2022-08-24 21:04:08
አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አሜን
ነሐሴ 19-ከሰማንያ ዓመታት በላይ በበርሃ ጽኑ ተጋድሎን የተጋደሉትና በግብጽ በገደሙት ገዳማቸው በአስቄጥስ ከ50,000 በላይ መነኮሳትን የመሩት የአባ መቃርስ የሥጋቸው ፍልሰት የተከናወነበት ዕለት ነው፡፡ ይኸውም የመነኮሳት ሁሉ አለቃ የሆኑት የአባ መቃርስ የሥጋቸው ፍልሰት በዚኽች ዕለት የተከናወነው ሳስዊር ከሚባል አገር ወደ አስቄጥስ ገዳም ነው፡፡ ከከበረች ዕረፍቱ በኋላ ከሀገሩ ከሳስዊር ሰዎች መጥተው ሥጋውን በድብቅ ወስደውት ቤተ ክርስቲያን ሠርተውለት ከዚያ አኖሩት፡፡ ነገር ግን እስላሞች ነግሠው በክርስቲያኖች ላይ ስደት ስላመጡ የአባ መቃርስን ሥጋ ወስደው በድጋሚ ቤተ ክርስቲያን ሠርተውለት የቅዱሱን ሥጋ ከዚያ አኖሩት፡፡ ሊቀ ጳጳሳቱም ወደ ቤተ መቅደስ ገብቶ ስለ አባ መቃርስ ሥጋ እያለቀሰ እግዚአብሔርን ለመነ፡፡ የአስቄጥስ ገዳም አረጋዊያን መነኮሳትንም አስከትሎ የአባ መቃርስ ዐፅም ወዳለበት ሄዱ፡፡ ነገር ግን የአገሩ ሰዎች መኮንናቸውን አስቀድመው ሰይፋቸውን መዘው በመጠበቅ የአባ መቃርስ ዐፅም ከለከሏቸው፡፡ ሊቀ ጳጳሳቱና መነኮሳቱም አዝነው ፈጽመው እያዘኑ አደሩ፡፡ ነገር ግን አባ መቃርስ በዚያች ሌሊት ለመኮንኑ በራእይ ተገለጠለትና ‹‹ከልጆቼ ጋር መሄድን ለምን ትከለክለኛለህ? እንግዲህስ ከልጆቼ ጋር ወደ ቦታዬ ልሄድ›› አለው፡፡ መኮንኑም በጠዋት ተነሥቶ እየፈራና እየተንቀጠቀጠ አረጋውያን መነኮሳቱን ጠርቶ የከበረ የአባ መቃርስን ሥጋ ሰጣቸው፡፡
እነርሱም እጅግ ደስ ብሏቸው የአባ መቃርስን ሥጋ ይዘው በመርከብ በመሳፈር ተርኑጥ የምትባል አገር አድረው በማግሥቱ ወደ ገዳማቸው አስቄጥስ ለመድረስ በረሃውን ሲያቋርጡ ጥቂት ሊያርፉ ወደዱ፡፡ ነገር ግን አባ ሚካኤል ‹‹የቅዱስ አባታችንን ሥጋ የምናሳርፍበትን ቦታ እግዚአብሔር ካልገለጠልን በቀር አናርፍም›› አላቸው፡፡ ወዲያውም የአባ መቃርስን ሥጋ የተሸከመው ግመል ወደ አንድ ቦታ ደርሶ በዚያ በርከክ ብሎ የአባ መቃርስ ሥጋ ያለበትን ሣጥን ራሱ ይጥል ዘንድ ወዲያና ወዲህ ሲዟዟር አዩት፡፡ መነኮሳቱም እግዚአብሔር የፈቀደው ቦታ መሆኑን ዐውቀው ደስ ተሰኙ፡፡ ያም ቦታ እስከዛሬም ድረስ እንደታወቀ አለ፡፡ ከዚህም በኋላ መነኮሳቱ የአባ መቃርስ ሥጋ ይዘው ወደ አስቄጥስ ገዳም በደረሱ ጊዜ የገዳሙ መነኮሳት ሁሉም ወጥተው ወንጌልና መስቀሎችን ይዘው እየዘመሩና እያመሰገኑ ወደ ቤተ ክርስቲያን አስገቡት፡፡ ከአባ መቃርስም ሥጋ ብዙ አስገራሚ ተአምራት ተገልጠው ታዩ፡፡
