2022-02-20 00:34:49
ስብሃት ለአብ!!
-
«ለኔ ከስብሐት ደራሲነት ይልቅ ስብዕናው ጎልቶ ቢነገር የበለጠ ደስ ይለኛል። ምክንያቱም የስብሐት ውበት በስብዕናው፣ በሰውነቱ ይበልጥ ይጎላል» ማስታወሻ ገጽ 393 (ሚያዝያ 2006 እንደ አዲስ የታተመው)
ከተማ ገብቼ ስሜ ረዘመብኝ፣ ለእርድና አይመችም ብዬ ከስሜ ላይ «ለአብ» የሚለውን በፈቃዴ ቀንሼ ስብሃት ብቻ ሆንኩ ይላል ስለ ስሙ ሲናገር - ተጫዋቹ ስብሃት ገብረእግዚአብሔር። የፍስክ ጨዋታ አዋቂነቱ፣ ድፍረቱ እና ራሱን እንደድሮዎቹ ደራሲያን የማይቆልል መሆኑ ታላቅነቱ ላይ ጥላ አጥልቶበታል ብዬ አምናለሁ። ስለሱ ሲወራ አብዛኛው ወጣት የሚመጣለት ጨዋታዎቹ ናቸው።
*
ከመስታውት አራጋው ጋር በአንድ ስሙን የማላስታውሰው የኢንተርኔት ራዲዮ ላይ ሲጨዋወት «አሪፍ ሰው ምን ዓይነት ነው ላንተ?» ትለዋለች። ጋሽ ስብሃት «አሪፍ ሰው ማለት ብሽቅ ሰው ሲያጋጥመው አፍንጫውን በቡጢ የሚል ነው» ብሏት ያልፋል።
ሌላ ጊዜ ደግሞ ጋሽ ስብሃት ወደ ካዛንቺስ ብቅ ባለበት አጋጣሚ አንድ ትልቅ ቢልቦርድ ያያል። ቢልቦርዱ ላይ የወቅቱን «ኤድስን በጋራ እንከላከል» የሚል መፈክር የያዘ ነው አሉ። ጋሽ ስብሃት ዞር ብሎ አጠገቡ ለነበረው ሰውዬ፦
«እንዴት ነዉ ነገሩ? በጋራ ነው የነፋናቸው እንዴ?» ይለዋል። ይሄን ሰምተን ብዙ ስቀናል።
*
በቅርቡ ከዚህ ዓለም በሞት የተለየው ደራሲና ጋዜጠኛ ተስፋዬ ገ/አብ ስለ ስብሃት ሁለት ገጠመኞችን አጋርቷል፦
#አንድ
«የእፎይታ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ሳለሁ ደራሲ ስብሀት ገብረእግዚአብሔር አንድ ፅሁፍ ይዞልኝ መጥቶ ነበር። ማርያም ህፃኑን እየሱስ አዝላ ከፈርኦን ከሸሸች በኋላ ለሀያ አመታት ያህል ጣና ደሴት ላይ እንደተቀመጠች የሚገልፅ ውብ ልብወለድ ትረካ ነበር። ሳነበው ደስ አላለኝም። ወደ መቀመጫው ሄጄ ጠየቅኩት፣
«ምንድን ነው ይሄ ጋሽ ስብሀት?»
«ታሪክ ነዋ»
«እንዲህ መቀለድ ከአማኞች ጋር አያጋጨንም?»
«እኔ ጽፌያለሁ። መወሰን ያንተ ፈንታ ነው።» አለኝ።
ጥቂት አመነታሁ። ከዚያም በወቅቱ ምክትል ዋና አዘጋጅ ከነበረው ከመኩሪያ መካሻ ጋር መከርን። «ቁጣ ቢመጣ ስብሀት ላይ ነው» በሚል ተስማማንና ታሪኩ ታተመ።
ትዝ ይለኛል።
በነጋታው ከምሳ በፊት ጋዜጣዋ ተሽጣ አለቀች። ከዚያም አልፎ በጥቁር ገበያ እስከ አምስት ብር መሸጥ ጀመረች። ያኔ ዋጋዋ አንድ ብር ነበር።
በዚያን እለት ስልክ አጨናነቀን።
እንዲህ የሚሉ ቃላት ጎረፉ፣
«እፎይታዎች! ዛሬ አስደስታችሁናል። ታሪካችንን እንዲህ እየጎለጎላችሁ አውጡልን። ጋሽ ስብሀትን አመስግኑንልን! እንዲህ ነው ጋዜጠኝነት!! በርቱ!!»
