Get Mystery Box with random crypto!

የመጋቤ ምሥጢር መሠረት ተሰማ የንባብና ዜማ ትምህርት ሕይወት ፤ በራሳቸው አንደበት ሲተዘት ፨፨፨፨ | መንፈሳዊ ግጥም ብቻ

የመጋቤ ምሥጢር መሠረት ተሰማ የንባብና ዜማ ትምህርት ሕይወት ፤ በራሳቸው አንደበት ሲተዘት
፨፨፨፨፨፨፨፨፨

አርታኢ ወአስተጋባኢ፦ዲ/ን ከሣቴብርሃን ገ/ኢየሱስ


መንደርደሪያ

ታኅሣሥ ፳፪ ቀን 2013 ዓ.ም
ከኮሮና አመጣሽ የዘጠኝ ወር አሰልቺ እረፍት መልስ የተጀመረው ትምህርት እየተጧጧፈ ያለበት ጊዜ በመሆኑ እኔም ሆነ ወንድሜ አብነት የተወጣጠረ ጊዜ ላይ እንደነበርን አስታውሳለሁ።
ይህ አስቸጋሪ ወቅት ሊቁ መምህራችን እንደልብ ለመጠየቅ አላስቻለንም። እንዲህ ባለው ጊዜ ነው እንግዲህ “ባስቸኳይ እፈልጋችኋለሁ” የሚል መልእክት በልጅ ልጃቸው ዲያቆን ናታን በኩል የተላለፈልን።

እንዲህ ያለ አስቸኳይ ጥሪ ስላልተለመደ ወዲያው ወደ ቤታቸው ሄድን። ከሳሎኑ ስንገባ ከሳሎኑ ስንገባ በተለመደ ሞቅ ያለ ሰላምታ ተቀበሉን። እንደሌሎቹ ጊዜያት ግን ትንሽ ትልቅ በማይመርጥ ትኅትና ቆመው ለማስተናገድ ቤት ያዋላቸው መጠነኛ የእግር ሕመም አላስቻላቸውም።
ከዚህ በኋላ ያሉን ነገር ቃል በቃል አይረሳኝም።

“እንግዲህ ነገ የሚፈጠረው ነገር አይታወቅም። እናንተ የመጨረሻ ልጆቼ ናችሁ። ይኼን ሁሉ ጊዜ ደክማችሁ አንድ ነገር ብሆን ልፋታችሁ ከንቱ ሆኖ እንዳይቀር የተማራችሁትን ዘርዝራችሁ ጽፋችሁ እንድታመጡልኝና የምስክሩን ወረቀት እንድሰጣችሁ ነው የጠራኋችሁ። እሱን ከያዛችሁ እንግዲህ አቅም እስከፈቀደና ነፍስ እስክትወጣ ድረስ ትቀጥላላችሁ።” ነበር ያሉን።

በጊዜው ንግግሩ ከማስደንገጥ ይልቅ አስገርሞን ነበር። ”ትንሽ እግራቸውን ያዛቸው እንጂ አሳሳቢ የሆነ የጤና እክል አልገጠማቸውም። ለምን እንዲህ አሉ?” ብለን ግራ እንደ መግባት አለን። ወዲያው ግን መምህር ደረጀ ከ4 ወይም ከ5 ወር በፊት የጉባኤ ቤታቸውን(በኋላ መካነ መቃብራቸውን) ሁኔታ እንዲመለከትና ጥገናም ያስፈልገው እንደሆነ እንዲያየው ያደረጉትን ነግሮኝ “እኚህ አባት ምን ታይቷቸው ነው?” ያለኝን አሰብኩና “ምናልባትም ለበቁ አበው ቀድሞ የሚሰጥ ነገር አለ።” በሚል እምነት የታዘዝነውን ግዴታ ፈጽመን ከ2 ቀን በኋላ ታኅሣሥ ፳፬ ቀን የምስክር ወረቀቱን ይዘን ሄድን። ጽሕፈቱን በሚገባ ተመልክተው ሁሉም ሳይጓደል መካተቱን ካረጋገጡ በኋላ “የደብሩ ሰበካ ጉባኤ ማኅተም በቅድሚያ ማረፍ አለበት። ሂዱና አስመቱ” ብለውን ያንን አስደርገን ከሁለት ቀን በኋላ ተመልሰን በመምጣት የራሳቸውን ማኅተምና ፊርማና ማኅተም አኑረውልን ሁለቱን ኮፒ ለእኛ ቀሪውን ሁለት ኮፒ ለራሳቸው ካስቀሩ በኋላ እንዲህ አሉ።

