2022-02-26 20:14:57
"ተከራያችን "
ክፍል፦፯
ደራሲ፦ሶፊ
" ምን እያልከኝ ነበር? " አለች ወደኔ እያየች
መድገም እየቀፈፈኝ እንደምንም ስሜቴን ታግዬ..."ምን ሆነሽ ነው የጠፋሽው? " አልኳት።
"ምንም አልሆንኩም...የጠፋሁበትንም ምክንያት ደጋግሜ ነግሬህ የለ ስራ ነው።" አለችና ዝም ስትል።
ከእንግዲህ ምንም መጠየቅ ትርፉ ድካም መስሎ ተሰማኝ፤አውቆ የተኛን ቢቀሰቅሱት አይሰማም።ምንም ልትነግረኝ እንዳልፈለገች ሁኔታዋ ይናገራል።
"ጨከጨኩሽ አይደል?" አልኳት። መልስ አልሰጠቺኝም።
ከቢራዬ ጎንጨት ብዬ ጥያት የመሄጃ ሀሳብ አብሰለስል ጀመር።አንዳንድ ሰዎች መሄጃ ያጣን ይመስላቸዋል።ከእናቴ ጋር እያወራሁ ባመሽ በስንት ጠሀሙ፤የሚወዱኝን ጓደኞቼን ባገኝስ...ፊልም ባይ መፅሐፍ ባነብ ብዙ የምወዳቸውን ነገሮች ማድረግ እየቻልኩ።ከማይወደኝ ጋር ምን እሰራለሁ?
ይቀየራሉ ሰዎች ይቀየራሉ ማንም ባለበት አይረጋም።አፈቀርኩህ ያለችህ የወደደችህ መስሏት ይሆናል።ግራ ገብቷት ነው ግራ ያጋባችህ። ታዲያ ስትፈልገኝ ብቻ ነው የምትነግረኝ አልፈልግህም ተብሎስ አይነገርም? የምን ሽሽት ነው? እናቴም
"ስልኳ አሁንም አሁንም ይጠራል።"
ትቆያለሽ? እኔ ትቼው የመጣሁት ስራ አለ። (በልቤ እሱ ነው የሚያዋጣኝ አልኩ።) ትጠብቀኛለች። ትንሽ እቆያለሁ አለቺኝ። አስተናጋጁን ስጠራው ተወው ስወጣ እከፍላለሁ አለች። የአለማየሁ ገላጋይን "ሐሰተኛው~በእውነት ስም" የሚለውን መፅሐፍ ከጠረቤዛው ላይ አነሳሁና...ግርምት ባልተለየሁ ፈገግታ "ሰላም እደሪ አልኳት...መልእክት እየፃፈች የስልኳ እስክሪን ላይ እንዳፈጠጠች "ሰላም እደር አለቺኝ።" ደግሜ ላያት እደማልፈልግ ልቤን እያስጠነቀኩት። "ጎንበስ ብዬ ጉንጯን ሳም አደረኳት...ይሁዳስ እንደዛ አይደል ያደረገው? ለድሮ ማንነቷ አሳልፎ ሰጠዋት ?" ማን ነው ምንን አሳልፎ የሰጠው?
እኔ ምን አደረኩ ? እሷ ናት የተቀየረችብኝ።እያልኩ እራሴን ከወቀሳ ለማዳን መሯሯጥ ጀመርኩ።
እኔንማ ገድላኛለች የምወዳትን ትቼ ከእርሷ ጋር እንደሆንኩ ታውቃለች? የማልወዳቸውን ነገሮች ለእሷ ብዬ እንደማደርግ ታውቃለች? አታውቅም!
ለእሷ ብዬ ያደረኳቸው ያ ሁሉ ነገሮች ምንም ናቸው ማለት ነው። ባዶ መና ።
እሺ እንዴት ነው...እንደዛ ቀርባ አስለምዳኝ ብቻዬን የምችለው።
ብዙ የእኔ የምላቸው ነገሮች የእርሷ ስለሆኑ...እርሷን ማጣት ማለት ራሴን ማጣት መስሎ ተሰማኝና ራሴን ጨምድዶ ያዘኝ።
" ሰው የሰጡትን ቦታ ካላወቀ ምን ይደረጋል?"
