2022-06-06 16:57:43
ከዐረብ ጥላቻ ጀርባ
~~~~
ድሮ ድሮ ህዝባችን ለዐረቦች ውዴታም አክብሮትም ነበረው። ህዝባችን ሙሐመድ ዐረብ፣ ዐረቡ፣… እያለ ልጆቹን መሰየሙ ለዐረቦች የነበረውን ከፍ ያለ ቦታ አመላካች ነው። እንዲያውም ይህን አክብሮቱን ለክፉ አላማ የሚጠቀሙበት አካላት ነበሩ። "ዐረብ ነን" እያሉ የነገሱበት፣ ያሻቸውን የፈፀሙበት በታሪክ ብዙ ናቸው። ይህ ሁሉ ለዐረቦች ካለው ከፍ ያለ አክብሮትና ግምት የተነሳ ነበር።
ዛሬ ትላንት አይደለም። በዐረብ ጥላቻ የሰከሩ ከሃዲያን ፕሮፓጋንዳ ብዙ ሙስሊሞችን ሸርሽሯል። ዛሬ በዐረብ ጥላቻ ያበዱ ብዙ ሙስሊሞችን እናገኛለን። ሌባው፣ ቀማኛው፣ ዝሙተኛው፣ ፈሪው፣ ጨካኙ ፣ … በቃ ክፋት ሁሉ የተሰባሰቡበት ፍጡር ዐረብ ነው አንዳንዱ ዘንድ። የሃገራችን የኢኽዋን አስተሳሰብም ለዚህ የጥላቻ ተውሳክ የራሱ ድርሻ አለው።
ብቻ ዐረብ እንደማንኛውም ፍጡር ነው። ክፉም ደግም አለው። ክፉዎች በውስጡ ስለኖሩ በጅምላ ልንጠላውም፣ ልናወግዘውም ፍትህ አይደለም። ያውም እኛ! በየትኛው መመዘኛ ነው ከነሱ የምንሻለው? ሌቦቻችን ከሌቦቻቸው፣ ዘረኞቻችን ከዘረኞቻቸው፣ ጨካኞቻችን ከጨካኞቻቸው፣ ፈሪዎቻችን ከፈሪዎቻቸው፣ ባለጌዎቻችን ከባለጌዎቻቸው፣ መሀይሞቻችን ከመሀይሞቻቸው፣… ይበዛሉ ይከፋሉ እንጂ አያንሱም አይሻሉም።
ደጎቻቸው፣ ጀግኖቻቸው፣ አዛኞቻቸው፣ ምሁሮቻቸው፣… ከኛዎቹ የበዙም የበለጡም ናቸው። ይሄ የትላንት ታሪካቸውን ቀርቶ የዛሬ ኑባሬያቸውን በጥልቀት ያስተዋለም በቀላሉ የሚያገኘው ሐቅ ነው። ዐረብ ሃገር ስንቱ ነው በነፃ የሚታከመው? ስንቱ ነው በነፃ የሚማረው? ስንቶች ናቸው በሐጅ ፣ በዑምራ፣ በረመዳን ዘርፈ ብዙ እርዳታዎችን የሚያከፋፍሉት?
