2022-08-17 22:19:16
++++###ያልበሩ_ችቦዎች####++++
በዓለ ደብረ ታቦር በእኛ ቤተ ክርስቲያን ከዘጠኙ ዐበይት በዓላት መካከል አንዱ ነው። በግብጽ ግን ዐበይት በዓላት ተብለው የሚከበሩት ሰባት ስለ ኾኑ በዓለ ደብረ ታቦር ከዐበይት አይመደብም።
ይህ በዓል ብዙ መለያዎች ያሉት ቢኾንም፥ በኢትዮጵያ ለየት የሚያደርገው ከበዐሉ ጋር ተያይዘው የሚከበሩት ትውፊታዊ ባህሎች ናቸው። ጅራፉ፣ ሙልሙሉ፣ ችቦው፣ ሕፃናት እየዞሩ የሚያቀርቡት ግጥም። እነዚህ በዓሉን ውብ አድርገው የሚያሳዩ ጌጦች ናቸው። ዋና ዓላማቸውም ጌታችን በታቦር ተራራ የገለጠውን ምሥጢረ መንግሥቱን ማሳየትና በዚያን ዕለት የኾነውን ነገር አኹን እንደ ኾነ አድርጎ ማቅረብ ነው።
አምላካችን ክርስቶስ ለቅዱሳን ሐዋርያት ከፍ ባለው ስፍራ (በታቦር ተራራ) አስደናቂውን አምላካዊ ብርሃን ብልጭታውን ጨረፍ አድርጎ አሳይቷቸዋል። በጣም በጥቂቱ። አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ አዳም ቀድሞ በገነት የለበሳትን የብርሃን ልብስ ገለጣት ይሉናል። አምላክ በአምላክነቱ ይገለጥ ዘንድ ተገቢ አይደለምና! ቢገለጥ የታቦር ተራራ አትችለውም ነበርና። የኾነው ኾኖ መገለጡ የተከወነው በከፍታ ነው። ነገሩ "በሰማይ የሀሉ ልበክሙ" ልቡናችሁን ከፍ አድርጋችሁ በሰማይ አኑሩት ነው! አእምሩ ኀበ ዘትቀውሙ "የቆማችሁበትንም ቦታ አስቡ" እንዲል። ወደ ታቦር መውጣት ቅዳሴን ወደ መረዳት መውጣት ነው። በንጽሕና እና በሥርዓት በቅዳሴ ውስጥ ከኾን፡በሕያዊት የታቦር ተራራ ላይ መኾናችንን ልብ እንበል። በዓለ ታቦርን ራቅ አድርገን ሳይኾን እዚሁ አጠገባችን እንዳለ ከመረዳት እንነሣ! ስለዚህ አስተሳሰባችንን ወደ ላይ ከፍ እስካላለ ድረስ በዓሉን በውስጣችን እያከበርነው አይደለም ማለት ነው። በዓሉን በዋናነት ማክበር ያለብን በእኛው ውስጥ ነውና!
