2022-07-18 15:27:55
Well እንግዲህ
=============
በዛሬው ዕለት በነበረው የመጅሊስ ሁለተኛ ዙር ጉባዔ 14 የሥራ አስፈጻሚዎች ተመርጠዋል። ከነዚህም መካከል፦
①) ሸይኽ ሐጂ ኢብራሂም ቱፋ → ዋና ፕሬዝዳንት፣
②) ሸይኽ ዐብዱ-ል-ከሪም ሸይኽ በድረዲን ሸይኽ ሙሐመድ ሱሩር → ምክትል ፕሬዝዳንት፣
③) ሸይኽ ሐሚድ ሙሳ → ዋና ጸሐፊ፣
④) ሸይኽ ዐብዱ-ል-ዓዚዝ ወሌ → ምክትል ጸሐፊ ተደርገው ተመርጠዋል።
በቀጣይ 3 አመታት የመጅሊሱን ተቋማዊ ሰውነት እንዲያሳልጡ ኃላፊነት ተጥሎባቸዋል። ከጠቅላይ ም/ቤቱ ሆነው ለህዝቡ መግለጫ ይሰጣሉ ተብሎ ይጠበቃል።
እነዚህ የተመረጡ ሰዎች ላለፉት በርካታ አመታት ሲንከባለል የቆየውን የመጅሊስ ጉዳይ የተረከቡ ናቸውና ትልቅ ኃላፊነት ተሸክመዋል። በአላህ ፈቃድ የተጣለባቸውን አማና በአግባቡ ለመወጣት የበኩላቸውን ሚና ሊጫወቱ ይገባል። በአላህ ፈቃድ ህዝበ ሙስሊሙና መንግስትም ከጎናቸው ይቆማል።
በተረፈ ግን እስካሁን የነበረውን ነገር በኦዲት ከተጣራ በኋላ መረከብ አለባቸው። የተመረጡትን ኦዲት ለማድረግ እንዲመቸን ያለንን ንብረትና ያለብንን እዳ ማወቅ እንፈልጋለን። ተጠያቂ መደረግ ያለበት ካለም ይደረጋል። ኡማው በብዙ መልኩ ዋጋ ሲከፍል ኖሯልና የሚገባውን ሊያገኝ ግድ ነው።
እንደ መጨረሻ ለሌሎቻችሁ የምለው ቢኖር፤ አላህ ፈቅዶልን ይህ ቀን ተከስቷል። ነገር ግን እነዚህ በዛሬው ዕለት ከስልጣን የተነሱ ሰዎችን ደጋፊዎች እልህ ውስጥ ወደሚከትና ለጥፋት ይበልጥ ወደሚያነሳሳ ተራ መበሻሸቅ ውስጥ እንዳንገባ አደራ ለማለት እወዳለሁ። በመበሻሸቅ የምናተርፈው የለም። ይልቁንም ዛሬ ያገኘነውን ይዘን ያላገኘነውን ለማግኘት ወደመጣር መሸጋገር አለብን። እዚሁ ወረዳ ወርደን ድንጋይ ስንወራወር መቆየት የለብንም። ያባከናቸው አመታት ይበቁናል። ለወደፊቱ ጉዞ ወደፊት አሁንም በዱዓችን እንወጥር። በሳል አካሄዶችን እንሂድ። ጌታችን አላህ የሰጠንን እያመሰገንን ያጣነውን እንጠይቀው። አላህ ለሁላችንም መልካም ጊዜን ያምጣልን።
ወንድማችሁ፦ ሙራድ ታደሰ
========
ሐምሌ 11, 2014 E.C.
ዙልሒጃህ 19, 1443 H.C.
July 18, 2022 G.C.
||
t.me/MuradTadesse
twitter.com/MuradTadesse
384 views12:27