በነጋታው ጋሽ ስብሀት ሲመጣ ለቡና ይዤው ወጣሁና የሆነውን ሳጫውተው አይኑን ጨፍኖ መሳቅ ጀመረ። ስቆ ስቆ ሲያበቃ እንዲህ አለኝ፣
«ህዝቡ ታሪኩን ካመነው ምናልባት ታሪኩ እውነት ሊሆን ይችላል።» በዚህ ጊዜ ግን የመሳቁ ተራ የኔ ሆነ።»
#ሁለት
«ለጋሽ ስብሐት ገብረ እግዚአብሔር ለስድስት ዓመታት ያህል አለቃዉ ሆኜ ብንሰራም በአንዳንድ ነገሮች ላይ እርሱ ነበር የሚያዘኝ። አንድ ቀን እንዲህ ሲል ጠይቆኛል።
«ላማክርህ ነበር የመጣሁት»
«እሺ ጋሽ ስብሐት ምን ነበር?»
«ገንዘብ ቸግሮኛል»
ዝም አልኩ። ምክንያቱም የመጪዎቹን ሁለት ወራት ደመወዙን ከወዲሁ ወስዶ ነበርና ምን እንደማደርግ ግራ ሊገባኝ ጀምሮ ነበር። እሱም ይህንን ተገንዝቦ ኖሮ ፈጥኖ ንግግሩን ቀጠለ።
«ደመወዜን ቀድመህ ስጠኝ ልልህ አልችልም። ወስጄዋለሁና። አሁን ሳስብበት ቆየሁና አንድ ሌላ ዘዴ መጣልኝ።»
«ምን ዘዴ አገኘህ ጋሽ ስብሃት?»
«ታታሪ ሰራተኛ በሚል ለምን ቦነስ አትሰጠኝም?»
* * *
የአንድ ደራሲ ስራዎች የደራሲው ማንነት ነፀብራቆች ናቸው። ለጋሽ ስብሐት ስራዎች ምንጭ ደግሞ የጋሽ ስብሐት ስብዕና ነው። ድንቅ ስብዕናን የታደለ ሰው ነው። ሰፌድን ሰፌድ ብሎ ለመጥራት ወኔው ነበረው ፥ በሐሰት ውዳሴ ሰው አያጅልም፥ አድር ባይነት አያውቀውም። የመረጠው መንገድ የሐቀኝነትን መንገድ ነው። ለዚህም ነው «የኤሚል ዞላን የአጻጻፍ ፈለግ ተከተልኩ» የሚለን። ሕይወትን ከነቡግሯ ሳትቀባባ ማስነበብ። እንደዚህ አይነት ጽሁፎች እኛው ራሳችን የምንኖረውን ሕይወት የሚያሳዩን በመሆናቸው ብዙ ላይስቡን ይችላሉ። የምንኖረውን ለምን እናነባለን የሚል ጥያቄ ያስነሳላ!! እውነተኛ ታሪክ የአንባቢውን ትኩረት እንዲያገኝ ልዩ የሆነ የሥነ ጽሁፍ ተሰጥኦ ይጠይቃል። ጋሽ ስብሃት ሁለቱን ነገሮች ተክኖባቸዋል።
*
አንዳንዶች ጋሽ ስብሐት የሀገራችንን ባህል በጽሁፎቹ ተጋፍቷል፣ አሳንሷል፣ አርክሷል በማለት ሲናገሩ ይስተዋላሉ። ይህ ለኔ የተንሸዋረረ አስተሳሰብ ነው። ከንባባችን ውስጥ የምናገኘው ቁምነገር ለማግኘት የምንፈልገውን ነገር ነው። ስለዚህ እነዚህ አንባቢዎች መልሰው ቢተቹትም የፈለጉትን ነገር ነው ያገኙት እላለሁ። አረዳዳችን ስናነብ የምንጠቀምበት «ሌንስ» ላይ ወይም ደግሞ ስናነብ ለማግኘት እየፈለግን ያለነው ነገር ላይ የተመሰረተ እንደሆነ አምናለሁ። በራሱ አገላለፅ «እኛ በድብቅ ያላደረግነውን ነገር አልጻፈም»። ጋሽ ስብሃትን በዚያ የሚከሱት ሰዎች ግብዞች ናቸው እላለሁ፤ ከአዝሙድና ከከሙን አስራት የሚያወጡ ነገር ግን ዋናውን ነገር የተዉ።
ገጣሚ ኑረዲን ኢሳም «ኢሻራ» በተሰኘው መድብሉ አንድ ግጥም ለርሱ መታሰቢያ አድርጓል፣ ርዕሱ «ከ`ዳ ሽሽት» ይላል።
ላንተ ለአዛውንቱ የቀለለችው ዳ
ለኔ ለወጣቱ እንደመርግ ከብዳ
እንዲህ ብዬ ፃፍኩኝ ስዳዳ ስዳዳ፤
“አይቶ የናዘረ
ያው አመነዘረ
ብሏልና ቄሱ መጽሐፉን ሲያስረዳ
ላይቀርልን ዕዳ
በይ ነይ እንባ . . .
