2022-07-14 23:29:18
እኔም አባ ባውማ በዚያ ቦታ ብቻዬን ቀረሁ ተመልሼም ወደ አባ አሞን በዓት ደረስሁ። ከዚያም የሦስት ቀን መንገድ ተጉዤ ወደ አባ ስምዖን በዓት ደረስሁ። ከዚያም ሦስት ቀን ተጉዤ ወደ ቦታዬ ወደ አስቄጥስ ገዳም ደረስሁ። ለመነኰሳቱም ሁሉ ያየሁትንና የሰማሁትን ሁሉ የቅዱስ አባ ኪሮስን ገድሉን ስለ አባ ሲኖዳም ዕረፍት ትንቢት እንደ ተናገረ ነገርኋቸው። መነኰሳቱም ሰምተው እጅግ አደነቁ የተመሰገነ እግዚአብሔርንም አመሰገኑት። እኔ አባ ባውማም የቅዱስ አባ ኪሮስን ገድሉን ጽፌ ለሚያነበውና ለሚሰማው ሁሉ መጽናኛ ይሆን
ዘንድ ወደ አብያተ ክርስቲያናት ሁሉና ወደ ገዳማትም ላክሁ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛን በአባ ኪሮስ በጸሎቱ ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
አባ ሚሳኤል፦ ይህም አባት አባ ኪሮስ የቀበረው የንጉሥ ልጅ ድኃ የነበረ ነው። ዜናውም እንዲህ ነው። አባ ኪሮስ በእግዚአብሔር ትእዛዝ ወደ ሳት ገዳም ሔደ። ከዚያም ደርሶ ቤተ ክርስቲያኒቱን ተሳለማት በዚያም አምላክን የወለደች የእመቤታችን የድንግል ማርያምን ሥዕል አየ። ከዐይኖቹም ዕንባ እያፈሰሰ "እመቤቴ ሆይ አስቢኝ" አላት ሥዕሊቱም "ኪሮስ ሆይ መምጣትህ መልካም ነው ከዚህም አትለፍ የአባትህን ዐፅም ትጠብቅ ዘንድ ወደ ማደሪያህ ተመለስ እንጂ" አለችው። አባ ኪሮስም ይህን ሰምቶ ከሥዕሏ ፊት ሰባት መቶ ሰግደትን ሰገደ። በዕብራይስጥም ቋንቋ "እንግዳ ነህና በቃህ በምሕረት መዝገብም ተመዝግቦልሃል" የሚለውን ቃል ሰማ።
ከዚያም በአለፈ ጊዜ መነኰሳቱ መልኩ የተዋበ ሁለመናውም ያማረ እንደሆነ ተመለከቱ። እርስ በርሳቸውም እንዲህ ተባባሉ "ይህ መነኵሴ ከመንግሥት ከተማ ከግብጽ አገር የመጣ ነው ሰውነቱ በጾምና በጸሎት አልጠወለገምና"። እጅግም ነቀፉት አልተቀበሉትም።ነገር ግን ወደ ሌላ ወደሚንቁት ቦታ ሰደዱት።
በዚያም መስፈርስ በሚባል ሕማም ለብዙ ጊዜ የታመመና በምድር ላይ የተጣለ ድኃ ሰውን አገኘ። በራስጌውም የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤልን በግርጌው ቅዱስ ገብርኤልን በቀኙም ቅዱስ ሩፋኤልን በግራውም ቅዱስ ሰዳካኤልን አየ። እነርሱም በክንፋቸው ጋርደውት ነበር ከሰውም ያለርሱ ያያቸው አልነበረም። "በገዳዩች ፊት ሞትን የማይፈራ ጐበዝ እንዴት ነህ" ብለው ሰላምታ ሰጡት። አባ ኪሮስም አደነቀ "በልዕልና ነዋሪዎች ሆይ ከዚህ ለምን ተቀመጣችሁ" አላቸው "ይህንን ድኃ እንድንጠብቀው ከእግዚአብሔር ታዘናል" አሉት አባ ኪሮስም "እስከ መቼ ነው" አላቸው። "ከዚህ ድካም እስከሚአሳርፈው ድረስ ነው" አሉት።
ከዚህም በኋላ ወደ ታመመው ደኃ ተመልሶ "በዚህ ቦታ ከኖርህ ምን ያህል ዘመን ነው" አለው በሽተኛውም "ሠላሳ አምስት ዓመት ነው" አለው ሁለተኛም "ከታመምክ ስንት ዓመት ነው" አለው "ሃያ ዓመት ነው" ብሎ መለሰ። "አበ ምኔቱና የገዳሙ መነኰሳት ይጐበኙሃልን" ብሎ ጠየቀው በሽተኛውም "አባቴ ሆይ የለም አይጐበኙኝም ፊታቸውን ከአየሁ ዓሥራ አምስት ዓመት ይሆናል" ብሎ መለሰ።
አባ ኪሮስም "ና ንገረኝ አባትህ ማነው እናትህስ ማናት" አለው በሽተኛውም እንዲህ ብሎ መለሰ "አባቴ የኬልቄዶን ንጉሥ እናቴም የራሕራሕ ንጉሥ ልጅ ናት። አባቴ ኪሮስ ሆይ እውነት እልሃለሁ በአባቴ ቤት ያሉ ሰዎች ወርቁንና ብሩን ቀጭኑንም ልብስ በእግሮቻቸው ይረግጡአቸዋል"። አባ ኪሮስም "ወደዚች ገዳም ማን አደረሰህ" አለው ድውዩም "እንዳንተ ያሉ ሁለት ሰዎች ወደ አባቴ ቤት መጥተው በዚያ አደሩ። እኩለ ሌሊትም ሲሆን ፊቱ ብሩህ የሆነ ሰውም ወደኔ መጣ "ሚሳኤል ብሎ ጠርቶ ሲነጋ ተነሥተህ ከእነዚህ ቅዱሳን ጋራ ሒድ" አለኝ በእንዲህ ያለ ሥራ ወጥቼ ወደዚህ ቦታ ደረስሁ ምንም በጎ ሥራ ሳልሠራም እንደ እነርሱ ሆንሁ"።
አባ ኪሮስም "እኔ አጽናናሃለሁና ወንድሜ ሆይ ስማ ስሙ በብኑዳ የሚባል አንድ እጅግ ድኃ የሆነ በበረሃ የሚኖር መነኵሴ ነበረ። የበጎ ሥራ ጠላት ሰይጣን ወደርሱ መጥቶ አሳተው እግዚአብሔርም ሥጋውን ለአንበሳና ለሰማይ ወፎች ሰጠ እርሱም በወገን የከበረ ከሮም ንገሥ በታች የሚገዛ የኬፋዝ ንጉሥ ልጅ ነበረ"። ሁለተኛም እነግርሃለሁ "የሮሜ ንጉሥ ልጅ የሆነ አንድ ድኃ ነበረ። እርሱም ከበትር ብቻ በቀር ከአባቱ ቤት ምንም ሳይዝ በቀስታ ወጣ ያንንም ሰው እኔ እጅግ አውቀዋለሁ። ከገዳም ወደ ገዳም ከተራራም ወደ ተራራ ይዞር ነበር ሞቱንም አላስተዋልኩም ሕይወቱንም አላወቅሁም"።
ዳግመኛም "አንድ የንጉሥ ልጅ ድኃ ነበረ። እርሱም በሰንበታት እነጂ በሌላ ቀን ምንም ሳይቀምስ ማቅ ለብሶ በቀንና በሌሊት ለጸሎት ይተጋ ነበር። በእንዲህ ያለ ሥራም ኑሮ አረፈ የብርሃን መላእክትም ነፍሱን ወስደው በመንግሥተ ሰማያት አኖሯት። አሁንም ወንድሜ የምነግርህን ስማ። የፈጣሪህ የእግዚአብሔርን ተግሣጽ አታድንቅ የወደደውን ይገሥጻልና" ያም በሽተኛ ድኃ መነኰስ "እውነት ነው ለእኔ ይገባኛል ስለ ኃጢአቴም ይህን ተቀበልሁ" ብሎ መለሰ። ይህንንም ብሎ ዝም አለ።