ቤት ስገባ እናቴን ሰላም ብቻ ብያት ትንሽ ራሴን እዳመመኝና ማረፍ እንደምፈልግ ነግሬያት ወደ መኝታ ክፍሌ ገብቼ...ሳስብ አደርኩ።
በመጨረሻም የመጣልኝ ሀሳብ ራሴን በሳምንት ነገሮች መጥመድ ነው።ከስራ በተጨማሪ ኦንላይን አጫጭር ትምህርቶችን መማር ጀመርኩ።
ሳልደውል እሷም ሳትደውልልኝ...ሶስት ሳምንት ሞላ በዛው ሳምንት እኔ ክፍለ ሀገር ለስራ ጉዳይ ሄድኩ 1 ወር የሚያስቆይ ስለነበር ደስ እካለኝ ነው የሄድኩት።
፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨
ወሩን ሙሉ ያለምንም እረፍት አሳለፍኩ።ደውላልኝ አታውቅም እኔም አልደወልኩላትም። ልመለስ አካባቢ እናቴ ድንገት ስለእርሷ ጠየቀችኝ ስለ እርሷ አንስታብኝ ስለማታውቅ ግራ ተጋባው። "ደውላልህ ታውቃለች" ብላ ነበር የጠየቀቺኝ።
"አዎ እማ ተደዋውለን ነበር ምነው አዲስ ነገር አለ?" ብዬ ጠየኳት ልቤ ፈራ እያለ። "አይ እንዲያው ነው" አለቺኝ ድምጿ ላይ ግን የሆነ ነገር እንዳለ ተረዳው።"ምንድነው እማ? አመማት እንዴ ?" አልኩ ይበልጥ እየተጨነኩ። "ኧረ እንዲያውም" አለች። "በጣም ትቀራረቡ ስለነበር ዝም መባባላችሁ አሳስቦኝ ነው።" ለዚህ መልስ ስለሌለኝ ዝም አልኩ። ሌላ ሌላ ነገር ስናወጋ ቆይተን ተሰነባብተን ስልኩ ተዘጋ።ያልተዋጠልኝ ነገር አለ። ሁለት ቀን አይደለች ስሄድ እደርስበታለሁ ብዬ ተፅናናሁ።
፨፨፨፨፨የመጀመሪያው መጨረሻ፨፨፨፨፨፨፨፨
ከሁለት ቀን በኋላ ወደቤት ለመሄድ በለሊት ነበር የተነሳሁት እንደተለመደው በመስኮት በኩል ተቀምጬ ወቅቱ የአብይ ፆም በመሆኑ "ሕማማት" የሚል ዲያቆን ሄኖክ ሀይሌ የፃፈውን መንፈሳዊ መፅሐፍ የአምላካችንን ሕማም በሚገርም ብዕር ስለተከተበ በፍፁም ተመስጦ በአይነ ህሊና ተጉዤ..."ይሁዳ ሊሸጠው ሲያስማማ እንዴት አምላክህን አሳልፈህ ትሰጣለህ? እርሱ እኮ መምህርህ ነው እያልኩ እሞግታለሁ። አይነ ስውራንን ሲያበራ፥የተመለከቱ አይኖችህ እንዴት የአምላክህን ጌትነት ጋረዱብህ? አንካሶችይሁዳን ሲዘሉ፤ሽባ ሲተረተር ድዊያን ሲድኑ፤እንዳልተመለከትክ እግሮችህ እንዴት አምላክህን ለመክሰስ ተራመዱ እያልኩ። ወቀስኩ። በይሁዳ ውስጥ ራሴንም ወቀስኩ።መፅሐፉ ክርስቶስን ወደ ይሁዳ ለፍርድ እያንገላቱ ሲወስዱት በህሊና ወሰደኝ ጲላጦስ ፊት እያንገላቱ አቆሙት እኔን ጌታ ሆይ እያሉ የእየሩሳሌም ወዛዝርት ሲያለቅሱ ሳይ አብሬያቸው ላለቅስ ዳዳኝ...ከጲላጦስ ሄሮድስ ክርስቶስን እያንገላቱ ተቀባበሉት~በሁሉ የሚፈርድ እርሱ ላይ ይፈርዱበት ዘንድ አንዳች በደል አጡበት።ያዳናቸው ከሰሱት፤38 አመታት በደዌ ዳኛ ተይዞ የነበረው መፃጉህ ከእዚህ እስራቱ ያዳነውን አምላክ፤መላእክት ከመለኮታዊ ግርማው የተነሳ ፊቱ ስለሚያስፈራቸው በክንፍ የሚሸፈኑለትን የሚፈት የሚንቀጠቀጡለን አምላክ በጥፊ መታው።በሁሉ ላይ ለሚፈርድ ለእርሱ ፍርድን አጓደሉበት።"
በተመስጦ እያነበብኩ ቆየሁ። ልደርስ አካባቢ እናቴ ደወለች። እየመጣሁ ነው እማ አልኳት።ከሁለት ቀን በፊት የነበረው ሁኔታ አሳስቦኝ መፅሐፉን ወደ ሻንጣዬ መልሼ መብሰልሰል ጀመርኩ። ከባሱ እንደወረድኩ ታክሲ ለመያዝ ስጣደፍ አንድ የስራ ባልደረባዬ ክላክስ አድርጎ መኪናውን በእኔ አቅጣጫ ሲያቆም ተመለከትኩ።ጎንበስ ብሎ በመስኮቱ አጮልቆ እያየ "ሶፊ ወደ ሰፈር ነህ?" አለኝ። አዎ አልኩት እኔም አንገቴን በመስኮቱ አጮልቄ። እኔም ወደዚያው ነኝ ና እንሂድ አለኝ። ከፍቼ ገባው።እያወራን።ቤት አካባቢ ስንደርስ አቆመ።እንዲገባ ብለምነውም እንቢ አለኝ።ተሰናብቼው ለወሬ እየጓጓው ወደ ቤቴ አመራው የጊቡውን በር አልፎ ወደ ውስጥ ስገባ ያየውትን ማመን አቃተኝ።
ይ~ቀ~ጥ~ላ~ል።
@bestletters
227 views17:14