*
አንድ የሱ «ማስተርፒስ» ነው የምለውን መጽሀፍ ለአብነት ላንሳ፤ አምስት ስድስት ሰባት።
የሀገራችንን ባህል፣ የአኗኗር ዘይቤ እና ነባራዊ ሁኔታ በጥልቀት ያሳየንን «አምስት ስድስት ሰባት»ን መቼም አንዘነጋውም። የዚህ መጽሃፍ ፍልስፍናዊ ይዘቱ የትየለሌ ነው። «በሴት ጉልበት እጦት» የተፈጠረውን የቤታቸውን ችግር «ሌሊት» እየተነሱ አቶ በርሱፈቃድ ወንድ ልጅ የማይሰራውን የእህል መፍጨት ስራ እንደሰሩ ይነግረናል። ነገር ግን አቶ በርሱፈቃድ የተሳሳቱት ነገር ነበር፤ ይህንንም ጋሽ ስብሓት እንዲህ ብሎ ይነግረናል «ሲያስቡት እጄም ወገቤም ሞፈር ለምደዋልና ከእፍረቱ በስተቀር ወፍጮ ምንም አያስቸግርም መስሏቸው ነበር። አልሆነም፤ እንዳሰቡት አልሆነም» ይለናል። ሴቶቹ ችለውት የኖሩትን ሸክም ጋሽ ስብሓት በሌሊት ያስቃኘናል። ከዚህም ባለፈ ያ የገበሬ ቤተሰብ (የአቶ በርሱፈቃድ ቤተሰብ) ከበሬአቸው ከሲሳይ ጋር ያላቸውን ቁርኝት ከዚህም የዘለለ እንደሆነ ይነግረናል።
አንድ ስሙ የተዘነጋኝ የማህበራዊ ሳይንስ ምሁር/ፈላስፋ በሰው ልጆች ሕይወት ውስጥ ሶስት አይነት ጥምረቶች አንዳሉ ይነግሩናል። እነዚህም የአሰሪና የሰራተኛ ጥምረት (አንዱ ስራ እንዲሰራለት ሌላው ገንዘብ ለማግኘት የሚያደርጉት ጥምረት)፣ የእኩሎች ጥምረት (ባልና ሚስት ዘር ለመቀጠል የሚያደርጉት ጥምረት) እንዲሁም የሰውና የእንስሳ ጥምረት (ለምሳሌ ገበሬው በሬው እንዲያርስለት እንዲሁም ሲብስበት ሊበላው ይፈልገዋል፣ በሬው ደግሞ ከአውሬ ስለሚጠብቀውና ስለሚቀልበው ገበሬውን ይፈልገዋል) ናቸው። ጋሽ ስብሐት ግን በዚህ ስራው በሃገራችን ያለው የሰውና የእንስሳ ጥምረት ከዚህ ያለፈ እንደሆነ ይነግረናል። አቶ በርሱፈቃድ በሬአቸው ሲሳይ ሲጎዳባቸው ተናደው ከገረፉት በኋላ እንዴት እንዳዘኑለት እና እንደተንሰፈሰፉ እንዲህ ሲል ይገልፅልናል « አቅፈው ሊያባብሉት አሰኛቸው. .
472 views21:34