በገዳም ለሚፈጸም ተጋድሎ ፋና የሆኑ በአስቄጥስ ገዳም ለሚኖሩ መነኮሳት ሁሉ አባት የሆኑት የከበሩ ታላቁ አባ መቃርስ፡- መቃርስ (መቃርዮስ) ማለት ‹‹ቅዱሱ ለእግዚአብሔር›› ማለት ነው፡፡ ከደቡባዊ ግብፅ ከተወደዱ ደጋግ ክርስቲኖች የተገኘ ታላቅ አባት ነው፡፡ አባታቸው አብርሃም እናታቸው ሣራ ይባላሉ፡፡ እነርሱም መጽሐፍ ቅዱስ ላይ እንዳሉት እንደ አብርሃምና ሣራ እጅግ ደጎች ነበሩ፡፡ ልጅ ግን አልነበራቸውምና በስለት መቃርስን ወለዱ፡፡ ሲያድጉም በግድ ያለፈቃዳቸው ሚስት አጋቧቸው፡፡ አባ መቃርስ ግን ወደ ሙሽራይቱ በገቡ ጊዜ ዐውቀው እንደታመሙ ሆነው ተኙ፡፡ ‹‹ከበሽታዬ ለጥቂት ጊዜ ጤና ባገኝ ወደ ገዳም ልሂድ›› ብለው ወደ አስቄጥስ በረሃ ሄዱ፡፡ መልአክም ተገልጦ ‹‹ይህች አስቄጥስ የአንተና የልጆችህ ርስት ናት›› አላቸው፡፡ ወደ ቤተሰባቸውም በተመለሱ ጊዜ ሙሽራ እጮኛቸው በድንግልና እንዳለች ሞታ ደረሱ፡፡ ከጥቂት ቀንም በኋላ እናትና አባታቸውም ዐረፉ፡፡ እርሳቸውም ንብረታቸውን ሁሉ ለድሆች መጽውተው ገዳም ገቡ፡፡ ሕዝቡም ደግነታቸውንና እውነተኛነታቸውን አይተው ትንሽ ማረፊያ ሠርተው ሌሎች እንዲያገለግሏቸው አደረጉ፡፡
ከዕለታትም በአንድ ቀን አንዲት ሴት ልጅ ከጎረምሳ አርግዛ ሳለ ጎረምሳው ‹‹አባትሽ ሲጠይቅሽ ከአባ መቃርስ አረገዝኩ በይ›› ብሎ መከራትና ለአባቷ እንደተባለችው ተናገረች፡፡ ‹‹አባ መቃርስ በግድ ደፍረውኝ አረገዝኩ›› አለች፡፡ የከተማው ሰውም አባ መቃርስን ከበዓታቸው አውጥተው ለሞት እስኪደርሱ ድረስ ደበደቧቸው፡፡ መላእክትም በሰው አምሳል ተገልጠው ዋስ ሆነው ለልጅቷም ምግቧን ሊሰጡ ተስማምተው ወደ በዓታቸው መለሷቸው፡፡ አባ መቃርስም ለራሳቸው ‹‹መቃርስ ሆይ እንግዲህ ባለ ሚስትና ባለ ልጅ ሆነሃልና ሌሊትና ቀን መሥራት ይገባሃል›› እያሉ ቅርጫቶችን እየሠፉ ለሚያገለግላቸው ልጅ እየሰጡት እርሱ ሸጦ እያመጣ ብዙውን ለዚያች በዝሙት ጸንሳ በሳቸው ላሳበበች ሴት ይሰጡ ጀመር፡፡ መውለጃዋም በደረሰ ጊዜ እስከ 4 ቀን ድረስ በጽኑ ሥቃይ ቆየች፡፡ እውነቱንም ተናግራ ንስሓ በገባች ጊዜ ወደ አባ መቃርስ ዘንድ አደረሷት፡፡ ሕዝቡም ሁሉ ‹‹አባታችን ይቅር በሉን›› ብለው ከእግራቸው ላይ ሲወድቁ ይቅር ብለዋቸው ቀድሰው አቆረቧቸው፡፡
