Get Mystery Box with random crypto!

9.  በአገራችን የተጀመሩ ልዩ ልዩ ኘሮጀክቶች ፍትኃዊነት፣ እኩል ተጠቃሚነትና ሁሉን-አቀፍ ተደራሽ | Christian Tadele Tsegaye

9.  በአገራችን የተጀመሩ ልዩ ልዩ ኘሮጀክቶች ፍትኃዊነት፣ እኩል ተጠቃሚነትና ሁሉን-አቀፍ ተደራሽነትን ባረጋገጠ መልኩ በፍጥነት እንዲጠናቀቁ  የሚኒስትሮች ምክር ቤት ተገቢውን ቁጥጥር እንዲያደርግ እና ትኩረት  እንዲሰጥ ቋሚ ኮሚቴው ያሳስባል፡፡ የተከበረው ምክርቤት እና በስሩ ያቋቋማቸው ቋሚ ኮሚቴዎችም ተገቢውን የቁጥጥር ሥራ እንዲሰሩ ቋሚ ኮሚቴው ይጠይቃል፡፡

10.   አንዳንድ ኘሮጀክቶች ያለቅድመ አዋጭነት ጥናት እና የአካባቢ ተጽእኖ ግምገማ ወደ ሥራ በመግባታቸው የኢኮኖሚ አዋጭነት እና  የአፈፃፀም መጓተት ችግሮች እየፈጠሩ ስለመሆናቸው የፌዴራል ዋና ኦዲተር የክዋኔ ኦዲት ሪፖርቶች ያሳያሉ፡፡ ስለሆነም የሚኒስትሮች ምክር ቤት ልዩ ትኩረት ሰጥቶ የመንግሥት ኘሮጀክቶችን አቅዶ እንዲንቀሳቀስ ቋሚ ኮሚቴያችን ያሳስባል፡፡ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤትም በስሩ ባቋቋማቸው ቋሚ ኮሚቴዎች በኩል ኘሮጀክቶች በስትራቴጂክ እቅድ ተይዘው እና በበቂ ጥናት ተደግፈው ወደ ሥራ መግባታቸውን የማረጋገጥ ኃላፊነቱን እንዲወጣ እንጠይቃለን፡፡

ማጠቃለያ

በ2014 ዓ.ም የተከበረው ምክር ቤት የ2013/14 በጀት ዓመት የኦዲት ሪፖርትን ባዳመጠበት ወቅት ቋሚ ኮሚቴያችን ባቀረበው የማጠቃለያ አስተያየት መሠረት በፌዴራል ዋና ኦዲተር በሚቀርቡ ተከታታይ ሪፖርቶች በአንድ የምርጫ ዘመን ለ3 ጊዜ አስተያየት መስጠት ያልተቻለባቸው መስሪያ ቤቶችን እና የጎላ ችግር ያለባቸው ሆነው በመገኘታቸው ተቀባይነት የሚያሳጣ አስተያየት የተሰጠባቸውን መስሪያ ቤቶች በኃላፊነት የመሩ የሥራ ኃላፊዎች ለመንግሥት የሥራ ኃላፊነት የማያበቃ ገዳቢ ሆኖ እንዲያዝ የሚል ሐሣብ አቅርበን የተከበረው ምክር ቤትም በሙሉ ድምጽ የተቀበለው እና ያፀደቀው በመሆኑ፣ ይህንኑ የምክር ቤቱ ውሣኔ የሕግ መሠረት ለማስያዝ፣ በምክር ቤቱ እና በጠቅላይ ሚኒስቴር ጽ/ቤት ለሚፀድቁ ሹመቶች የመመዘኛ መስፈርት ደንብ ውስጥ እንዲካተት ቋሚ ኮሚቴያችን እያሳሰበ፣ የመንግሥት እና የሕዝብ ኃብቶችን በማስመለስ አጥፊዎችም በሕግ እንዲጠየቁ ይደረግ ዘንድ በአጽንፆት እንጠይቃለን፡፡