Get Mystery Box with random crypto!

++ በሰንበት መፍረስ ++ የኢያሪኮ ሰዎች የሠራዊት ጌታ የእግዚአብሔርን ኃይል በመናቃቸው ምንኛ | መርጌታ ሚካኤል የበሀል ህክምና

++ በሰንበት መፍረስ ++

የኢያሪኮ ሰዎች የሠራዊት ጌታ የእግዚአብሔርን ኃይል በመናቃቸው ምንኛ ተጎዱ?! እርሱ ዓለምን የፈጠረ መሆኑን ስላላመኑ እንዳልተፈጠሩ የሆኑት የኢያሪኮ ሰዎች መጨረሻ እጅግ አሳዛኝ ነበር፡፡

ቅጥራቸው ከመፍረሱ በፊት እስራኤል የእግዚአብሔርን ታቦት ይዘው ለስድስት ቀናት ያህል በዝምታ ኢያሪኮን ዞሯት፡፡ ዓለምን በስድስት ቀናት የፈጠረውን ጌታ እንዲያስተውሉ ስድስት የዝምታ ቀናት ተሠጧቸው፡፡ በሰባተኛው ቀን ግን ጮኹ የኢያሪኮም ቅጥር ፈረሰ፡፡

ሰባተኛ ቀን የዕረፍት ቀን ነው፡፡ ለኢያሪኮ ግን የመፍረስ ቀን ሆነባት፡፡ ሰባተኛ ቀን ፈጣሪን ለሚያምኑ የተቀደሰ ቀን ነበር ፤ ለኢያሪኮ ግን የመረገም ቀን ሆነባት፡፡
እግዚአብሔር የፈጠረው ሁሉ መልካም እንደሆነ ባየበት ሰባተኛ ቀን ኢያሪኮ ግን ከፉ እንደሆነች ታየባት፡፡

እግዚአብሔር የሌለበት ሕይወት እንዲህ ነው፡፡ ወዳጄ እግዚአብሔር በሕይወትህ ውስጥ ከሌለ የሰንበት ቀን የነፍስህ ዕረፍት ቀን መሆኑ ይቀርና እንደ ኢያሪኮ የመፍረስ ቀን ይሆናል፡፡ በዚያ ቅዱስ ቀን ቅጥርህን በመጠጥ ፣ ብስካር ብዝሙት ስታፈርስ ትውልና ታድራለህ፡፡ ራስህን አንድደህ ትሞቃለህ ፤ እያራገብህ ትቃጠላለህ፡፡ ታቦት ይዘው ቢዞሩህም የኃጢአት ግንብን አጥረሃልና አትሰማም፡፡ በላይህ ላይ ቢቀደስብህም እንደ ኢያሪኮ ሰዎች ካህናቱን እያየህ ‘ዝም ብሎ መዞር ምንድር ነው?’ እያልክ ትስቃለህ፡፡ የካህናቱ የቅዳሴ ዜማ ለአንተ የሚያፈርስ ጩኸት ይሆንብሃል፡፡ የኢያሪኮ ሰው ከመሆን ፣ በሰንበት ፈራሽ ከመሆን ያድንህ!

ቅዳሴያችን መካከል ካህኑ ዕጣን እያጠኑ ዞረው ሲመለሱ የዚህች አጭር ጽሑፍ መነሻ ሃሳብ የሆነውን ይህንን ጸሎት ይጸልያሉ፦ አምላካችን እግዚአብሔር ሆይ አስቀድመህ በባሪያህ በነዌ ልጅ በኢያሱ እጅ የኢያሪኮን ግንብ እንዳፈረስከው የእኔንና የሕዝብህን የኃጢአታችንን ግንብ አፍርሰው፡፡

ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ
ለተጨነቀች ነፍስ ዕረፍት የሆነው የእግዚአብሔር ቃል ለሁሉ ይዳረስ ዘንድ ጸልዩ! ሌሎች እንዲያነቡትም የሚከተሉት አድራሻዎች Like እና Share ያድርጉ