Get Mystery Box with random crypto!

‹‹ወላጆች እንደሌላቸው ልጆች አልተዋችሁም›› /ዮሐ. 14፥18/ #ጰራቅሊጦስ በመንፈስ ቅዱስ | አሚነ ፅድቅ✨

‹‹ወላጆች እንደሌላቸው ልጆች አልተዋችሁም›› /ዮሐ. 14፥18/

#ጰራቅሊጦስ በመንፈስ ቅዱስ ለምትመራው የሐዲስ ኪዳን ቤተክርስቲያን የልደት ቀኗ ነው፡፡
ቤተክርስቲያን ለሁሉም በየቋንቋው ሃይማኖትን ማስተማር እንዳለባት ከመንፈስ ቅዱስ በላይ ምስክር አያስፈልግም፡፡
በየሀገሩ ቋንቋ ወንጌልን ማስተማር እንጂ የየሀገሩን ቋንቋ ለህዝብ ማስተማር የቤተክርስቲያን ኃላፊነት አይደለም፡፡
ለቅዱሳን ሐዋርያት የተገለጡላቸው ልሳናት (ቋንቋዎች) የታወቁ፣ ሰዎችም የሚግባቡባቸው ቋንቋዎች ናቸው፡፡
ለቅዱሳን ሐዋርያት የየሀገሩ ቋንቋ መገለጡ ሁሉም የዓለማችን ቋንቋዎች የሐዲስ ኪዳን ቤተክርስቲያን ልሳናት መሆናቸውንና የትኛውም ቋንቋ በተለየ ሁኔታ ብቸኛ የቤተክርስቲያን ልሳን እንዳልሆነ ያረጋግጥልናል፡፡
የልሳናት (ቋንቋዎች) መገለጥ ዓላማ ደቀመዛሙርቱ በተለያዩ የዓለም ክፍሎች ወንጌልን ለማስተማር ሲዘዋወሩ ሁሉንም በየቋንቋው ማስተማር እንዲችሉ ነው፡፡
የሐዋርያትን ፈለግ በምትከተል ኦርቶዶክሳዊት ቤተክርስቲያን ከሚከበሩ ዘጠኝ ዐበይት በዓላት መካከል አንዱ በዓለ ጰራቅሊጦስ ነው፡፡ ይህም በዓል በሐዋርያት ሥራ ምዕራፍ 2 በተገለጸው መልኩ ጸጋ መንፈስ ቅዱስ ለ120ው ቤተሰብ የወረደበትን ዕለት የምናስብበት ነው፡፡ በዚህች የአስተምህሮ ጦማር ስለ መንፈስ ቅዱስ ጸጋ፣ ስለ በዓለ ጰራቅሊጦስ የብሉይ ኪዳን ምሣሌዎች፣ ለሐዋርያት ስለተገለጠው ልሳን (ቋንቋ) እንዲሁም ስለተያያዥ ጉዳዮች እንዳስሳለን፡፡


#ጰራቅሊጦስ ማለት ምን ማለት ነው?