በዚያች ሰዓትም ያን በሽተኛ በሞት ያሰናብተው ዘንድ አባ ኪሮስ ወደ እግዚአብሔር ጸለየ። ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም በድንገት መጣ። እልፍ አእላፋት መላእክትም በዙሪያው ሆነው ከእርሱ ጋር ነበሩ ለጻድቃን ሞገሳቸውና ንጉሣቸው የሆነ አምላካችንን እናመስግነው ለችግረኞችም ተስፋ የሆነ አምላካችንን እናመስግነው እያሉ ይዘምሩ ነበር። በዚህ ዓለም በገድል የደከሙ በእርሱ ደስ ይላቸዋል።
አባ ኪሮስም በአየ ጊዜ በምድር ላይ ሰግዶ "ጌታዬ ፈጣሪዬ ሆይ ወደዚህ ምን አመጣህ" አለ ጌታችንም "ስለ ጠራኸኝ መጣሁ" አለው። አባ ኪሮስም "ይህ ሰው ፃዕር በዝቶበታልና ያርፍ ዘንድ አሰናብተው" አለው። ጌታችንም "ምን ያህል እንደምወድህ የመላእክት ሠራዊት ያዩና ያውቁ ዘንድ ይቺን የገነት ተክል አበባ ከእጄ ወስደህ በዚህ በሽተኛ በፊቱ ላይ ጣል" አለው። አባ ኪሮስም ያንን የገነት ተክል አበባ ከጌታችን እጅ ተቀብሎ በበሽተኛው ፊት ላይ አኖረ ያን ጊዜም ነፍሱ ያለ ፃዕር በፍጥነት ወጣች መድኃኒታችንም ተቀብሎ ሳማት ከእርሱም ጋር በብርሃን ሠረገላ ውስጥ አስቀመጣት አውጥቶም በሰማያዊ ክብር አኖራት።
አባ ኪሮስም እያደነቀ አለቀሰ ከዚህም በኋላ ወደ አበምኔቱ ሔዶ "እነሆ ያ ድኃ ስለ አረፈ መቃብር ቆፍረው ይቀበሩት ዘንድ ከመነኰሳቱ እዘዝ" አለው አበ ምኔቱም "ምን ግዴታ አለብኝ" አለው አባ ኪሮስም ትኩር ብሎ ተመለከተውና "ይህ የሰይጣን ሥራ እንጂ የሰው ሥራ አይደለም" አለው። ሰለ አስጨነቀውም ሰባት መነኰሳትን አዘዘለት እነርሱም ማዕጠንታቸውን ይዘው ተነሡ አባ ኪሮስም "የሚአጥኑት አሉና የረከሱ ማዕጠንቶቻችሁን አስወግዱ። በቦታቸውም ተዉአቸው ነገር ግን ቅበሩት" ብሎ አማላቸው።
ያን ጊዜም አራቱ የመላእክት አለቆች ሥጋውን በከርቤና በሚዓ አጠኑ መዓዛውም ያንን በዓት "መላው እነዚህ መነኰሳትም የሚያሸተን ምንድነው ይህመነኰስ ሥራይን ያውቅ ይሆን" ተባባሉ። ከዚህም በኋላ ሥጋውን ወስደው በዚያው ገዳም በእንግዳ መቃብር ቀበሩት ከመቃብሩም ጥሩ ውኃ ፈልቆ ለበሽተኞች ፈውስ ሆነ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛን በአባ ሚሳኤል በጸሎቱ ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የሐምሌ 8 ስንክሳር።
32 views20:29