በሃገራችንስ በዐረብ ለጋሶች ስንቱ አቅመ ደካማ ፣ የቲም፣ ስንቱ ዱዓትና መሻይኽ ነው የሚደጎመው? ስንት መስጂድና መድረሳ ነው የተገነባው? ስንት መንገድ፣ የውሃ ጉድጓድ፣ የህክምና ተቋም፣ … ተሰርቷል። ከዐረብ ሐገር በመጡ የህክምና ቡድኖችና በዐረብ እስፖንሰሮች እልፍ አእላፍ ህዝብ ታክሟል። በመቶ ሺህ የሚቆጠር ህዝብ (ምናልባት በሚሊዮንም ሊሆን ይችላል) በዐረብ ሃገር እየሰራ እራሱን፣ ወገኑን አልፎም ሃገሩን ይህን ያክል ነው ተብሎ በማይገመት መጠን ደጉሟል። ዐረብ ሃገር ለኢትዮጵያ ሙስሊሞች መሸሻም ነው። በአረመኔዎች የተሳደደው፣ ለደህንነቱ የሰጋው ሁሉ የሚኮበልለው በአብዛኛው ወደ ዐረብ ሃገር ነው።
እውነቱ ይህ ከሆነ ቅናት ካልሆነ በስተቀር ዐረብን በጅምላ እንድንጠላ የሚያደርገን ምን ምክንያት አለ?! መጥፎ ትርክቶችን እየነቀሱ የሚያራግቡ ምቀኞች ሴራ ሰለባ አንሁን። አዎ ዐረብ ውስጥ የደካማ ሐቅ የሚበላ፣ ለሌሎች ንቀት ያረገዘ፣ ጨካኝ፣ ቦቅቧቃ፣ ክፉ፣ ወዘተ አለ።
የኛስ ሰው ከነዚህ እንከኖች ነፃ ነው? ግብረ ገብነታችን፣ ባህላችን ተንኮታኩቶ የት እንደደረስን እያየንኮ ነው። ኧረ ያገር ቤቱ ይቅር። የኛ ሰው በዐረብ ሃገር ስንት መጥፎ ነገር እየፈፀመ አይደለምንዴ? እርስ በርስ አይገዳደልም? ቪዛ ቆርጦ ለስርቆት የሚኳትን የለም?! አረቄ፣ ሀሺሽ የሚያከፋፍል የለም? የሴት ድለላ ላይ የተሰማራ የለም?! የአገርን ገፅታ የሚያቆሽሹ ሰላም ወዳዱ ሐበሻ የሚሳቀቅባቸው ስንት ጥፋቶች አይፈፀሙም? ልጆቻቸው በሰራተኞች አልተገደሉም? እኛ ስለነሱ እንደምናወራው እነሱም ስለኛ የሚያወሩት ብዙ አላቸው።
•
ግን ለምንድን ነው የነሱ ጥፋት ገኖ የሚታየን?አዎ ምክንያቱ ወዲህ ነው። ምክንያቱ እነሱን ከፍ አድርገን መጠበቃችን ነው። በዚህ የተነሳ ከኛ ጃሂል የነሱ ጃሂል፣ ከኛ በዳይ የነሱ በዳይ፣ ከኛ ባለጌ የነሱ ባለጌ፣ ከኛ ጨካኝ የነሱ ጨካኝ ይጎላብናል፤ ይገንብናል። የተሻለ ቦታ ስለምንጠብቃቸው እነሱ ዘንድ የሚታየው ጋጠ ወጥነት እኛ ዘንድ ካለው የበለጠ ይረብሸናል። ይሄ እንጂ እውነት እነሱ ከኛ ብሰውም ከፍተውም አይደለም።
ሌሎቻችን ደግሞ የኢስላም ጠላቶች ፕሮፓጋንዳ ሰለባ ሆነናል። በተለያዩ ስልቶች ህዝባችን ውስጥ የዐረብ ጥላቻ እንዲጨምር ሳይታክቱ ይሰራሉ። ከዐረብ የምናገኘውን ጥለው የሚደርስብንን፣ የምንፈፅምባቸውን አልፈው የሚፈፅሙብንን ያራግባሉ። ወደ ዐረብ ሃገራት የሚሰደዱ ዜጎች የሃገርን ገፅታ ከሚያጠለሹ ተግባራት እንዲቆጠቡ ከማሳሰብና ከማስተማር ይልቅ በጥቂት ዐረቦች የሚፈፀሙ ጥቃቶችን ማስጮህ ላይ ይረባረባሉ።