ጰራቅሊጦስ ማለት የግሪክ ቃል ሲሆን ከሦስቱ አካላት አንዱን እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስን የሚገልጥ ነው፣ ትርጉሙም መንጽኢ (የሚያጸና)፣ መንጽሒ (የሚያነጻ)፣ ናዛዚ (የሚያጽናና፣ የሚያረጋጋ) ማለት ነው፡፡ በተጨማሪም ጰራቅሊጦስ ማለት ከሣቲ (ምስጢር ገላጭ)፣ መስተሥርዪ (ይቅር ባይ) እና መስተፍሥሒ (ደስታን የሚሰጥ) ማለት ነው፡፡ ከቅዱሳን ሐዋርያት የሚበዙት ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ሞት በኋላ አይሁድን ፈርተው ይሸሹ ነበር፡፡ ከአይሁድ ፍርሃት ሙሉ በሙሉ መላቀቅ ያልቻሉ ደቀመዛሙርቱ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከእነርሱ ተለይቶ እንደሚያርግ ሲነግራቸው አዘኑ፡፡ ለተልዕኮ የጠራቸው፣ ዓለምን በወንጌል ብርሃን እንዲያበሩ የመረጣቸው ጌታ ግን ለድካማቸው አሳልፎ አልሰጣቸውም፡፡ ከትንሣኤው በኋላ እስከ ዕርገቱ ድረስ ለ40 ቀናት እየተገለጠላቸው እምነታቸውን አጸናላቸው፣ ቅዱስ ቃሉን አስተማራቸው፣ ለሐዲስ ኪዳን ቤተክርስቲያንም መሰረት የሆነ መንፈሳዊ ሥርዓትን አሳያቸው፡፡ ሰብሳቢ፣ ጠባቂ እንደሌላቸው የሙት ልጆች የሚሆኑ መስሏቸው ነበርና “የሙት ልጆች ትሆኑ ዘንድ አልተዋችሁም” (ዮሐ. 14፡18) አላቸው፡፡ ስለ ስሙ መከራን ለመቀበል እንዲጸኑ መንጽኢ (የሚያጸና) መንፈስ ቅዱስ ያስፈልጋቸው ነበርና “እኔ የአባቴን ተስፋ ለእናንተ እልካለሁ፤ እናንተ ግን ከአርያም ኃይልን እስክትለብሱ ድረስ በኢየሩሳሌም ከተማ ተቀመጡ፡፡” (ሉቃስ. 24፡49) በማለት ተስፋ ሰጣቸው፡፡ ይህም ተስፋ አስቀድሞ በነቢያት የተነገረ ነው (ትንቢተ ኢዩ. 2፡15)፡፡


#ጰራቅሊጦስ ስለምን #ኀምሳው ቀን በተፈጸመ ጊዜ ወረደ?

የመንፈስ ቅዱስ ጸጋ በግልጥ ለሐዲስ ኪዳን ቤተክርስቲያን የተገለጠው ቅዱሳን ሐዋርያት፣ አርድእትና ቅዱሳት አንስት ከእመቤታችን ጋር በአንድነት ለጸሎት ለምስጋና ተሰብስበው እያለ ነው ፡፡ “ኀምሳው ቀን በተፈጸመ ጊዜ፣ ሁሉም በአንድነት በአንድ ቦታ ተሰብስበው ነበር” (ሐዋ 2፡1-47)ሐዋ 2:1) እንዲል፡፡ በነቢያትና በሐዋርያት መሰረትነት የቆመች ኦርቶዶክሳዊት ቤተክርስቲያን (ኤፌ. 2፡20) በዓለ ጰራቅሊጦስን በሐዋርያት ዘመን እንደነበረው ከጌታችን ትንሣኤ በኋላ በኀምሳኛው ቀን ታከብራለች፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በዓለ ጰራቅሊጦስን “የቤተክርስቲያን የልደት ቀን” ሲል ጠርቶታል፡፡ በመንፈስ ቅዱስ የምትመራው የሐዲስ ኪዳን ቤተክርስቲያን በመንፈስ ቅዱስ ጸጋ ተመልታ ለሰው ልጆች ሁሉ እውነተኛ የክርስቶስን ወንጌል መስበክ የጀመረችበት ቀን ነውና፡፡

በዘመነ ሐዲስ ከሚከበሩ በዓላት ብዙዎቹ በዘመነ ብሉይ የነበሩ ምሣሌዎች አሏቸው፡፡ ከእነዚህ አንዱ በዓለ ጰራቅሊጦስ ነው፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ሙሴ በኦሪት መጻሕፍት እንደገለጠልን እስራኤል ዘሥጋ በዓለ ፋሲካን (እስራኤል ዘሥጋ ከግብጽ ባርነት ነፃ የወጡበት) ካከበሩ በኋላ ሰባት ሣምንታትን ቆጥረው በኀምሳኛው ቀን በዓለ ሰዊት (የእሸት በዓል) ያከብሩ ነበር (ዘሌ 23፡15-22፣ ዘጸ 34፡22፣ ዘኁ 28፡26)፡፡ ይህ የብሉይ ዘመን ታሪክ ሊመጣ ላለው ለክርስቶስ ቤዛነት ምሣሌ ነበር፡፡ መቶ ሃያ ቤተሰብ (12ቱ ሐዋርያት፣ 72ቱ አርድእትና 36ቱ ቅዱሳት አንስት) ከጌታችን ትንሣኤ በኋላ ሞገሳቸውን እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን በመካከል አድርገው በፍፁም አንድነት በጸሎት እየተጉ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሰጣቸው የተስፋ ቃል የሚፈምበትን ዕለት በእምነትና በተስፋ ይጠብቁ ነበር (ሉቃ. 24፡49፣ ዮሐ. 14፡15-18፣ ዮሐ. 16፡7-15፣ ሐዋ. 1፡8)፡፡

