Get Mystery Box with random crypto!

#_የሰይጣን_ጠበቆች_አታርፉም_አታፍሩም! #_የመንገድ_ዳር_ሰይጣኖች! ሰይጣን ከሰው ለምን ወጣ | ቀሲስ ሄኖክ ወልደ-ማርያም

#_የሰይጣን_ጠበቆች_አታርፉም_አታፍሩም!

#_የመንገድ_ዳር_ሰይጣኖች!

ሰይጣን ከሰው ለምን ወጣ ብላችሁ ሰይጣናዊ ሰልፍ እንውጣ ትላላችሁ?

እሳቸውን ለመቃወም ፊርማ እንዳሰባሰባችሁ መተተኛ ደብተራዎችንም ለመቃወም ፊርማ አሰባስቡ!

በቀሲስ ሄኖክ ወልደ-ማርያም

ሼር በማድረግ ለወዳጆ አዳርሱ!

ተወዳጆች ሆይ ክቡር አባታችን መላከ መንክራት መምህር ግርማ ወንድሙ በአሜሪካ አትላንታ March 24-25 እና 26 ለሦሰት ቀን የሚቆይ ታላቅ ጉባኤ አላቸው። በጉባኤው ላይ እኔም እንድገኝና አብረን ምዕመናኑን እንድናገለግል ጋብዘውኝ ነበር። ነገር ግን እኔ በካሊፎርኒያው አገልግሎት ምክንያት አትላንታ ሄጄ ማገልገል አልቻልኩም። እጅግ በጣም የሚገርመው የእሳቸውን ጉባኤ ለማደናቀፍ፣ በመተት ወዘተ የተያዙት እንዳይድኑ የመንገድ ዳር ሰይጣኖች ብዙ መልፋታቸውን ሰምቼ አዘንኩ በእነሱም አፈርኩ።

ወዳጆቼ ሰይጣን ለምን ከሰው ወጣ ብለው ለሰይጣን ጠበቃ የሚቆምበት አሳፋሪ ዘመን ላይ ደርሰናል። ክፉ መንፈስ ከሰው ለምን ወጣ የሚሉ የመንገድ ላይ ሰይጣኖች ብዙ አሉ። ትዝ ይላቹኃል አባታችን አብረሃምን ሲፈትነው የነበረው የመንገድ ላይ ሰይጣን ነው።

ወደ አብርሃም ቤት ሰዎች ሄደው የአብርሃምን የእንግዳ ተቀባይነቱን በረከት እንዳይቀበሉ፣ በአብርሃም ቤት እንዳይበሉ፤ ሰይጣን መንገድ ላይ ተቀምጦ፣ እራሱን በምትሃት ለውጦ፣ ጭንቅላቱ የተፈረከሰ፣ ደሙ የፈሰሰ ሰው መስሎ "ወደ አብርሃም ቤት አትሂዱ ይኸው አብርሃም እንግዳ ከመጥላቱ የተነሳ መሃል እራሴን ፈንክቶኝ፣ ደሜን አፍስሶኝ" እያለ ሰዎች ወደ አብርሃም ቤት ለበረከት እንዳይሄዱ ይከላከል ነበር።

ዛሬም የመንገድ ዳር ሰይጣኖች አሉ። ዳር ይዘው በሰዎች የድኅነት መንገድ ላይ ቆመው አትሂዱ፣ አትጠመቁ፣ ቅብዓ ቅዱስ አትቀቡ የሚሉ ብዙ የመንገድ ዳር ሰይጣኖች አሉ። ሰይጣን ወደ አብረሃም አይቀርብም። መንገድ ዳር ቆሞ የመከላከል ሥራን ብቻ ይሠራል። አሁን ያሉትም የመንገድ ዳር ሰይጣኖች ወደ ምዕመናኑ ቀርበው "ችግራችሁ ምንድን ነው? ፈተናችሁ ምንድን ነው? ምንድነው የሚያስቸግራችሁ? ምንድን ነው የሚያሰቃያችሁ ወተዘ" ብለው አጠይቁም መንገድ ዳር ቆመው ይቃወማሉ በሰው ቁስል እንጨት ይሰዳሉ።