እነሱ ዐረብን ቢያብጠለጥሉ አላማ አንግበው ነው። ብዙ የእምነታችንን እሴቶች የዐረብ ባህል አድርጎ በማቅረብ እየሸራረፉ ከሃይማኖታችን ሊያለያዩን ያምራቸዋል። በፈረንጅ ልብስ እያጌጡ ኢስላማዊ አለባበሳችንን በዐረብ ባህልነት በመፈረጅ ሊያጣጥሉ ይሞክራሉ። በአይሁድ ስም እያሸበረቁ የዐረብኛ ስሞቻችንን ጥለን "እርገጤ"፣ "ጎንጤ" እንድንሆን ያባብሉናል።
ወንድሜ ከያንዳንዱ ጩኸት ጀርባ ያደፈጡ ሴራዎች አሉ። ለወገን በመቆርቆር ስም መቅረባቸው ሽፋን ብቻ ነው። ያኔ ትዝ ይልሀል ወገኖቻችን ተፈናቀሉ ተብሎ ሳር ቅጠሉ ሲቆጭ? በደርግ ጊዜ ስንትና ስንት ዐረብ ንብረቱን ጥሎ ከሃበሻ መባረሩኮ ሩቅ አይደለም። ሁሉንም ልክ ነው ወይም ስህተት ነው ብየ ልመዝን አይደለም። ግን የኛን ቅዱስ የነሱን እርኩስ የማድረጉ አባዜ ሰበቡ ከተራ ጥላቻ ያለፈ ነው።
እንጂማ በሰው ሃገር ሰልፍ የወጣው፣ መኪና የሰባበረው ወገናችን ታፍሶ ሲገባ ምን እንደደረሰበት እናውቃለን። የጠበቀው የአበባ ጉንጉን አልነበረም። በመጣ በወሩ እግሩ በመራው አገር እያቆራረጠ መሰደዱ የሚያስተላልፈው መልእክት ከግልፅም በላይ ነው።
አንዳንድ እራሱን እንኳን የማያውቅ ጥራዝ ነጠቅ አለ። ፀረ ዐረብ እሳቤው ሲሞገት "ዐረቦች ድሮ ነበር እንጂ ዛሬ ዘቅጠዋል" ይላል። "አመድ በዱቄት ይስቃል" አሉ። ማን ያልዘቀጠ አለ?! "ድሮ ድሆች እንጂ ባለጌዎች አልነበራችሁም። አሁን ግን ድሃም ባለጌም ሆናችሁ" ተብሎ በፈረንጅ የተተረተብንኮ እኛ ነን።
ብቻ እርግጠኛ ሁን! ይሄ በሶሪያና በግብፅ ዐረቦች የተጠመቀ አካል አምስት አመት ከቀጠቀጠው ጣሊያን በላይ የትላንት ባለውለታውን ዐረብን የሚጠላበት ምክንያት ኢስላምና ዐረብን የአንድ ሳንቲም ሁለት ገፅታ አድርጎ በመሳሉ ነው። እትብቱ በተቀበረባት ሃገር ነፃነት የተነፈገው ሙስሊም በዐረብ ድጋፍ እምነቱን እንዳይማር፣ ንቃተ ህሊናውን ከፍ እንዳያደርግ፣ አቅሙን እንዳያጎለብት የሚሰጉ ኃይላት ብዙ ናቸው። እኛን ከወንድሞቻችን ጋር ሆድና ጀርባ ሊያደርጉ የማይፈነቅሉት ድንጋይ የማይምሱት ጉድጓድ የለም። ስለዚህ ንቃ!! ቆም ብለህ ተመልከት። (በመጨረሻም የምነግርህ ቢኖር ከዚህ ፅሁፍ የተረዳሀው "ዐረብ ፍፁም ነው፣ አይሳሳትም፣ …" እንዳልኩ ከሆነ በአረዳድህ ቁንፅልነት ከማዘን ውጭ ምንም ልረዳህ አልችልም።)
=
(ኢብኑ ሙነወር፣ ግንቦት 29/2011)
የቴሌግራም ቻናል
https://t.me/IbnuMunewor
270 viewsكوني زوجة صالحة تقية, 13:57