኣ ስታገኛቸው እንደማያውቁህ ጠርቅመውህ ማለፋቸው ይበልጥ ያከፉሃል ክርስትና ይህንን አይመክርም ከክርስቶስም ይህንን አልተማርንም ብዙ ቀናኢ ወንድሞች እህቶች ባሉበት ጥቂት እርሾዎችንም አስተውያለሁ ።
ሀሳቤን ስጠቀልለው ፦ አገልግሎት ስላለኝ አልታክትም ።
741 viewssolomon abubeker, 06:51