“እንኳን ደስ አላችሁ። ይኼን በብዙ ድካም የጨረሳችሁት መንፈስ ቅዱስ ስላበረታችሁ ነው። እኔም ደግሞ በተጋድሎ ሳይሆን ሥራዬ ግዴታዬ ስለሆነ ጤንነት ሰጥቶኝ እኚህን ዓመታት (5 ዓመታት) ማንም የማያገኝውን ዕድል መንፈስ ቅዱስ ሰጥቷችሁ ተማራችሁ። ወንጌልን ብቻ ለመማር አምስት ዓመትም የማይጨርሱ አሉ። እናንተ ግን ሐዲሳትን ሙሉ ትርጓሜያቸውን ከብሉይ የዳዊትን ትርጓሜ አጠናቃችሁ እንዲያውም ቅዳሴንና ሃይማኖተ አበውን ጨምራችሁ እዚህ ደርሳችኋል። ታዲያ እናንተ እዳ አለባችሁ። ‘በከንቱ የተቀበላችሁትን በከንቱ ስጡ’ ይላልና ቃሉ።”
ይኼን ካሉ በኋላ ለእኛ በከንቱ የሰጡትን ዕውቀት በከንቱ የሰጧቸውን መምህራን ሊዘረዝሩ ፣ የአብነት ትምህርት ሊተርኩ ገቡ። እኔም ይኼንን እንደወረደ ምንም ማሻሻያና ጭማሪ ሳላደርግ አቅርቤዋለሁ።
ልክ መንግሥቱ ለማ ለ48 ሰዓት ከሊቁ አባታቸው ጋር ያደረጉትን ቃለ መጠይቅ ምንም ሳይጨምሩ ቃል በቃል “መጽሐፈ ትዝታ ዘአለቃ ለማ ወልደ ታሪክ” ብለው እንዳሳተሙት በተለይ የመጋቢን አንደበተ ርቱዕነትና የቋንቋ አጠቃቀም ፣ የጊዜውንም መንፈስ በሚገባ ያሳያልና ይልቁንም በEOTC TV ላይ ከተላለፈላቸው በራሳቸው አንደበት ከተገለጠው የሕይወት ታሪክ አንጻርም ዘርዘር ያለ ገለጻ ያለው በመሆኑ ሰፊ ግንዛቤ ያስጨብጣል ብዩ አምናለሁ። ከዚህ ቀጥሎ ያለው ሙሉ በሙሉ የእሳቸው ቃል ነው።



ተቀምጦ ማስተማር

እኔ ለአባቴ ለአስተማሪዬ ትንሽ ልጅ ሆኜ እንደ በኵር እንደ በኵረ ተማሪ እቆጠር ነበር። የመጽሐፍ መምህሬን። እጃቸውን ይዤ አብሬያቸው ተቀምጬ ነበር ምውል። ያ ነው አሁን እኮ ተቀምጦ ተማሪዎችን ለማስተማር የረዳኝ የልጅነቴ ጊዜ ሁኔታ ነው።
ያኔ መቀመጥ ያልተማረ ልቅሶ መሄድ ሠርግ መሄድ ሚያበዛ ዛሬ መቀመጥ አይችልም። እኔ ልቅሶ አልሄድም። ሠርግ አልሄድም።የታመመ አልጠይቅም። የታሠረ አልጠይቅም። አስተማሪ ነኝ አስተምራለሁ።