ጅራፉ በራሱ መጮኸ አይችልም። በሰው እጅ ተይዞ ሲጮኸ ግን በታቦር ተራራ ላይ የተሰማውን ድምፅ የሚወክል ይኾናል። ይህም ድምፅ በእኛ ሰውነት ውስጥ መሰማት አለበት። ለሰው ልጆች በሙሉ ያለን የፍቅር ድምፅ! ክርስቶስን በሙሉ ሰውነታችን ለማግኘት የመጓጓት ድምፅ! ሰላምን ለዓለም የሚያበራ ድምፅ! ይህ ድምፅ ከሕያው ሰውነታችን መውጣት አለበት። እኛ ዕውቀት ያላቸው ጅራፎች ኾነን መቅደስ በኾነ ሰውነታችን ውስጥ የቅድስናና የንጽሕናን ድምፅ ማሰማት አለብን። ሌላ ታቦር ፍለጋ አንሂድ ሰውነታችንን ከቀደስነው ሕያዋን የታቦር ተራራዎች እኛው ነንና። አምስቱ አገልጋዮች (ሙሴ፣ አልያስ፣ ጴጥሮስ፣ ያዕቆብና ዮሐንስ) የአምስቱ የስሜት ሕዋሶቻችን ምሳሌዎች ናቸው። እንግዲህ እኒህን አካላት ቀድሰን ለእግዚአብሔር ስናቀርብ እግዚአብሔር በእኛ ሰውነት አድሮ ብርሃኑን ይገልጣል። የፍቅር ድምፁን በእኛ በኩል ለኃጥአን ያሰማል፥ ኑ ወደ እኔ እኔ አምላካችሁ ነኝና ይላል።
ልበ አምላክ ዳዊት "ታቦር ወአርሞንኤም በስመ ዚአከ ይትፌስሑ ወይሴብሑ ለስምከ" ያለው ስለ ታቦርና አርሞንኤም ለማውራት ብቻ አይምሰለን፥ ስለ እኛም እንጂ። የተግባራዊ ሕይወት ድምፃችንን ከፍ አድርገን ክርስቶስን መምሰል ለዓለም በማሳየት ደስ ልንሰኝ የሚገባ ነውና። የጅራፉ ጩኸት የአብን ድምፅ የሚወክል እንደ ኾነ ከጅራፉ በላይ የኾን እኛ የአብን ድምፅ በእውነተኛ ሕይወታችን ለአሕዛብ ልናሰማ ይገባናል። በሕይወት ጨለማ ውስጥ ላሉት ኃጥአን በሕይወታችን የክርስቶስን የፍቅር ብርሃን እያበራን ወደ እውነት ልንጎትታቸው ይገባል።
ታቦር ጨለማ አይደለችም፥ የሥግው ቃል ብርሃን የተገለጠባት ልዩ ስፍራ እንጂ። እንግዲህ ያን በታቦር ተራራ የበራውን ብርሃን በችቦ በኩል እንገልጠዋለን። በችቦው ብርሃን በኩል ወደ አማናዊው ብርሃን እንጓዛለን። እንግዲያውስ ከክርስቶስ ሕያዊት ማኅደር ሰውነታችን በቀር ብርሃኑ የማይቋረጥ ችቦ ወዴት ያለ ይመስላችኋል? የእኛ ሰውነት እየነደደ የሚያበራ ችቦ ነው። ወንጌልን የሚያበራ ችቦ! ወዲህ አለ። የኸውም የቅዱሳን ሰውነት ነው። ለዚህም ነው ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ የሚነድና የሚያበራ መብራት ተብሎ በጌታችን የተመሰከረለት። ስለዚህ ችቦውን ስታዩ፡ ወደ ሰውነታችሁ ተመለሱና የእግዚአብሔር ትእዛዝ በመጠበቅ ማብራት አለማብራታችሁን መርምሩ። እግዚአብሔር ለጨለማው ዓለም መብራት እንኾን ዘንድ በክርስቶስ ክርስቲያን ብሎ ከብርሃናዊው አምላክ ብርሃን ሲያሳትፈን እኛ ግን የዚህን ዓለም ርካሽ የጨለማ ሐሳብ ይዘን አልላቀቅ አልን። እንኳንስ ለሌላው ለራሳችንም ማብራት አቅቶን በዘረኝነት፣ በጥላቻ፣ በትዕቢት፣ በስንፍና እና በመሳሰሉት ጨለማዎች ውስጥ ተሸሸግን። ለዓለም ችቦ መኾን ሲገባን ጨለማ ኾንን። ብርሃን በማጣት ለጨለመችው ዓለም ተጨማሪ ጨለማ ኾነን ጨለምተኝነቷን አሰፋነው። እንግዲህ እርሱ እግዚአብሔር በቸርነቱ ወደ እውነተኛ የክርስትና ሕይወት እንድንመለስ የሚያደርግ ኀይል ያድለን አሜን!
862 views19:19