ሰዎች ወደ አብረሃም ቤት ሲሄዱ መንገድ ዳር ቆሞ አትሂዱ እያለ የሚከላከለው ሰይጣን አብርሃም የሚሠራውን ሥራ ስለማይሠራ ይቃወማል። "አብርሃም ክፉ ነው፣ ደግ አይደለም፣ አጥፊ ነው፣ ገዳይ ነው" እያለ ለሰዎች እንቅፋት ይሆናል። ዛሬም የታመመውን አያጠምቁ፣ ቅብዓ ቅዱስ አይቀቡ፣ በክፉ መናፍስት ተይዘው የሚሰቃዩትን አያገለግሉ፤ በሰዎች ሕመም፣ ስቃይ እና ችግር ፈተና ይሆናሉ፣ በቁስላቸውም እንጨት ይሰዳሉ። የመንገድ ላይ ሰይጣን እጅጉን ክፉ ነው። ምክንያቱም እውነትን ሐሰት አድርጎ ስለሚያቀርብና በሐሰት ስለሚከስ ነው።

ወዳጆቼ በሰይጣን ጥበብ፣ በመተት ትልቅ ቦታ የደረሰ፣ የሰይጣንን ውለታ የተቋደሰ ሰው ሰይጣን ሲነካ ደስ አይለውም። ሰይጣን ከሰዎች ሲወጣ ነፍሳችን ካልወጣ የሚሉት ወደው አይደለም። አፍንጫ ሲመታ ዓይን ያለቅሳል የሚባለው ትክልክል ነው። የሰው ሲለቅ የእናንተም ስለሚጨነቅ ስለሚሳቀቅ ነው።

ቆይ ሰው እንዴት የሰይጣን ጠበቃ ይሆናል? ሰይጣን ከሰው ለምን ወጣ የሚሉት እርግጠኛ ሆኜ የምነግራችሁ በአንድም በሌላም የሰይጣን ውለታ አለባቸው። ለዜማ፣ ለቅኔ፣ ለድምጽ፣ ለመጻሕፍት እውቀት፣ ለግርማ ሞገስ፣ አቃቤ ርዕስ/ለመጠበቂያ/ ወዘተ እያሉ ያስገቡት ቢቃወሙ አይደንቅም።

ግብረ ሰዶማዊነት፣ ሌዝቢያንነት በሕግ በተፈቀደበት ሀገር፣ የሰይጣን ቸርች ባለበት ሀገር፣ መላከ መንክራት መምህር ግርማ ወንድሙ በአትላንታ እንዴት ያገለግላሉ ብላችሁ ፊርማ ከምታሰባስቡ "ግብረ ሰዶም፣ ሌዝቢያንነት ይቁም" ብላችሁ ፊርማ አሰባስባችሁ ለምን አትቃወሙም? የሚደርስባችሁን ስለምታውቁ ዝም ጭጭ ትላላችሁ።

ከኢትዮጲያ ዘፋኝ መጥቶ ኮንሰርት ሲያዘጋጅ፣ ሰዉን ዳንኪራ ሲያስመታ "ዘፋኝነት ኃጢአት ነው፣ መጽሐፍ ቅዱስም ይከለክላል ስለዚህ የእከሌ ኮንተሰርት ላይ አትገኙ" ብላችሁ ለምን አትቃወሙም? ደብተራና ዘፋኝ እንደልብ በሚፏልልበት ሀገር አገልጋይ መጣ ብላችሁ መጮኃችሁ ያሳፍራል። ደብተራና ዘፋኝን ለመቃወም በነካ እጃችሁ ፊርማ ብታሰባስቡ መልካም ነበር።

አባታችን የሚያገለግሉበትን ቦታ ለማዘጋት ለማስከልከል የዘፋኞችንም አዳራሽ፣ የሰይጣንን ቸርች ለማዘጋት ለምን ተሰባስባችሁ ፊርማ አታሰባስቡም? ምነው በቤተ ክርስቲያን የተሰገሰጉትን፣ ትውልድ አማካኞችን፣ የሰው ዕድል ሰላቢዎችን፣ አውደ ነገሥት ገላጮችን፣ ሟርተኞችን፣ አጋንንት ጎታቾችን፣ መተት መታቾችን፣ በጥላ ወጊ ሰው ገዳዮችን ለመቃወም ፊርማ ብታሰባስቡ?