ከዚህ በኋላ መልአኩ ወስዶ አስቄጥስ ገዳም አደረሳቸው፡፡ የቅዱሳኑ የመክሲሞስና የዱማቴዎስ በዓት ወደ ሆነች ቦታም አስገብቶ በዚያ በልጆቻቸው ቦታ ላይ በዓታቸውን እንዲያጸኑ ነገራቸው፡፡ አባ መቃርስ ወደ አባ እንጦንስ ዘንድም በመሄድ በረከታቸውንና ምክራቸውን ይቀበሉ ነበር፡፡ ሰይጣናትም በእርሳቸው ላይ የሚያደርሱትን ክፉ ነገር ሲመካከሩ ይሰሟቸው ነበር፡፡ በእሳት እያቃጠሉ ፈተኗቸው፣ የዝሙት መንፈስ እያመጡም ፈተኗቸው፣ በዚህም ትዕግስትን ቢያደርጉ በሌላም ዓለማዊ ክብርን መውድን፣ ትዕቢትን፣ መመካትን፣ ታካችነትን፣ ስድብን፣ ሃይማኖት ማጣትን፣ ተስፋ መቁረጥን በልባቸው አሳደሩባቸው፡፡ በአጋንንት ምክንያት ይህም እንደሚመጣባቸው አባ እንጦንስ አስቀድመው ነግረዋቸው ነበር፡፡ ወደ አባ እንጦንም በመሄድ በአጋንንቱ የደረሰባቸውን ፈተናና ጾር ነገሯቸው፡፡ አባ እንጦንስም አመንኩሰው እንዲጸኑ በመምከር ወደ በዓታቸው ሸኟቸው፡፡ አንድ እርኩስ መንፈስ ያደረበት ባሕታዊ አግኝቶ ትንሣኤ ሙታንን አላምንም ቢላቸው ሙት አስነሥትው አሳይተው አሳምነውታል፡፡ ሙቱንም አጥምቀው አምነኩሰውት 7 ዓመት በተጋድሎ ኖሮ በሰላም ዐረፈ፡፡
አባ መቃርስ በበረሃ ውስጥ ራቁታቸውን ጌታችን ከብርዱም ሆነ ከሙቀቱ እየጠበቃቸው 40 ዘመን የኖሩ ጻድቃንን አገኟቸውና ‹‹እንደ እናንተ እንድሆን ምን ላድርግ?›› ቢሏቸው ‹‹ወደ በዓትህ ተመልሰህ ስለ ኃጢአትህ አልቅስ አንተም እንደ እኛ ትሆናልህ›› አሏቸው፡፡ አባ መቃርስም የጻድቃኑን በረከታቸውን ተቀብለው ወደ በዓታቸው ተመልሰው ማልቀስ ጀመሩ፡፡ ጻዲቁ በመጨረሻ ነፍሳቸውን መላእክት ሲያሳርጓት ይፈትኗቸው የነበሩ አጋንንት ‹‹መቃርስ ሆይ አመለጥከን አሸነፍከን…›› እያሉ ሲጮኩ አባ መቃርስም ‹‹እስከ ዛሬ ገና ነኝ፣ በጌታዬ በቀኙ ልቁም በግራው አላወኩምና›› ብለው በትሕትና መለሱላቸው፡፡ የአባ መቃርስ ረድኤት በረከታቸው ይደርብን፣ በጸሎታቸው ይማረን፡፡
ከገድላት አንደበት
✞ ✞ ✞
766 viewsmiki2721, 18:04