በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ ፡፡ አሜን ፡፡ ❀ ሚያዝያ ፳፯ ❀ ✞✞✞ እንኩዋን ለታላቁ ሰማዕት "ቅዱስ ፊቅጦር" ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ ✞✞✞ +*"+ ማር ፊቅጦር +"*+ =>ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን በደማቸውና በገድላቸው ያስጌጡ ብዙ ሰማዕታት አሉ:: ነገር ግን ከኮከብም ኮከብ ይበልጣልና ማን እንደ ጊዮርጊስና እስጢፋኖስ! +ከእነርሱ ቀጥለው ከሚጠሩ ሰማዕታት ደግሞ አንዱና ዋነኛው ቤተ ክርስቲያን "ማር" የምትለው ቅዱስ ፊቅጦር ነው:: እስኪ ከበዛው መዓዛ-ገድሉ ጥቂት እንካፈል:: =>ቅዱስ ፊቅጦር አባቱ ኅርማኖስ ይባላል:: አረማዊና ጨካኝ ነው:: እናቱ ግን የተመሰገች ቅድስት ማርታ ትባላለች:: ልጇን እንደሚገባ አሳድጋው 20 ዓመት ሲሞላው የአንጾኪያ ንጉሥ የሠራዊት አለቃና በመንግሥቱ 3ኛ አድርጐ ሾመው:: +የድሮዋ አንጾኪያ (ሮም) እንደ ዛሬዋ አሜሪካ ዓለምን የተቆጣጠረች ሃገር ነበረች:: ቅዱስ ፊቅጦር ደም ግባቱ ያማረ: በጦርነትም ኃይለኛ ስለ ነበር ሁሉ ያከብሩት: ይወዱትም ነበር:: እርሱ ግን ቀን ቀን ሲጾም: ነዳያንን ሲያበላ ይውል ነበር:: +ሌሊት ደግሞ እኩሉን ሲጸልይና ሲሰግድ: እኩሉን የእስረኞችን እግር ሲያጥብ ያድር ነበር:: ይህ ሁሉ ሲሆንኮ እርሱ የንጉሡ 3ኛ: የሠራዊትም አለቃ ነው:: በዘመኑ የሚያገድፍ ምግብና የወይን ጠጅ በአፉ ዙሮ አያውቅም:: +ከነገር ሁሉ በሁዋላ ንጉሡ ዲዮቅልጢያኖስ ካደ:: ዘመነ ሰማዕታትም ጀመረ:: አብያተ ክርስቲያናት ተቃጠሉ:: ከ47 ሚሊየን በላይ ክርስቲያኖች በመንኮራኩር ተፈጩ: በመጋዝ ተተረተሩ: ለአራዊት ተሰጡ: በግፍም ተጨፈጨፉ:: ቀባሪ አጥተውም ወደቁ:: +በዚሕ ጊዜ ማር ፊቅጦር እናቱን ቅድስት ማርታን በዕንባ ተሰናብቶ ወደ ንጉሡ ቀርቦ በክርስቶስ ስም ታመነ:: ክፉ አባትም በልጁ ላይ ሞትን መከረ:: +ከዚያም ቅዱሱን አፉን በብረት ለጉመው ወደ ምድረ ግብፅ አወረዱት:: መሪያቸው እንዳልነበረ ወታደሮቹ መኳንንቱ ሁሉ ተዘባበቱበት:: እርሱ ከምድራዊ ንግሥና ሰማያዊ መንግስትን: በሰዎች ፊት ከመክበር ስለ ክርስቶስ ሲል መናቅን መርጧልና:: +ለቀናት: ለወራትና ለዓመታት መኳንንቱ እየተፈራረቁ አሰቃዩት:: በርሱ ላይ ያልሞከሩት የስቃይ ዓይነት አልነበረም:: አካሉን ቆራርጠዋል: ዓይኖቹን አውጥተዋል: ምላሱንም ቆርጠዋል:: +በዚሕች ዕለት ግን በሰይፍ አንገቱን ቆርጠውታል:: ስለዚህም እናት ቤተ ክርስቲያን በታላቅ ማክበር ታከብረዋለች:: እግዚአብሔርም ለቅዱስ ፊቅጦር እንዲህ አለው:- "እንደ አቅሙ ስምህን የጠራ: መታሠቢያህን ያደረገ: ስምህን ያከበረ: የብርሃን ልብስ አጐናጽፌ ወደ መንግስተ ሰማያት አስገባዋለሁ::" ❖ቸሩ አምላከ ፊቅጦር ሁላችንም ይማረን:: ከቃል ኪዳኑ አሳትፎ ለርስቱ ያብቃን:: ❖ሚያዝያ 27 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት= 1.ጽኑዕና ኃያል ማር ቅዱስ ፊቅጦር ሰማዕት 2.ቅድስት ማርታ (የፊቅጦር እናት) 3.ብጽዕት እስጢፋና (በክርስቶስ ስላመነች ከ2 ሰንጥቀው የገደሏት የ15 ዓመት ወጣት) 4.ቅዱሳን ሳሲማና አባ ኖባ (ሰማዕታት) =>ወርኀዊ በዓላት 1.የጌታችንና አምላካችን መድኃኔ ዓለም ክርስቶስ በዓለ ስቅለት 2.አቡነ መብዐ ፅዮን ጻድቅ 3.ቅዱስ መቃርስ (የመነኮሳት ሁሉ አለቃ) 4.ቅዱስ ያዕቆብ ዘግሙድ 5.ቅዱስ ገላውዴዎስ ሰማዕት (ንጉሠ ኢትዮዽያ) 6.ቅዱስ ቢፋሞን ጻድቅና ሰማዕት ++"+ እግዚአብሔር ቅዱሳንን ስላገለገላችሁ: እስከ አሁንም ስለምታገለግሏቸው ያደረጋችሁትን ሥራ: ለስሙም ያሳያችሁትን ፍቅር ይረሳ ዘንድ ዓመጸኛ አይደለምና:: በእምነትና በትእግስትም የተስፋውን ቃል የሚወርሱትን እንድትመስሉ እንጂ ዳተኞች እንዳትሆኑ ተስፋ እስኪሞላ ድረስ እያንዳንዳችሁ ያን ትጋት እስከ መጨረሻ እንድታሳዩ እንመኛለን::+"+ (ዕብ. 6:10-13) > https://t.me/saint_mikael 935 views21, 06:51