2022-07-02 10:36:48
ለ2 ቀናት ሲካሄድ የሰነበተው የምክክር ጉባኤ ባለ7 ነጥብ የአቋም መግለጫ በማውጣት ተጠናቀቀ!!
***
(ሰኔ 24 ቀን 2014 ዓ.ም
አዲስ አበባ-ኢትዮጵያ)
በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት አዘጋጅነት ከሰኔ 23-24 ቀን 2014 ዓ.ም ለ2 ቀናት በአብነት ት/ቤት መዳከም እና ፍልሰት እንዲሁም በመምህራኑ ትኩረት መነፈግ ዙሪያ ሲካሄድ የሰነበተው የአብነት ት/ቤት መምህራን የምክክር ጉባኤ ባለ7(ሰባት)
ነጥብ የአቋም መግለጫ በማውጣት በዛሬው ዕለት ተጠናቅቋል።
በምክክር ጉባኤው የአዲስ አበባ እና የጉራጌ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ መልከጼዴቅ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት በብዙ ችግሮችና ተግዳሮቶች የተተበተበ ሰለሆነ በአስተዳደራዊ ጉዳዮች ተጠምደን ስለነበር ሁኔታዎች ተመቻችተው እስካሁን ድረስ ሊቃውንቱን አላወያየናችሁም ነበር ብለዋል።
አክለውም የቤተክርስቲያንን ችግር ለመፍታት ከእናንተ በላይ ባለድርሻ አካል የለምና ወደፊት ችግሮችን በጥልቀት እና በተከታታይነት የምንፈትሽበት ሰፊ የምምክርና የውይይት መርሐ ግብር እናሰዘጋጃለን ሲሉ ብፁዕነታቸው ተደምጠዋል።
አሁን ሀገረ ስብከታችን እየተከተለ ባለው የውስጥ አሠራር የቤተክርስቲያንን ሊቃውንት ይቅርና የትኛውም ቤተክርስቲያንን ተጠግቶ የሚሠራ ሰው ባለበት ሥፍራ ተከብሮና ተረጋግቶ እንዲሠራ ማድረግ ነው ያሉት ደግሞ የሀገረ ስብከቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ ሊቀ ጉባኤ ቆሞስ አባ ተክለሃይማኖት ወልዱ ናቸው።
ለሁለት ቀናት በቆየው ጉባኤ አገልግሎት ተኮር የሆኑ ጥናታዊ ጽሁፎች ቀርበው ውይይት ተደርጎባቸዋል።
በጉባኤው ተሳታፊ መምህራን በኩል የቤተክርስቲያንን አስተምህሮና ዕውቀት ከማስቀጠል አንጻርና ተገቢውን ትኩረት ከአለማግኘት አንጻር በርካታ ጥያቄዎች ተነሥተው፣ በሀገረ ስብከቱ ሊቀጳጳስ እና ዋና ሥራ አስኪያጅ ምላሽ ተሰጥቶባቸዋል።
በመጨረሻም አጠቃላይ የጉባኤው ኩነቶች የተዳሰሱበት ባለ 7 ነጥብ የአቋም መግለጫ በመ/ብ ሳሙኤል ደምሴ የሀገረ ስብከቱ ሰበካ ጉባኤ ማደራጃ ዋና ክፍል ኃላፊ ተነቦ በብፁዕነታቸው ጸሎት ጉባኤው
ተፈጽሟል።
ሙሉ የአቋም መግለጫው ከዚህበታች እንደሚከተለው ቀርቧል፦
የአቋም መግለጫ
1. ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ቆማና ጸንታ የቆየችው በሊቃውንት የእምነት ጽናት፣መንፈሳዊ ሕይወት መሆኑ ይታመናል፡፡ በመሆኑም ለወደፊት የጉባኤ መምሕራንን ያሳተፈና ያካተተ አሠራር በሀገረ ስብከቱ በኩል እንዲሰፍን እየጠየቅን፣ አሁን በትምሕርትህ ማሰልጠኛ ዋና ክፍል ለተደረገው ሊቃውንቱን የማወያየት ተግባር ምስጋናችንን እናቀርባለን፡፡
