Get Mystery Box with random crypto!

ጭፍን እምነትን አውልቃችሁ ጣሉ ምንጭ ፦ የፍልስፍና ሀሁ ፀሀፊ ፦ በላይ ደስታ መሪር ሀሳቦችን | ኑ እናንብብ

ጭፍን እምነትን አውልቃችሁ ጣሉ

ምንጭ ፦ የፍልስፍና ሀሁ
ፀሀፊ ፦ በላይ ደስታ

መሪር ሀሳቦችን ለማንሳትና ለመወያየት ካልደፈራችሁ? ሗላ ቀር የሆነውና ከቤተሰቦቻችን የወረስናቸው ልማዶችና አስተሳሰቦች እርስ በእርስ አባልተው ይጨርሱናል፡፡ ስለእውነት ነው የምላችሁ፣ እንደሰው ተፈጥረን እንደድመት የምናልፍ ከንቱዎች እንሆናለን። በየጎጡ ጎራ እየሰራን እንለያያለን:: እምነታችን ሁሉንም የዓለም ህዝብ ካልቀየረ ብለን አክራሪነት ውስጥ ተቻኩለን እንወተፋለን። በንቁ ሀሳባችን ካልተመራን፣ ያው መሪያችን ልማድ ሆኖ መቅረቱ ግልጽ ነው፡፡

በሀሳብ፣ ልማድና እምነት መካከል ሰፊ ርቀት አለ፡፡ በሀሳቡ የሚያምን ሰው ይልቃል። በእምነቱ የሚያምን ግን አዲስ ሀሳብ አይፈጥርም፡፡ ቀድሞ የተፈጠረውን ስርዓት ተቀብሎ ወደ ልጁ ሰፈር ያደርሳል። እንደዱላ ቅብብል ማለት ነው። የዱላ ቅብብል ተወዳዳሪ ስለዱላው ምንም የሚያስበው የለም፡፡ ዱላው ብረት ይሆን እንጨት አያስብም። የሱ ስራ፣ ከኋለኛው አጋሩ የተቀበለውን ዱላ ይዞ ወደ ፊት መሸምጠጥ ብቻ ነው። ከዚያ ከፊቱ ለሚጠብቀው ሯጭ እስኪያቀብል ሳያባራ ይሮጣል፡፡

በእምነትና በባህላዊ ስርዓት ውስጥ የሚኖሩ ህዝቦችም እንዲሁ ናቸው። ከአባቶች የወረሱትን እምነትና ትዉፊት የሙጥኝ ብለው ወደፊት ይሮጣሉ። ለቀጣዩ ትዉልድ እስኪያስረክቡና ህይወታቸው እስኪያልፍ የሚያስቡት አዲስ መንገድ አይኖርም፡፡ አእምሯቸው በጥልቀት እንዲያስብ ፈቃድ አይሰጡትም፡፡ ለዚህ ነው፣ ብዙ እምነት ውስጥ የሚኖሩ ህዝቦች ስልጣኔን የሚሸሹት።

እምነትን ብቻ የሁሉ ነገር ምንጭና መንገድ አድርጎ የሚቆጥር ህዝብ ያየለበት ማህበረሰብ ወይም ሀገር፣ ኋላቀርነቱ እዚያው ኋላ እንደቀረ የሚኖር ይሆናል። ትልቁ ፈተና ደግሞ፣ እምነት ውስጥ የተኛ ህዝብ ኋላ ቀርነቱን እንደጸጋ ማየቱ ነው፡፡ የትኛውም የኑሮ ገጠመኝ ማለትም ድህነት፣ አለመማር፣ አለማወቅ፣ የበታች መሆን፣ ስደት፣ በሽታ፣ ጦርነትና መሰል እልፍ ወረርሽኞች እግር ተወርች አስረውት ጭምር አያዝንም፡፡ እልህ ውስጥ አይገባም፡፡ ለምን እንዲህ ተፈተንኩ ማለትን አይፈልግም፡፡

