Get Mystery Box with random crypto!

'ትርፉ ትዝብት ነው!!' ሌብነት (ሙስና) ያልተገባ ጥቅም ለማግኘት ሲባል ታማኝነትን በማጉደል | Prosperity Party A.A ብልፅግና

"ትርፉ ትዝብት ነው!!"

ሌብነት (ሙስና) ያልተገባ ጥቅም ለማግኘት ሲባል ታማኝነትን በማጉደል የሚፈፀም ኢ-ሞራላዊና ኢ-ህጋዊ የሆነ የወንጀል ተግባር ነው። አስቦ፤ ፈቅዶና ተዘጋጅቶ የሚፈፀም መሆኑ ደግሞ የድርጊቱን ለሞራል፣ ለህግና ለማህበረሰብ መስተጋብር ተቃራኒ የሆነ የክህደት ገፅታውን በግልፅ የሚያሳይ የእምሮ መላሸቅና ህሊና ቢስነት እንዲሁም የቅንነት መጓደል ውጤት ነው።

ይህ ተግባር በግለሰብ፣ በቡድና በተቋም ደርጃ ሊፈፀም ይችላል። በእዚህ የተነሳም በአይነቱ ዝቅተኛ /petty / እና ትልቅ /Grand/ በደረጃው ደግሞ አስተዳደራዊ ወይም ፖለቲካዊ ወዘተ...የሚል ክፍፍል በማድረግ ውስብስብ ባህሪውንና የሚያደርሰውን ተፅዕኖ ማሳየት የተለመደ ነው::

ዓይነቱም ይሁን ደረጃው ይለያይ እንጂ በፍላጎትና በዓላማው አንድና ያው ነው። በመጠንም ይሁን በሚያስከትለው ማህበረሰባዊ ጉዳቱም አደገኛ ነቀርሳ መሆኑ ነው::

ጉዳቱም ከግለስብና ከተቋም እስከ ሀገር የመደርስ አቅም ያለው ነው:: የሀገርን ጥቅም የማስከበር ወይም የተቋምን ተወዳዳሪነት፣ የማረጋገጥ ጥንካሬን በማላላት ሀገርንና ህዝብን ለጥቃት ተጋላጭ ተቋምን ደግሞ ለኪሳራ ይዳርጋል:: በውጤቱም እድልና ተስፋን በመንጠቅ ለጤናማ ማህበረሰባዊ መስተጋብር እና እድገት እንቅፋት በመሆን ያለህንና የሚኖርህን ሁለንተናዊ አቅም ያሽመደምዳል::

በዚህም በአንድ ሀገር ፖለቲካዊ ስርዓት ውስጥ ዲሞክራሲን በማቀጨጭ፣ በኢኮኖሚው የምርትና የአገልግሎት እንዲሁም የግብይት ሂደት በማዛባት በማህበራዊ ህይወት ድልብ ሀብቶችን በመሸርሸር፤ የህግ የበላይነት እንዳይከበር በማድረግ ፍትህን በማዛባት፤ ቴክኖሎጂን በመጠቀም ቅልጣፌንና ግልፅነት የማስፈን ትሩፋት በመቀማት ሊገለፅ የሚችል አደገኛ ቫይረስ ነው:: ዛሬ ሀገራችንን ከገጠማት የውስጥና የውጭ ጠላቶች ያልተናነሰ ግንባር መሆኑን ልብ ይሏል::

ይህ እኩይ ተግባር ባለቤትና ተዋናይ ያለው ነው:: ሰራቂና ተሰራቂ ተጠቃሚና ተጎጂ ተከላካይና አጥቂ ሆነው የሚሰለፉበት ትዕይንትም አለው:: በዘራፊና በተዘራፊ መካከልም እስከ ግልፅ ግብግብ ሊደርስ የሚችል ነው:: ስርዓታዊ ሊባል በሚችል ደረጃ /state captured/ ሲደርስ ጦር እንደሚያማዝዝ ሀገራችንን ጨምሮ የብዙ ሀገራት ልምድ ያሳያል::

ስለሆነም ሌብነትን ምንም ይሁን ምን መቼም ይሁን መቼ በምንም ይሁን በማን ኃላፊነት የሚሰማው ሰው ተቋምና መንግስት ህገርን ፣ ህዝብንና ተቋምን ገዳይ ተግባር በመሆኑ በጋራ የመታገል የማውገዝ ልምምድና ባህል ማሳደግ እንዳለብን ይሰማኛል:: ይህን ያልኩበት ምክንያት ከሰሞኑ የአዲስ አበባ ነዋሪዎች የቤት ችግር ለመፍታት በሚደረገው ጥረት የግልና የቡድን ፍላጎት ለማሳካት ሲባል ቴክኖሎጂ በማበልፀግ ሂደት ውስጥ የሙያና የሃላፊነት እምነት በማጉደል የተፈፀመው ፀያፍ ተግባር ለህዝብ ጥቅም ሲባል እየተወሰደ ባለው እርምጃ የህዝብ ድጋፍ የታየበት ቢሆንም በአንፃሩ የተስተዋለው አሉታዊ እንቅስቃሴ ግን የሚያስተዛዝብ ነበር::

የከተማ አስተዳደሩ ቁርጠኝነትና የህዝብ ውግንና ተግባር ተጠናክሮ ይቀጥላል:: በሌብነት ላይ ከተሰመረ ቀይ መስመር ማዶ የሚካሄድ ግብይት ግን ለሀገርም ለከተማው ማህበረሰብና ለተቋም ግንባታ ጠቃሚ ባለመሆኑ ትርፉ ትዝብት ነው::
የሌብነት አስተሳሰብን የመለወጥ ከባድ ትግል ቀልጣፋና ግልፅ የተግባር አውድ ለመፍጠር ሲባል በቴክኖሎጂ ለመደግፍ የሚደረገውን ጥረት ማጠናከር እና ገንቢና ደጋፊ የህዝብ ተሳትፎ በማጎልበት ለጠንካራና የበለፅገች ሀገር ግንባታ አቅማችንን እናውል።

- አቶ መለሰ ዓለሙ
የአዲስ አበባ ብልፅግና ፓርቲ ጽ/ቤት ኃላፊ