2.ሌሊት በማሕሌት፣ ቀን በፍትሐት በትርፍ ሰዓታችን ደግሞ ደቀ መዛሙርቱን በማፍራት እየደከምን የመምሕራኑ ደመወዝ ካስተማርናቸው ዲያቆናት ከድጋፍ ሰጪ ሠራተኞች ማነሱ የሊቃውንቱን ሞራል የሚነካ አገልግሎቱን የሚያዳክም ስለሆነ የደመወዝ እስኬል እንዲሰራልን እንጠይቃለን፡፡
3. ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እስካሁን የቆየችው ያለደመወዝ ወንበር ዘርግተው ጉባኤ አስፍተው ባሉ መምሕራን መሆኑ ይታወሳል፡፡ በመሆኑም እኛ በአዲስ አበባ የምንገኝ የጉባኤ መምሕራን በተመደብንበትና በተማርነው ሙያ ጉባኤ ዘርግተን ለማስተማር ቃል እንገባለን፡፡
4. ሳይማሩ የሊቃውንቱን ስም የሚወስዱ በዕውቀት በተራቀቁ ሊቃውንት ስም የሚጠሩ ለሙያው ያለውን ክብር የሚያሳጣ ሊቃውንትም ክብራቸውን የሚያሳንስ ስለሆነ ለወደፊቱ እንዲህዓይነቱ ስም ባልተሰጣቸው ሥልጣን የሚሰጡ አገልጋዮች እርምት እንዲሰጣቸው እየጠየቅን ብፁዕ አባታችን አቡነ መልከ ጼዴቅ ለገዳማትና ለአድባራት አባታዊ መመሪያ በጽሑፍ እንዲያስተላልፉልን በታላቅ አክብሮት በልጅነት መንፈስ እንጠይቃለን፡፡
5.ድጓውን፣ ቅኔውን አቋቋሙን ዝማሬ መዋስዕቱን እንደባጣ ቆይኝ የሚቆጥሩትን፣ ሳይማሩ ተምረናል የሚሉትን በስማችን የሚነግዱትን፣ ድምጽ ማጉያ የሚዘጉትን በማስተማር፣ በመምከር የበኩላችንን ጥረት በማድረግ ማሕሌቱ እንደጥንቱ ለካህናትና ለምዕመናን ተደማጭ ለማድረግ በጋራ እንሰራለን፡፡
6. በቤተ ክርስቲያናችን የማስመስከሪያ ጉባኤ ቤቶች በቅዱስ ሲኖዶስ የተወሰነ የታወቁና ጥንትም የነበሩ ናቸው፡፡ አሁን ግን በየደብሩ የሚሰጡ የአብነት መምሕራን ምስክሮች አግባብ ካለመሆኑም ሌላ የሊቃውንትን እውቀት የሚያሳንስ ስለሆነ ይሕ እንዲታረም እየጠየቅን፣ በማሕሌት ወቅት የማሕሌቱን ክብር የሚያሳንስ የከበሮ አመታት ዘይቤ እንዲስተካከል በጋራ ለመሥራት ቃል እንገባለን፡፡
7. ሊቃውንት በዶግማ በቀኖና ቤተ ክርስቲያን በአጠቃላይ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ጉዳይ በመሳተፍ የመወሰን ድርሻ ስላላቸው አስፈለጊ መሆኑ ታምኖበት አዲስ አበባ ሀገረ ስብከት በማዕከል ያለ የሊቃውንት መገኛ በመሆኑ ለወደፊት በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ደረጃ ጉባኤ ተዘጋጅቶ በገጠር ላሉ መምሕራን ጭምር የመፍትሔ ሀሣብ ለማቅረብ እንድንችል መርሐ ግብር እንዲመቻችልን እየጠየቅን ይህንን ባለ 7 የአቋም መግለጫ አውጥተናል፡፡
ሰኔ 24 ቀን 2ዐ14 ዓ.ም.
40 viewsKalkidan cherent, edited 07:36