ክፉ መንፈስ ከሰው ሲወጣ የምትቃወሙት ደህና ነገር የወጣ መስሏችሁ ነው? የወጣውኮ ደህና ነገር አይደለም። በተለይ እኔ የታዘብኩት እዚህ አሜሪካ ያሉት የሰይጣን ጠበቆች ይገርማሉ። ሰይጣን በገሃድ በሚመለክበት፣ የሰይጣን ቸርች ባለበት፣ ለሰይጣን ባፎሜት ተብሎ ሐውልት በቆመበት ሀገር ሰይጣን የለም ይላሉ። የእኛዎቹ አገልጋይ ተብዬዎቹ ሰይጣን የለም ሲሉ ሰይጣን የሚስቅባቸው ነው የሚመስለኝ። እሱ አለሁ ይላል እነሱ የለም ይሉታል። እሱ ሰው ላይ እየጮኸ ይወጣል እነሱ ለምን ወጣ ብለው ከእሱ በባሰ ይጮሁለታል።

እኔ የሚገርመኝ ሰይጣን ከሰው ለምን ወጣ ብላችሁ እርር ምርር የምትሉት ሰይጣን እንኳን እንደናንተ ከሰው ሲወጣ አልተማረረም። ሰይጣን "ትላንት ከገነት አስወጥቻቸው ዛሬ ከሰው ሲያስወጡኝ፣ ከሰው ለምን ወጣህ የሚሉኝ እነዚህ ከእኔ ወገን ናቸው እንዴ?" እያለ ግራ የሚጋባ ነው የሚመስለኝ። ሰይጣን ከሰው ለምን ወጣ ብላችሁ ተባብራችሁ ስትጮሁ፤ ከሰው የሚወጣው ሰይጣን እንኳን እንደናንተ አይጮህም። ሰይጣን ከሰው ውጣ ሲባል በሰከንድ ጮሆ ይወጣል። እናንተ ደግሞ ሰይጣን ከሰው ለምን ወጣ ብላችሁ ሦስት ሰዓትና ከዛ በላይ በሚዲያ ትጮኃላችሁ። ጉድ እኮ ነው! እባካችሁ የምዕመናኑ የነፍስ ጠበቃ እንጂ የሰይጣን ጠበቃ አትሁኑ!

በጣም የሚገርመው አሜሪካ ከአንድም ሁለት ሥራ እየሠሩ ጠብ የማይልላቸው፣ አመድ አፋሽ የሆኑ በልፋት ብቻ የሚኖሩ እልፍ አሉ። ሠርተው ሳይሆን እጅጉን ለፍተው፣ ደም ተፍተው ገንዘብ ያገኛሉ። ገንዘባቸው ግን የት እንደሚገባ፣ የት እንደሚደርስ አያውቁም። ገንዘቡ እጃቸው ይገባል ሳያውቁት እጥፍ ሆኖ ይወጣል። እነዚህ ሰዎች እኮ በሰላቢ መተት የሚሰቃዩ ናቸው። ለፍተው ለሰው፣ ሠርተው ለሰው! እነሱ ከአንድም ሁለት ሥራ ይሠራሉ ሌሎቹ አንድም ሥራ ሳይሠሩ የእነሱን እየሰለቡ ይኖራሉ። ደግሞኮ የሚገርመው ደብተራው ያለው እዚሁ አሜሪካ መሆኑ ነው!

እውነት እናውራ ከተባለ በአሜሪካ በአውሮፖ የሰው ዕድል ለሰው የሚሰጡ፣ የሚለውጡ፣ የሚሸጡ ሀገር የፈቱ፣ ትዳር ያፋቱ፣ ሰውን በመተት ያንገላቱ፣ ቤተሰብን የበተኑ፣ የሰውን መልካም ዕድል ያመከኑ የሉም? መጽሐፍ ቅዱስ "የዲያብሎስን ሽንገላ ትቃወሙ ዘንድ" ይላል እናንተ ደግሞ ከመቃወም ትደግፋላችሁ። ከመደገፍም አልፋችሁ ለዲያብሎስ ጠበቃ ትሆናላችሁ። /ኤፌ 6፥11/