"የፈጣሪ ፈቃድ ነው ብለን ዝም አልን” በሚል የተለመደ ዋሻ ውስጥ ይደበቃል፡፡ ይህን ለማረጋገጥ፣ ዛሬም ወደ ራሳችን ማየት ነው፡፡ እየወደቅንም ፈጣሪ የምንለውን ሀይል አመስጋኞች ነን። ብንራብ፣ ብንጠማ፣ ፈተናዎች ቢደራረቡብን፤ ጦርነት ውስጥ ብንናጥ ሁሌ እያመሰገንን እናልፋለን፡፡ ለምን በዚህ ሁኔታ ውስጥ ገባን? እንዴትስ መውጣት እንችላለን? ብለን አንጠይቅም። ምክንያቱም "ሁሉም ነገር የፈጣሪ ፈቃድ ነው” በሚለው ራሳችንን እናታልላለንና።

መፍትሔ የምንጠብቀው ከጸሎትና ከፈጣሪ ነው። እጆቻችንን ወደ መሬት አዙረን መዶሻና አካፋ አንይዝም፡፡ ምንም ሳንይዝ አየሩ ላይ ወደ ሰማይ አንጋጠን እንለምናለን። በዛ ጥፋታችን ለፈረሰ ቤት ጥገና የምንጠይቀው ፈጣሪን ነው:: ይህ መንገድ ለሁሉም ነገር መፍትሄ አይሆንም፡፡

ፍጹም አማኝ ሆኖ የተሰባሰበ ህዝብ ስልጣኔ የማይሰራው ለምን እንደሆነ ግልጽ ነው። የተሰባሰበው ሰማያዊ መንግስትን እያሰበ እንጂ፣ በእጁ የጨበጠውን የምድር ህይወት ከግምት አያስገባም፡፡ እየኖረ በመሆኑ ግን፣ የግድ መንግስት ይፈጥራል። የሚፈጥረው የመንግስት አይነት ግን ምድር ላይ ያለውን እውነት ያማከለ አይሆንም፡፡ የተዘበራረቁ መልኮች ይኖሩታል፡፡

የራሱን የህይወት መንገድ እንዲፈጥር ነጻነትን ያልተማረ ህዝብ፣ ጥያቄ አይጠይቅም፤ የተለየ ሀሳብም አያስብም፡፡ ሀሳብ የሚያድገው ደግሞ በፍልስፍና ነው ! በፍልስፍና አስተሳሰብ ያልተገራ ህዝብ በነጻነት ውስጥ ሆኖ የእውቀት ልዩነት የሚፈጥር የሀገር ቅርጽ አይወልድም፡፡ በጥንት ልማድና አሁን ባለው የሀገር ቅርጽ መሃል የተለየ ማንነት አይኖርም።

በልማድና በእምነት ውስጥ ብቻ የሚኖር ህዝብ አንደኛው ችግር ይኼው ነው፡፡ ከዘመን መለወጥ ጋር የሚያድግ ርዕዮት አይፈጥርም፡፡ የእርሱ ጉዳይ ዶግማዎችን እንዳሉ ማስቀጠል ነው፡፡ የባህል ዱላ ቅብብል ላይ የተገደበ ስርዓት ነው የሚፈጥረው፡፡ ባህል ግን ብቻውን ስልጣኔ አይሆንም ፤ ስልጣኔንም አያመጣም፡፡ ባህል የቡድን ባህሪ እንጅ የግለሰብ አስተሳሰብ አይደለም፡፡ የሳይንስ ወይም የፍልስፍና ተግባር ደግሞ ዶግማዎችን ብቻ ማስቀጠል አይደለም።