ንባብ ዜማና ቅኔ

ስንት መምህራን ዘንድ ተምሬያለሁ? ንባብ ከተማርኩባቸው መምህራን የመጀመርያው የተከበሩ አባት መምሬ ዳምጤ ገብረ ጊዮርጊስ ናቸው። ከፊደል ጀምሮ ዳዊት ያስደገሙኝ። በጥቂት ጊዜ ውስጥ። “እንደገና ዳዊት ደግሞ መከለስ አለብኝ እነ አርጋኖን እነ ሌሎችም ንባብ ማስፋፋት አለብኝ” ብዬ ያስተማሩኝ ክቡራን አባቶቼ መምሬ ሣህሌ አባ ፋንታዬ አባ ገብረወልድ ጠቅላላ ከእኚህ አራት አባቶች ዘንድ ንባብ ከጨረስኩ በኋላ እዚያው የተወለድኩበት ሃገር አንጎለላ መጣሁ። እንደ እድሌ ሆኖ ከንባብ በኋላ በዜማ ቤት በመጽሐፍ ቤት ያስተማሩኝ መምህራን ዓይነስውራን ናቸው። ሦስቱ።
ከዚያ አሁን ዜማ ፤የቤተልሔም ዜማ ይባላል፤ የኔታ ምትኬ ዘንድ። አባቴ እንድማርለት ይወዳል። እዚያችው ቤተክርስቲያን አጠገብ አክስት አሉኝ ፤ ወይዘሮ አስካለ ገብረሕይወት የሚባሉ ፤ እንደ በግ እየጠበቁኝ ሲያገኙኝ እዚያው ሲያገኙኝ
“አለ?”
”አዎ”
“ይማራል?” እያሉ እየተቆጣጠሩኝ የኔታ ምትኬ ጋር ቀጸልኩ።
ዓይነ ሥውር ናቸው የኔታ ምትኬ። ከየኔታ ምትኬ ዘንድ ደግሞ ጾመ ድጓ ጀመርኩና የቃል ትምህርት የሚባል አለ። መስተጋብዕ። ከሰኞ እስከ ዓርብ ድረስ። ጾመ ድጓ ጀምሬ ልጆች እንሂድ ሲሉ ጅሩ ዳዋ የሚባል ሃገር አለ ሃገራችን። ዳዋ ኢየሱስ ይባላል። አለቃ ወልደ አብርሃም ዘንድ። አለቃ ወልደ አብርሃምም ዓይነ ስውር ናቸው። እሳቸውም ደግሞ ዘንድ ጾመ ድጓ ስናጋምስ እንሂድ ተባለና በጌምድር ። ጎንደር ማለት ነው። ሰሜን ጎንደር። ገና ዓባይን ሻገር ስንል ምክሬ ማርያም የምትባል አለች። እሷ ጋር የኔታ ይኄይስ የሚባሉ አሉ። በጣም በጣም በጣም ግሩም የሆኑ መምህር ናቸው። መንደር ሰጥተውን እንደ ወንድሜ የሆነ ጓደኛዬ አለ። የማንለያይ። አብረን ስንሄድ ለእርሱም ስም ለእኔም ስም አውጥተው እሱን ዜናዊ እኔን ጸዳለብርሃን ብለው ሰይመው እኔን በተለይ ባለቤታቸውም ሆኑ እሳቸው በጣም ይወዱኝና ያቀርቡኝ ነበር።መምህር ናቸው። ጸሐፊ ናቸው። እማራለሁ እላቸዋለሁ።ለምሳ ሲገቡ “ና እንጀራ ብላ” ይሉኛል “አልበላም የኛ እንጀራ ምን ሁኖ ነው” እላቸኋለሁ። ያመጣላ ዜናዊም። በግድ ያስገቡኛል። እና እዚያ ሳልለይ ከማዕዳቸው ተምረን ጾመ ድጓ ዘለቅን። የቃል ትምህርት ክሥተት አርያም የሚባል አለ መወድስ ያንን ሁሉ ተማርንና እንደገና አሁን ደጋ ወጣሁ ጋይንት። ይኼ ቆላ ነው። አንዳቤት ይባላል። ሰሜን ጎንደር ነው ይኼም። ከዚያ ከአንዳቤት ምክሬ ሐናን ለቀቅሁና የጥጆ ማርያም የምትባል ዙርአምባ የሚባል የአቡነ አረጋዊ ገዳም አለ። ከዚያ በአፋዛዥ ናት። የገዳሙን ተራራ እንደዚህ እንደ ጭላሎ ተራራ ነው ምናየው። የሁለት ሰዓት መንገድ አይሆንም በእኛ አካሄድ። ሂጀ አልሳምኩም እዚያ። ጓደኛዬ ሄዶ “ዙርአማባ የተባለውን ዞረን አይተን መጣን።” ይለኛል። ግድ የለኝም እኔ። እንደ አጋጣሚ ሲሆን ብዙ ገዳሞችን ረግጫለሁ። “ይኼ ገዳም ማነው?” “እገሌ ይባላል” “ፍቀዱልን