2022-07-12 17:26:29
" የዮና ልጅ ጴጥሮስ ሆይ ደምህ በመስቀል ጽዋ ተቀዳ የጳውሎስ ደም ደግሞ ወደ ሰማያት ጮኸ
ቅዱስ ያሬድ
" ክርስቶስ ለደቀ መዛሙርቱ በዚህ ዓለም ሳሉ ብቻ ሳይሆን ከሞቱ በኃላ እንኳ እንዲያበሩና እንዲሠለጥኑ አድርጓቸዋል ።እስኪ ንገረኝ የታላቁ እስክንድር መቃብር የት አለ ? እንዲሁም የሞተበትን ቀን እስኪ ንግረኝ የክርስቶስ አገልጋዮች ግን መቃብራቸው እንኳ ሳይቀር የተከበረ ነው ያረፉበት ቀንም በሚገባ የታወቀ ነው ዕለተ ዕረፍታቸውም በዓለሙም ሁሉ የበዓል ቀን ሆኖ ይከበራል "
ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ
እንኳን ለቅዱሳን ሐዋርያት ለቅዱስ ጴጥሮስ እና ቅዱስ ጳውሎስ ዓመታዊ መታሰቢያ ክብረ በዓል በሰላም አደረሳችሁ!!!
ሁለቱ ቅዱሳን ሐዋርያት ቅዱስ ጴጥሮስ እና ቅዱስ ጳውሎስ መድኃኒዓለም ኢየሱስ ክርስቶስ ለሰማያዊ አገልግሎት በድንቅ አጠራሩ የጠራቸው ናቸው በማቴ 4 ፣18 እንደተጻፈ ቅዱስ ጴጥሮስ ከወንድሙ ቅዱስ እንድርያስ ጋር ሆኖ ዓሳ በማጥመድ ላይ እያለ ጌታ ኑ እና ሰዎችን የምታጠምዱ አድርጋችኃለው ሲላቸው መረቡን ትቶ የተከተለ ቅዱስ ሐዋርያ ነው በሐዋ 9፣14 እንደተጻፈ ቅዱስ ጳውሎስ ክርስቲያኖችን ለማሳደድ ከሊቀ ካህናቱ የፍቃደ ደብዳቤ ይዞ በደማስቆ ሲያልፍ ጌታ ለሐናንያ እንዳለው በአህዛብ እና በነገሥታት በእሥራኤል ልጆች ፊት የጌታን ስም ይሸከም ዘንድ የተመረጠ እና የተጠራ ምርጥ ዕቃ ነው ።ለተጠሩለት አገልግሎትም እስከ መጨረሻው ታምነው እስከ ምድር ዳርቻ ሄደው ወንጌልን በብዙ ትጋት ያስተማሩ ቅዱሳን ናቸው የቤተ ክርስቲያናችን ጌጥ ቅዱስ ያሬድ በዝማሬው ይሄንን ሲገልጽ እንዲህ ይላል
" ቅድመ ዓለም የነበረ ዛሬ የለ ወደ ፊትም ዓለምን አሳልፎ ለዘለዓለም የሚኖር የእግዚአብሔር ቃል ስምዖን ጴጥሮስንና ጳውሎስን መምህራን አድርጎ ለሰማያዊ ሥራ ሾማቸው ሂዱ አስተምሩ በስሜ ስበኩ አላቸው ከዚያ ትምህርታቸው በዓለም ሁሉ ተሰማ "
ቅዱስ ጴጥሮስ ዓሳ የሚያጠምድበትን መረብ ትቶ ክርስቶስን የተከለበትን የአገልግሎት ጥሪ በምድር ላይ ፈጽሞ ወደ አምላኩ በክብር የሚሄድበት ጊዜ ሲደርስ በዘመኑ የክርስቲያኖች ጠላት የነበረው የሮም ንጉሥ ወደ አካይያ ዘምቶ ድል አድርጎ በደስታ ወደ ሮሜ ሲመለስ መኳንንቱን ለማስደሰት፤ ጣዖታቱንም ለማክበር ሲል በቅዱስ ጴጥሮስና በሌሎችም ክርስቲያኖች ላይ የሞት ፍርድ ዐወጀ፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስም በሮም ሲያስተምር ቆይቶ የሮም መኳንንት እንዳይገድሉት ትጥቁን ለውጦ ከሮም ሲወጣ ጌታችን መስቀል ተሸክሞ ተገለጸለት፡፡
