ፀሎቴን ባሰማ ፥ እንደሰው ዝም አለኝ እሱንም ዘመቻ ፥ ወሰዱት መሰለኝ ....... የእቴሜቴ ጀምበር ሲራክ ወንድሙ . እረኛ አይዘምርም ፥ ዝም ነው አድባሩ ፋኖስ ክሩን አጥቷል ፥ መሸ ደህና እደሩ ቡሬ መንደር ራቃት ፥ የለችም ከቤቷ በሌት አልዘመረች ፥ ከፍቷታል ወፊቷ ማልዶ ሌት ሚያነቃኝ ፥ ዶሮ በጉድ ወጣ የሌት ድምፁን ሸጦ ፥ መውዜር ይዞ መጣ ወዲያም ወደ ሰማይ ከጎጆዬ በላይ ፀሎቴን ባሰማ እንደሰው ዝም አለኝ እሱንም ዘመቻ ወሰዱት መሰለኝ . የዛች የእዝነት አርማ ፥ የህዋ ላይ ሰንደቅ እንዴት ቀን ከፍቶባት ፥ ውብ ጀምበሯ ትጥለቅ ከዛች ከገራገር ፥ ከደጊቱ ዳሴ እንደምን ብርቅ ይሁን ፥ ሰላም ለእለት ጉርሴ ኧረ እንደምን በምን ኧረ እንደምን በምን አምነን ያነገስነው ብራ ቀን ይዳምን እኔን አፈር ይብላኝ ፥ ለእኔ ቀኑ ይክፋ አንቺን ያሳጣችሽ ፥ ያች አለም ትደፋ እስከ መች አስከ መች ፥ የአረር ሙዳይ ቋጥረን እንደጃኖ ኩታ ፥ ዝናር ጥለት አርገን ሀገር እያጠፋን ፥ ያልፋል እንላለን ? እንዴት ነው መሰንበት ? መውዜር እንደነዶ በሚመዘዝበት? ኧረ እንደምን በምን ኧረ እንደምን በምን አምነን ያነገስነው ብራ ቀን ይዳምን? . ከጩኸትሽ ማዶ ፥ ካኮረፈው ሰማይ ቄራ ከመሰለው ፥ ከአድማስሽ ሸራ ላይ እብሪት ያጠላበት ፥ ምስል ድንገት ካየው ለቸር አንመስለኝም ፥ ያን ጊዜ ፈራለሁ አርብ አርቡን አመሻሽ የሰማዩ ገላ ሲመስል የደም ሻሽ ንትብ የለበሰ ከወደ አንገቱ ዘሞ የተዘለሰ ይሁዳሽን ባላይ ፥ ወድቆ ሲያንሰራራ መስቀል ሆኗል ለሻጭ ፥ ገዢ ራሱን ያኩራ ከክርስቶስ ይልቅ ፥ ይሁዳ ነውና ሚረከብ መከራ ምክኒያቱም ...... ዘመን እያሰፉ ትውልድ ለሚነቅፉ ነገር ጠንቷል ዛሬ ፥ አውቀውት ይረፉ ለሻጭ መስቀል ሊሆን ፥ ምሏልና ዛፉ . በኑረት ቀራንዮ ፥ በህይወት ጎለጎታ ከገዳይሽ ቀዬ ፥ አንቺ ሆነሽ ጌታ በሰማያ አኮርባጅ ፥ ወዲያ ስትላጊ የመከራን መስቀል በሌት ተሸክመሽ ፥ መንገድ ስትፈልጊ ጨረቃዋ ገባች ፥ ከደመና ጉያ ከዋክቶች ሸሽተው ፥ እንደሰደድ ቋያ ጠረንሽን ገፍተው ፥ ከገላሽ ሲርቁ በንቄት ሸምቀው ፥ ሊጥሉሽ ዘለቁ . ዞር ብንል ወዲያ ፥ አራራይ መረዋ ቀና ብንል ኦና ፥ የጠቆረ ህዋ የፀሎትሽ ጩኸት ፥ ካልደረሰው ያ ቃል እሱም እንደሰዉ ዘምቶልሽ ይሆናል። ..................... //// .............. ሲራክ ወንድሙ @siraaq የእቴሜቴ ጀምበር ህዳር ፳፻፲፬ ዓ.ም http://t.me/kinchebchabi 4.0K viewsC-ራክ, 10:22