2022-04-26 11:11:08
ቶማስ፣ አልዓዛር,፣ አዳም
የትንሣኤ ሳምንት ሥያሜዎች
ማዕዶት(ሰኞ) ፣ ቶማስ(ሠሉስ)፣አልዓዛር(ረቡዕ)፣አዳም ሐሙስ፣ቤተ ክርስቲያን (ዓርብ)፣ አንስት አንከራ (ለቅዱሳት አንስት)(ቅዳሜ) ተብለው እንደሚጠሩ ይታወቃል፡፡
ቶማስና አልዓዛርና አዳም ከትንሣኤው ጋር የተገናኙበት ምክንያት ሦስቱም ሞተው የተነሡ ስለሆነ ነው፡፡
ቶማስ በጥርጥር የሞተ ነበር
አልዓዛር በሥጋ ሞቶ ነበር
አዳም በሥጋም በነፍስም ሞቶ ነበር
✞ቶማስ፦ ሰዱቃዊ ነው ትንሣኤ ሙታንን የማይቀበል የማያምን ሰው ነበር፤ የጌታን ትንሣኤ ለመቀበል የተቸገረው አእምሮውን ገድሎት የነበረው ሰዱቃዊው ሀሳብ ስላልተለየው ነበር፡፡ ይሄ ብቻ ሳይሆን ጌታ አልዓዛርን ለማስነሣት ሐዋርያትን እንሂድ ሲላቸው "ዲዲሞስ የሚሉት ቶማስ ለባልንጀሮቹ ለደቀ መዛሙርት። ከእርሱ ጋር እንሞት ዘንድ እኛ ደግሞ እንሂድ አለ" ይላል ዮሐ 11፡16፡፡
የጌታችንን ከሞት መነሣት እርግጥ ሆኖ ሲያገኘው ግን የሞተው አእምሮው/ሀሳቡ ተነሥቷል ፤ "ጌታዬ አምላኬ" ብሎ ጠርቶ ሕያውነትን ተቀላቅሏል፡፡
"አንሥአኒ በትንሣኤከ፤ በትንሣኤህ አንሣኝ" እንዲል ቅዱስ ያሬድ ቶማስን በትንሣኤው አንሥቶታል፤ ስለዚህ የትንሣኤው 3ኛው ቀን ለቶማስ መታሰቢያ ሆኗል፡፡
✞አልዓዛር ፦ የሞተው ረቡዕ መጋቢት 18 ቀን ነበር ፤ የተነሣው ደግሞ ቅዳሜ መጋቢት 21 ቀን ነው፤ የስሙ ትርጓሜም የእግዚአብሔርን ረዳትነት የሚጠቁም ነው፡፡
አልዛር ጌታ የሚወደው፤ ልቡም ቤቱም ለጌታ እንግድነት የተከፈተ ነበር፡፡
በዚህም ንጹሕነቱና የዋህነቱ መቃብሩ ላይ ጌታውና አምላኩ መንታ መንታውን የእንባ ዘለላ እያወረደ አልቅሶለታል፤ እንደሚያስነሣው እያወቀ ግን ስለ ሞቱ ስለ አሟሟቱ በመቃብርም ስለመቆቱ አልቅሶለታል
በእርግጥ ያለቀሰው ለአልዓዛር ብቻ አልነበረም በመርገም ምክንያት በሞት ስለተነጠቁት የሰው ልጆች ሁሉ ነበር!!!
አይሁድ የጌታን የዕንባውን ብዛት የኀዘኑን ጽናት ተመልክተው "ርእዩ መጠነ ያፈቅሮ፤ ምን ያህል እንደሚወደው እዩ" እየባባሉ ተገርመዋል!!!
በዚህ ጊዜ የማወደውን አልዓዛርን ከመቃብር ጠርቶታል ጊዜያዊ ትንሣኤንም አስነሥቶታል
አልዓዛር ከዛ በኋላ 40 ዓመት ቆይቶ አርፏል፡፡
የሞተበትን ዕለተ ረቡዕን ሳይለቅ ረቡዕ የአልዓዛር መታሰቢያ ሆኖ አልዓዛር እየተባለ ይጠራል፡፡
☞ቅዱስ ያሬድ " ነአምን በዘአንሥኦ ለአልዓዛር እመቃብር ወኪያነሂ ያነሥአነ ምስሌሁ በትንሣኤሁ እምነ ሙታን፤ አልዓዛርን ከመቃብር ባስነሣው ጌታ እናምናለን፤ከሙታን ተለይቶ በመነሣቱ እኛንም ከእርሱ ጋር እንደሚያስነሣን እናምናለን" በማለት ተናግሯል፡፡ (የዕለቱ "እስመ ለዓለም")፡፡
✞አዳም ፦ አዳም ሐሙስ፤ ይህ ቀን አጠቃላይ ጌታ ለአዳምና ለልጆቹ ለልጅ ልጆቹ የከፈለውን ካሳ የፈጸመውን የማዳን ሥራ የምንዘክርበት ነው፡፡
በሥጋም በነፍስም በመንፈስም ሞቶ የነበረውን ሰውነታችንን ማዳኑ ይነገርበታል፡፡
አዳም ከነልጆቹ "ስብሐት ለእግዚአብሔር ዘከውረሰነ መንግሥቶ ሰማያዊተ" እያለ ወደ ገነት መግባቱ ይታሰብበታል፡፡
ክርስቶስ እኛም ተነሥተናልና የእኛም ትንሣኤ ይከበርበታል፡፡
በዚህ ምክንያት ዕለተ ሐሙስ በበኩራችን በአዳም "አዳም ሐሙስ" ተብሎ ይጠራል፡፡
የዓመት ሰው ይበለን!
አሜን!!!
@rsjie
159 viewsedited 08:11