ኢትዮጵያ ዘመናትን ያስቆጠሩ ሥነቃላዊና የፅሁፍ ፍልስፍናዎች ባለቤት ናት። ከአስራ ሰባተኛው መቶ ክፍለ ዘመን በፊት፣ ከሌሎች የአፍሪካ ሀገሮች በተለየ መልኩ በርከት ያሉ የፍልስፍና ስራዎችን በመስራት በቀዳሚነት የምትጠቀሰው በጥንታዊው የግእዝ ቋንቋ ከተጻፉት የፍልስፍና ስራዎቿ መካከል ከፊሎቹን በትውልድ ካናዳዊ፣ በምርጫ ደግሞ ኢትዮጵያዊ የሆነው ፕሮፌሰር ክላውድ ሰምነር ወደ እንግሊዝኛ ቋንቋ በመተርጎም፣ በዓለም አቀፍ ደረጃ እንዲታወቁ እድርጓል። ሌሎች በርካታ በግዕዝና በአረብኛ ቋንቋዎች የተፃፋ የጽሁፍ ስራዎች በጥንታዊ ቤተእምነቶችና ቤተመዛግብት ውስጥ ተቀምጦ አንስቶ የሚመረምራቸውን የሀገራቸውን ጠቢብ በመጠባበቅ ላይ ናቸው።

ፍልስፍና በጥቅሉ የተጻፉትንና በቃል ከትውልድ ወደ ትውልድ የሚተላለፋትን የማህበረሰብ ወጎች፣ ልማዶች፣ ጥበቦች፣ የእውቀት ዘርፎችንና አስተሳሰቦችን፤ በግለሰብ ፈላስፋዎች፣ በአንድ ዘመን ተሰርተው በጽሁፍ የተላለፉትን ስራዎች የሚመለከት ምጡቅ የጥበብ ዘርፍ ነው። በቃል ከትውልድ ወደ ትውልድ የሚተላለፉ ማኅበረሰባዊ ፍልስፍናዎች፤ በተረትና ምሳሌ፣ በምሳሌያዊ አነጋገሮች፣ በዘይቤዎች፣ በቅኔዎችና በወጎች ሊገለጡ ይችላሉ።

ሀገራችን ኢትዮጵያ፣ ገና ያልተጠኑ የበርካታ ጥንታዊ ስነ ጽሁፎች ባለቤት ናት፤ ማጥናትና መመርመር አቅቶን ሌሎች አጥንተው የቅጂ መብቱን ከመውሰዳቸውና የታሪክ ክፍትት ተፈጥሮ በመጪው ትውልድ ተወቃሾች ከመሆናችን ሰፊት፣ ከትምህርት ቤት ጀምሮ፣ በወጣቶች አዕምሮ ውስጥ የምርምር ሀሳቦችን በማንሳትና የዘርፉ ምሁራንም ተገቢውን ጥናትና ምርምር በማካሄድ፣ በየደረጃው ያሉ የትምህርት ተቋማትም፣ የፍልስፍና ጥበብን በትምህርትና በምርምር ስራቸው ውስጥ በማስገባት፣ ወጣቶች ከተለመደው አስተሳሰብ ወጥተው፣ በተለያዩ የፈጠራ አስተሳሰቦች ውስጥ እንዲመሰጡ ማበረታት ወቅቱ የሚጠይቀው አቢይ ስራ ነው፡፡

እየኖርን ባለነውም ሆነ ወደፊት በምንኖረው ዘመን፣ ለአንድ ሃገር አስፈላጊና ወሳኝ ነገሮች ናቸው ተብለው ከሚታመንባቸው ጉዳዮች መካከል፤ ለዘመኑ የሚመጥን የሳይንስ፣ የቴክኖሎጂና የፈጠራ ውጤት ሊያመነጭ የሚችል ተመራማሪ ትውልድ ማፍራት መቻል ነው፡፡ አዳዲስ የሳይንስ ግኝቶችንና የተራቀቁ የቴክኖሎጂ ውጤቶችን ሊያመነጩ የሚችሉ ጠይቂ አዕምሮዎች እንዲፈጠሩ ደግሞ፣ በነባሩ ባህላዊ አስተሳሰብ ውስጥ ያሉ ዜጎች፣ አዲሱ ትውልድ፣ የምርምር ሀሳቡን በሚያምንበት መንገድ ያለገደብ፣ እንዲያራምድና እንዲያዳብር መፍቀድ መቻል አለባቸው።

@Zephilosophy
@Zephilosophy