Get Mystery Box with random crypto!

ደብረ ዘይት፡- ዳግም ምጽአት ዘመነ ሥጋዌ የጌታችን መገለጥ ለመጀመሪያ ጊዜ የተመለከትንበት፣ ይህ | ማኅበረ ቅዱሳን ዋናው ማእከል

ደብረ ዘይት፡- ዳግም ምጽአት

ዘመነ ሥጋዌ የጌታችን መገለጥ ለመጀመሪያ ጊዜ የተመለከትንበት፣ ይህም ከሰማያት ወርዶ እኛን ለማዳን ከንጽሕት ቅድስት ድንግል ማርያም ከሥጋዋ ሥጋ ከነፍሷ ነፍስ ነሥቶ ሰው በመሆን ዓለምን ያዳነበት ነው፡፡ እርሱ እንደ ሰው ተወልዶ፣ እንደ ሕፃናት በጨርቅ ተጠቅልሎ፣ ጡት ጠብቶ፣ በየጥቂቱ አድጎ፣ በአጭር ቁመት በጠባብ ደረት ተወስኖ፣ በእግር ተመላልሶ፣ እንደ ሰው ተርቦና ተጠምቶ፣ ኀዘን መከራን ተቀብሎ በፍጹም ፍቅሩ አድኖናል፡፡

ፈውሰ ነፍስ በሆኑት ትምህርቶቹ ዓለምን አጣፍቶ፣ አዳኝ በሆኑት እጆቹ ልምሾዎችን፣ ድዊዎችንና አንካሶችን አድኖ፣ ጎባጣን አቅንቶ፣ የዕውራንን ዓይን አብርቷል፡፡ የእግዚአብሔር አንድያ ልጅ መሆኑንም በፈለገ ዮርዳኖስ በመጥምቀ መለኮት እጅ ተጠምቆ አስመስክራል፡፡ ብርሃነ መለኮቱ በታየበት በደብረ ታቦር ተራራም አምላክነቱን ገልጧል፡፡ (ማቴ.፫፥፲፫-፲፯፣፲፯፥፩-፰)

ይህን ሁሉ ያደረገው ሰዎች አምላክነቱን አውቀን፣ ከሰማየ ሰማያት የወረደውና መከራን ተቀብሎ በመስቀል ላይ የሞተው ለእኛ ድኅነት መሆኑን እንዲሁም ድንቅ ሥራውን የፈጸመበት ይህን ጥበቡን ተረድቶና፣ የእጁን ሥራ፣ የቃሉን ተእምራት ያመነውን ሁሉም እንደሚድነን ሲያበስረን ነው፡፡ በተጓዳኝም በመዋዕለ ስብከቱ ስለ ዳግም ምጽአቱና ምልክቶቹ በደብረ ዘይት ተራራ ላይ በዝርዝር በደቀ መዛምርቱ በኩል አሳውቆናል፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ማርቆስ በወንጌሉ እንዲህ ይገልጸዋል፡፡ (ማር.፲፫፥፫-፴፯)