በዚህ ጊዜ ‹‹አቤቱ ጌታ ሆይ ወዴት ትሔዳለህ?›› ሲል ቢጠይቀው። ጌታችንም ‹‹ልሰቀል ወደ ሮም እሔዳለሁ›› አለው፡፡ ‹‹ዳግመኛ ትሰቀላለህን?›› ባለው ጊዜም ‹‹አንተ ስትፈራ ጊዜ ነው ›› ሲል መለሰለት፡፡ ያን ጊዜም ‹‹ጐልማሳ ሳለህ ወገብህን ታጥቀህ ወደ ወደድከው ትሔድ ነበር ስትሸመግል ግን እጅህን ታነሣና ሌላ ሰው ያስታጥቅሃል፤ ወደማትወደውም ይወስድሃል፤›› ዮሐ 21፣18 በማለት ጌታችን የነገረው ቃል አሟሟቱን የሚያመለክት መሆኑን አስታውሶ ወደ ሮም ተመልሶ ስብከቱን ቀጠለ በሮማውያን እጅም ወደቀ ። እንደ ሥርዓታቸውም ቅዱስ ጴጥሮስን ከገረፉት በኋላ ሊሰቅሉት ሲሉ ወታደሮቹን ‹‹እንደ ክብር ንጉሥ እንደ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ አቁማችሁ ሳይኾን፣ ዘቅዝቃችሁ ስቀሉኝ›› አላቸው ቅዱስ ያሬድ በድጓው " ጴጥሮስ ወደ መስቀል ፊት ተመለከተ እንዲህም ሲል ጸለየ እኔ ወደ መስቀል መውጣትን ለምን እታክታለሁ ለምን እሰንፋለሁ ሲል ቁልቁል ይሰቅሉት ዘንድ ጠየቀ" እንዳለ
እነርሱም እንዳላቸው አድርገው ሐምሌ 5 ቀን ዘቅዝቀው ሰቅለውታል፡፡ በመስቀል ላይ ሳለም ተከታዮቹን በሃይማኖታቸው እንዲጸኑ ካዘዛቸው በኋላ ነፍሱን ለእግዚአብሔር ሰጠ፡፡
ብርሃን ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ በደማስቆ ሳለ የተጠራበትን አገልግሎት የጌታ ምርጥ ዕቃ ሆኖ ፈጽሞ ሲጨርስ ወደ አምላኩ በክብር የሚሄድበት ጊዜ ሲደርስ የሮም ንጉሥ ኔሮን ቄሣር የክርስቲያኖች ቍጥር እየጨመረ የመጣው በቅዱስ ጳውሎስ ትምህርት በመማረካቸው ምክንያት መኾኑን ተረድቶ፤ ይልቁንም የቤተ መንግሥቱ ሰዎች ሳይቀር በቅዱስ ጳውሎስ በመማረካቸው ተቈጥቶ ቅዱስ ጳውሎስን ወደ ፍርድ ሸንጎው አስቀረበው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም በቀኝ እጁ ከሰንሰለቱ ጋር መስቀሉን ይዞ ንጉሡንና ወታደሮችን ሳይፈራ የኢየሱስ ክርስቶስን የእግዚአብሔር ልጅነትና አምላካዊ ሥልጣን ይመሰክር ነበር፡ንጉሡም በቍጣ ይሙት በቃ ፈረደበት። ወደሚገደልበት ስፍራ ሲወስዱትም በንግግሩና በአስተያየቱ ሁሉ ምንም ፍርኀት አይታይበትም ነበር፡፡ እንዳውም በጦርነት ድል አድርጎና ማርኮ እንደ ተመለሰ ወታደር ይደሰት ነበር እንጂ፡፡ ለሚገድሉትም ይቅርታን ይለምን ነበር፡፡
በገዳዮቹና በተከታዮቹ ፊትም የክርስትና ሽልማቱ የእግዚአብሔር መንግሥት መኾኑን የሚያስገነዝብ ቃል እያስተማረ እግዚአብሔር የሚሰጠውን የጽድቅ አክሊል ለመቀበል ይቻኮል ነበር ፡፡ ወታደሮች ሊገድሉት ሲወስዱትም ከንጉሥ ኔሮን ወገን የኾነችውን የአንዲት ብላቴና መጐናጸፊያ ‹‹ዛሬ እመልስልሻለሁ›› ብሎ ከተቀበላት በኋላ ‹‹መልካሙን ገድል ተጋድያለሁ፤ ሩጫዬን ጨርሻለሁ ሃይማኖቴን ጠብቄአለሁ፤ ወደፊትም የጽድቅ አክሊል ተዘጋጅቶልኛል፤›› በማለት ራሱ በመልእክቱ እንደ ተናገረው ፊቱን በብላቴናዋ መጐናጸፊያ ተሸፍኖ አንገቱን በሰይፍ ተቀልቶ አገልግሎቱን በሰማዕትነት ፈጽሟል፡፡
" ቅዱስ ጴጥሮስ የሃይማኖት ዐለት ነው ቅዱስ ጳውሎስ ልሳነ ምዑዝ ነው በታወቀች በዓላችሁ የምሕረት አሥራታችሁን ያዙ " ብሎ ቅዱስ ያሬድ በዝማሬው እንዳመሰገናቸው በእነዚህ በከበሩ ቅዱሳን ሐዋርያት የዕረፍት ቀን ጌታ ለሀገራችን እና ለህዝቦቿ ምሕረትን ያደርግ
https://t.me/Ortodox_Mezmure
150 viewsedited 14:26