ዝክረ ቅዱሳን ማኅበረ ቅዱስ ዳዊት - ዘብሔረ ጎንደር (ዲ/ዮርዳኖስ አበበ): † † እንኩዋን ለእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ዓመታዊ የኪዳን በዓል በሰላም አደረሳችሁ † † † † 7ቱ ኪዳናት † † =>ተካየደ ማለት ተስማማ: ተማማለ እንደ ማለት ሲሆን ኪዳን በቁሙ ውል: ስምምነት እንደ ማለት ነው:: ይኸውም እግዚአብሔር ከሰዎች ጋር: ሰዎችም ከሰዎች ጋር የሚያደርጉት ሊሆን ይችላል:: ልዩነቱ የእግዚአብሔር ቃል ኪዳን ቅዱስና የማይለወጥ መሆኑ ነው:: +እግዚአብሔር አምላክ ከሥነ ፍጥረት ጀምሮ በየጊዜው ከብዙ ወዳጆቹ ጋር ኪዳንን አድርጉዋል:: ቅድስት ቤተ ክርስቲያንም እነዚህን ኪዳናት ጥቅልል አድርጋ 7 እንደ ሆኑ ታስተምራለች:: ስለዚህም ዛሬ ፈጣሪ ቢረዳን እነዚሁን 7 ኪዳናት በጥቂቱ እንመለከታለን:: "ኪዳነ ተካየድኩ ምስለ ኅሩያንየ" "ከመረጥኩዋቸው ጋር ቃል ኪዳንን አደረግሁ" (መዝ. 88:3) 1. +" ኪዳነ አዳም "+ =>አዳም ማለት የእግዚአብሔር ድንቅ ፍጥረት: የፍጡራን አስተዳዳሪ: ነቢይ: ካህንና ንጉሥ ነው:: እግዚአብሔር ከአዳም ጋር አስቀድሞ በእጸ በለስ አማካኝነት ቃል ኪዳን ነበራቸው:: ነገር ግን አባታችን በዲያብሎስ ሴራ በመረታቱ ኪዳኑ ፈረሰ:: (ዘፍ. 3:1) +አዳምና ሔዋን ተጸጽተው ቢያለቅሱ ግን አዲስ የኪዳን ተስፋ: "ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ" የሚል ኪዳንን ተቀበሉ:: (ቀሌምንጦስ: ገላ. 4:4) 2. +" ኪዳነ ኖኅ "+ =>ከአዳም እስከ ኖኅ ድረስ ባሉት 10 ትውልድ ዓለም በዓመፃ ተሞላች:: ቅዱስ ኖኅ በደግነቱ መርከብ ሠርቶ ቤተሰቡን ሲያተርፍ ዓለም በማየ ሥራዌ ጠፋች:: ከመርከቡ ከወጣ በሁዋላ ኖኅና እግዚአብሔር በቀስተ ደመና ምልክትነት ቃል ኪዳን ተጋቡ:: "ኢያማስና ለምድር ዳግመ በማየ አይኅ" እንዲል:: (ዘፍ. 9:12) 3. +" ኪዳነ መልከ ጼዴቅ "+ =>መልከ ጼዴቅ የእግዚአብሔር ካህኑ: የክርስቶስም ምሳሌው የሆነ የሳሌም ንጉሥ ነው:: በ15 ዓመቱ መንኖ: አጽመ አዳምን ይዞ: በቀራንዮ በሕብስትና በወይን ያስታኩት ነበር:: +እግዚአብሔር ለመልከ ጼዴቅ: በሐዲስ ኪዳን ለምትሠራው ክህነትና ምሥጢረ ቁርባን ምሳሌ አድርጐ በቃል ኪዳን አትሞታል:: በዚህም ተሰውሮ ይኖራል እንጂ ሞትን እስካሁን አልቀመሰም:: ይህም ካህኑ መልከ ጼዴቅ ከአብርሃም ጋር በተገናኙበት ጊዜ ተገልጧል:: (ዘፍ. 14:17, ዕብ. 7:1) 4. +" ኪዳነ አብርሃም "+ =>ቅዱስ አብርሃም የሕዝብና የአሕዛብ አባት: ሥርወ ሃይማኖት: የጽድቅም አበጋዝ ነው:: ስለ ፍቅረ እግዚአብሔር ሲል ከርስቱና ከወገኖቹ ተለይቶ በቅድስና ኑሯልና እግዚአብሔር "በዘርሕ አሕዛብ ይባረካሉ" አለው:: (ዘፍ. 12:1) የቃል ኪዳን ምልክትም ይሆነው ዘንድ ግዝረትን ሰጠው:: (ዘፍ. 17:1-14) 5. +" ኪዳነ ሙሴ "+ =>ቅዱስ ሙሴ የነቢያት አለቃ: የእሥራኤል እረኛ: የእግዚአብሔር ሰው እና ፍጹም ትሑት (የዋህ) ሰው ነው:: በፈጣሪው ትዕዛዝ እሥራኤልን ከግብጽ ባርነት አውጥቶ ለ40 ዘመናት በበርሃ ሲመራቸው ከእግዚአብሔር የኪዳንን ጽላትና አሠርቱን ትዕዛዛት ተቀብሏል:: (ዘጸ. 20:1, 31:18) 6. +" ኪዳነ ዳዊት "+ =>ቅዱስ ዳዊት ሥርወ ነገሥት: ጻድቅ: የዋህና ቡሩክ የሆነ አባት ነው:: እግዚአብሔር ከእረኝነት ጠርቶ ንጉሥ አድርጐ ሹሞት "ከሆድህ ፍሬ በዙፋንህ ላይ አኖራለሁ" (መዝ. 131:11) ሲል ምሎለታል:: አክሎም ሰፊ ቃል ኪዳን ሰጥቶ "አልዋሰሽህም" ብሎ ሲምልለት እንመለከታለን:: (መዝ. 88:35) 7. +" ኪዳነ ምሕረት "+ =>በብሉይ ኪዳን የነበሩ 6ቱ ኪዳናት በዘመናቸው ክቡርና ሕዝቡን ከመቅሰፍት ይታደጉ የነበሩ ቢሆንም ከሲዖል ማዳን ግን አልቻሉም:: ስለዚህም አንድ ፍጹም ኪዳን ያስፈልግ ነበር:: ይህን ፍጹም ኪዳን ይፈጽም ዘንድም ከቅድስት ሥላሴ አንዱ ወልድ ከሰማያት ወርዶ በድንግል ማርያም ማሕጸን አደረ:: +በፍጹም ተዋሕዶም በሕቱም ድንግልና ተወልዶ: አድጎ: ተጠምቆ: አስተምሮ: ሙቶ: ተነስቶና ዐርጐ ሥጋ ማርያምን በዘባነ ኪሩብ አስቀመጠው:: ኪዳነ ምሕረት (የምሕረት ኪዳን) የምንለው አንዱ ታዲያ ይሔው ነው:: +የጌታችን መጸነሱ: መወለዱ: መሰደዱ: መጠመቁ: ማስተማሩ: ሥጋውንና ደሙን መስጠቱ: መሰቀሉ: መሞቱና መነሳቱ: ማረጉና መንፈስ ቅዱስን መላኩ በአንድ ላይ ኪዳነ ምሕረት ይባላል:: ታዲያ ይህ ሁሉ የተደረገው በሥጋ ማርያም ነውና የኪዳኑ ባለቤት እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ናት:: +የእርሷ ኪዳን 6ቱን አበው ኪዳናት ፍጹም በማድረጉ የኪዳናት ማሕተም ይባላል:: የድንግል ማርያም ኪዳኗ ከሲዖልና ከገሃነም ሊታደገን አቅሙ አለውና:: መድኃኒታችን ክርስቶስ ለድንግል እናቱ ቃል ኪዳኑን ያጸናላት ደግሞ ካረገ ከዓመታት በሁዋላ ጐልጐታ ላይ ነው:: +እመ ብርሃን በዚያ ቁማ ስለ ኃጥአን ስታለቅስ "እናቴ ሆይ! በስምሽ ያመነውን: በቃል ኪዳንሽ የተማጸነውን እምርልሻለሁ" ብሎ ደስ አሰኝቷታልና:: ይሔው በእመ ብርሃን ምልጃና ቃል ኪዳን ምዕመናን ከመቅሰፍትና ከገሃነመ እሳት ማምለጥ ከጀመሩ 2ሺ ዓመታት ሆኑ:: ዛሬም እኛ ኃጥአን ልጆቿ ከእሳት እንደምታድነን አምነን በጥላዋ ሥር እንኖራለን:: *" ኢትዝክሪ ብነ አበሳነ: ኃጢአተነ: ወጌጋየነ: ማርያም እሙ ለእግዚእነ: በኪዳንኪ: ወበስደትኪ ድንግል ተማሕጸነ::" "ድንግል ሆይ! ኃጢአታችን: አበሳችንና በደላችንን አታስቢብን ዘንድ በስደትሽና በኪዳንሽ ተማጽነናል::" =>የአርያም ንግሥት: የሰማያውያንና ምድራውያን ኁሉ እመቤት: የአምላክ እናት: ቅድስት: ስብሕት: ክብርት: ልዕልት: ቡርክት: ፍስሕትና ጥዕምት የሆነች ድንግል ማርያም የድኅነታችን መሠረት: ላመኑባት አንገት የማታስደፋ እውነተኛ አማላጅ ናት:: +በዚህች ዕለት የካቲት 16 ስለ ወገኖቿ የሰው ልጆች ፍቅር በእንባ ያቀረበችውን ልመና የባሕርይ አምላክ የሆነ ልጁዋ ተቀብሎ በማይዋሽ ንጹሕ አንደበቱ ቃል ኪዳን ገብቶላታል:: በስምሽ ያመነ በቃል ኪዳንሽ የተማመነ እሳት አያይም ብሏታል:: =>ቸሩ ልጇ ከበረከተ ኪዳኗ አይለየን:: በዓሉንም የሰላም: የፍቅርና የበረከት ያድርግልን:: =>የካቲት 16 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት= 1.ኪዳነ ምሕረት (የሰባቱ ኪዳናት ማሕተም) 2.ቅድስት ኤልሳቤጥ (የመጥምቁ ዮሐንስ እናት / የእመቤታችን አክስት / የሶፍያ ልጅ) 3.ቅዱስ ገብረ ማርያም ጻድቅ ንጉሠ ኢትዮዽያ (የቅ/ላሊበላ ወንድም) =>ወርኀዊ በዓላት 1.ቅዱስ አኖሬዎስ ንጉሥ ጻድቅ 2.አባ አቡናፍር ገዳማዊ 3.አባ ዮሐንስ ወንጌሉ ዘወርቅ 4.አባ ዳንኤል ጻድቅ =>+"+"+ . . . ኤልሳቤጥም የማርያምን ሰላምታ በሰማች ጊዜ ፅንሱ በማኅፀንዋ ውስጥ ዘለለ:: በኤልሳቤጥም መንፈስ ቅዱስ ሞላባት:: በታላቅ ድምፅም ጮኻ እንዲህ አለች:- አንቺ ከሴቶች መካከል የተባረክሽ ነሽ: የማኅፀንሽም ፍሬ የተባረከ ነው:: የጌታዬ እናት ወደ እኔ ትመጣ ዘንድ እንዴት ይሆንልኛል? እነሆ የሰላምታሽ ድምፅ በጀሮየ በመጣ ጊዜ ፅንሱ በማኅፀኔ በደስታ ዘሎአልና:: ከጌታ የተነገረላት ቃል ይፈፀማልና ያመነች ብፅዕት ናት:: +"+"+ (ሉቃ. 1:39) ††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር ††† የካቲት 16 ✞ እንኩዋን ለእናታችን ቅድስት ኤልሳቤጥ ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ ✞ + " ቅድስት ኤልሳቤጥ " + 178 views03:38