2023-07-04 15:19:23
ከብዙ ሥፍራ ብዙ ድንንጋይ ተወርውሮብናል፤
እኛ ግን የተወረወረብንን ድንጋይ ሰብስን ለነፍሳችን የሚሆኑ ጥሩ ጥሩ ሕንፃዎችን ገንብተንበታል።
በየቀኑም እየተሳሉ የሚወረወሩብን የጦር እና የገጀራ ቁጥሮች በርካታ ናቸው፤
እኛ ግን የሚወረወርብንን ጦር እና ገጀራ ወደ ማረሻ እና ወደ ማጭድ ቀይረን ልማት ላይ ነን።
በሚሳደቡን ሰዎች ስድብ አንድም ቀን ተበሳጭተን አናውቅም፤
ይልቁንስ ከሚሰድቡን ሰዎች ስድብ ውስጥ ምክርን እያወጣን ስድቡን ለምክር ተጠቅመንበታል።
ጉልበተኞቹ ገፍትረው ቢጥሉንም፤
እኛ ግን መውደቃችን አጋጣሚ ሆኖልን ከወደቅንበት ሥፍራ ብዙ ነፍሳትን ይዘን ተነሥተናል።
ጳውሎስ እና ሲላስም የወኅኒ ቤቱን ጠባቂ ከነቤተሰቦቹ አጥምቀው የሥላሴን ልጅነት ያጎናፀፉት እጅ እና እግራቸው ታሥሮ ወደ ወኅኒ ቤት ተገፍትረው ተጥለው በነበሩበት ወቅት ነው።
የሐዋርያት ሥራ 16
ስለዚህ ወዳጄ!
አንተም ተገፍትረህ ስትጣል ምናልባት እግዚአብሔር ባወቀ ከወደቅህበት ሥፍራ የምታነሣቸው በርካታ ነፍሳት ይኖራሉ እና ችግርህን እንደ መልካም አጋጣሚ ተጠቅመህ መልካም ሥራን እየሠራህ ለችግርህ ችግር ሁንበት እንጂ ዝም ብለህ በማጉረምረም ጊዜህን አታበላሽ!
ደግሞም በሐዋርያት ዘመን ለክርስትናው መስፋፋት
የነ እስጢፋኖስ መገደል ትልቅ ሚና እንደነበረው አትርሳ!
የእስጢፋኖስ መገደል ለአይሁድ በየሀገሩ መበትን ምክንያት ሆነ፤
የአይሁድ መበተን ደግሞ ለክርስትናው መስፋፋት መልካም አጋጣሚን ፈጠረ።
የሐዋርያት ሥራ 8 ፤ 1
ስለዚህ በክርስትና ሕይወት ውስጥ ችግሮችን ወደ መልካም አጋጣሚ ገልብጦ ሥራ ላይ ማዋል እንጂ ማለቃቀስ ብሎ ነገር የለም ወዳጄ!
ስትሰደድ በዚያ በተሰደድክበት ሥፍራ በወንጌሉ ቃል ልታጽናናቸው የሚገባ በርካታ ስደተኞች ይኖራሉ።
ስትታሠርም በዚያ በታሰርክበት ሥፍራ በወንጌሉ ቃል ከኃጢአት እሥራት የምትፈታቸው በርካታ እሥረኞች ይኖራሉ።
ስለዚህ ሁል ጊዜ፦
መንፈሳዊ ሕይወትህን ሊፈታተኑ ከዓለም ውስጥ የሚደርሱብህን ተግዳሮቶች ወደ መልካም አጋጣሚ የመቀየር መንፈሳዊ ብቃት ሊኖርህ ይገባል!
እንዲህ ስታደርግ
ችግሮች ለአንተ ችግር መሆናቸው ቀርቶ ለችግሮችህ አንተ ራስህ ችግር ነህ።
╭══•|❀:✞✟✞❀|•══╮
✥┈┈••●◉✞◉●••┈••✥
ከ መልአከ ኃይል ቀሲስ ኃይለመለኮት ግርማ ወንድሙ
27 /10/2015 ዓ.ም
ከሕይወት ተራራ ላይ መንፈሳዊነት ይብለጥ!
✥┈┈••●◉✞◉●••┈┈✥
╰══•|❀:✞✟✞❀|•══╯
3.3K views12:19