አባታችን አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ በመጽሐፈ ምስጢር የበዓለ ኀምሳ ምንባብ እንደገለፀልን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለደቀመዛሙርቱ “የመንፈስ ቅዱስን መውረድ ተስፋ በሰጣቸው በኀምሳ ሦስተኛው ቀን፣ ከሙታንም ተለይቶ በተነሣ በኀምሳኛው ቀን፣ በዕለተ እሁድ ከጠዋቱ ሦስት ሰዓት ደቀመዛሙርቱ በጽርሐ ጽዮን ተሰብስበው ሳሉ” የሚያጸና፣ የሚያነፃ፣ የሚያረጋጋ የእግዚአብሔር መንፈስ በእሳትና በነፋስ አምሳል ተገለፀላቸው፡፡ በዕለተ እሁድ በመገለፁም የሰንበተ ክርስቲያንን ክብር አስረዳን፡፡ ነገረ ምጽዓቱ (ደብረ ዘይት)፣ የትንሣኤው ብርሃን፣ የመንፈስ ቅዱስም መውረድ ዘላለማዊት በሆነች (ዓለማት በሚያልፉባት ስለዚህም ጊዜ በሚጠፋባት)፣ የመንግስተ ሰማያት ምሳሌ በሆነች በሰንበተ ክርስቲያን ነውና መንፈስ ቅዱስ በዕለተ እሁድ በእሳትና በነፋስ አምሳል ተገለፀ፡፡

እንግዲህ እናስተውል እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ግን ከቅዱሳን ሁሉ በላይ ናትና ቁጥሯ (ክብሯ) ከ120ው በቤተሰብ ጋር አንድ አይደለም፤ የመንፈስቅዱስን ጸጋ ለመቀበል እንደ ሌሎች ቅዱሳን በዓለ ኀምሳን መጠበቅም አላስፈለጋትም፡፡ ከአበው አብራክ ከፍሎ የጠበቃት፣ በማኅፀነ ሐና ያከበራት፣ በቅዱስ ገብርኤል ብስራት ክብሯን የገለጠ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ በተለየ ክብር ቀድሷታልና (ሉቃስ 1፡35)፡፡

#የእሳትና #የነፋስ ምሳሌነቱ ምንድን ነው?

እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ በፍፁም አንድነት በልዩ ሦስትነት የሚመሰገን የራሱ ፍፁም መልክ፣ ፍፁም ገፅ፣ ፍፁም አካል ያለው፣ ከአብና ከወልድ ጋር ህልው ሆኖ የሚኖር፣ ዓለማትን የፈጠረ፣ የፍጥረታት ሁሉ መጋቢ፣ ዓለምንም አሳልፎ ለዘለዓለም የሚኖር አምላክ ነው፡፡ አባታችን አባ ሕርያቆስ መንፈስ ቅዱስ በገለጠለት የቅዳሴ ማርያም ምስጋናው እንዳስተማረን መለኮት (እግዚአብሔር) ግን ይህን ያህላል፣ ይህንንም ይመስላል ሊባል አይቻልም (ቅዳሴ ማርያም ቁጥር 47)፡፡ ይሁንና በዓለም ሁሉ በምልዓት የሚኖር አምላክ በፈቃዱ ለፍጥረታት ይገለጣል፡፡ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስም ዓለምን የፈጠረ፣ የሚጠብቅ፣ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስም ህልው ሆኖ (በህልውና ተገናዝቦ) ደቀመዛሙርቱን ለሐዲስ ኪዳን አገልግሎት የጠራቸው፣ በትምህርትም በተዓምራትም ከአብ ከወልድ ጋር የማይለይ ነው፡፡