Get Mystery Box with random crypto!

Daniel: ✞ እንኩዋን ለቅዱስ 'አምላካችን አማኑኤል' : 'ዕለተ ማርያም' እና 'ዕለተ ጌና | ✞ገድለ ቅዱሳን✞

Daniel:
✞ እንኩዋን ለቅዱስ "አምላካችን አማኑኤል" : "ዕለተ ማርያም" እና "ዕለተ ጌና ስቡሕ" ዓመታዊ በዓል በሰላም አደረሳችሁ ✞

+*" ቅዱስ አማኑኤል "*+

=>የክርስትና ሃይማኖት እጅግ ብዙ ምሥጢራትን ያካትታል:: ታላቅ መዝገብ ነውና:: ሰዎች እናልፋለን:: ዓለምም ታረጃለች እንጂ ምሥጢረ ክርስትና አያረጅም:: እዚህ ቦታ ላይ ይጠናቀቃልም አይባልም::

+"አማኑኤል" የሚለውን ስም መረዳት የሚቻለው በአንድ መንገድ : እርሱም ምሥጢረ ሥላሴንና ምሥጢረ ሥጋዌን ጠንቅቆ በመማር ነው:: ምሥጢራት ደግሞ በእምነት ለማይኖር: በትሕትናም ለማይቀርብ የሚገለጡ አይደሉም::

+እግዚአብሔር አንድም ነው: ሦስትም ነው:: ጊዜ ሣይሠፈር: ዘመንም ሳይቆጠር እግዚአብሔር በስም: በአካል: በግብር ሦስትነቱ: በባሕርይ: በሕልውና: በመለኮትና በሥልጣን አንድነቱ የጸና አምላክ ነው::

+ከዓለም መፈጠር በፊት ስለ ነበረው ነገር የሚያውቅ ራሱ ሥላሴ ብቻ ነው:: ዓለምን ከፈጠረ በሁዋላም ምሥጢረ ሥላሴ (መለኮት) ብለን የምንማረው ትምሕርት እንድንና እንጠቀም ዘንድ እርሱ የገለጠልንን ያህል ብቻ ነው::

+ይኼውም በየጊዜው እርሱ ለወደዳቸውና ደስ ላሰኙት ቅዱሳኑ የገለጠው ምሥጢር ነው:: ከዚህ አልፈን በሥጋዊ አዕምሯችን ጌታን "እንመርምርሕ" ብንለው ግን ፍጻሜአችን ሞት: ማደሪያችንም ገሃነመ እሳት መሆኑ አይቀርም::

+ወደ ቀደመ ነገራችን እንመለስና እግዚአብሔር በአንድነቱና ሦስትነቱ ሳለ ይህንን ዓለም ፈጠረ:: እግዚአብሔር ዓለምን ለምን ፈጠረ ቢሉ:- ስሙን ቀድሰን ክብሩን እንድንወርስ ነው:: ከዚህ የተረፈውን ምክንያት ግን ራሱ ባለቤቱ ያውቃል::

+እግዚአብሔር በሁዋለኛው ዘመን ሰው የሆነበት ምሥጢር እኛን ለማዳን ቢሆንም ይሔው ተግባሩ ዓለም ሳይፈጠር ያሰበው እንጂ በአዳም ውድቀት ምክንያት ድንገት የታሰበ አይደለም::

+እግዚአብሔር አዳምን በ7 ሃብታት አክብሮ በገነት ቢያኖረው "አትብላ" የተባለውን ዕፀ በለስ በላ:: በዚህም ከፈጣሪው ተጣልቶ: በሞተ ሥጋ ሞተ ነፍስ: በርደተ መቃብር ርደተ ገሃነም ተፈረደበት:: በሁዋላ ግን ንስሃ ስለ ገባ "ከ5 ቀን ተኩል (5,500 ዘመን) በሁዋላ ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ" የሚል ቃል ኪዳንን ሰጠው::

+ከዚህ በሁዋላ ለ5,500 ዘመናት ጊዜ ወደ ታች ይቆጠር ጀመር:: ስለ እግዚአብሔር ሰው መሆንና ዓለምን ማዳንም ትንቢት ይነገር: ሱባኤ ይቆጠር: ምሳሌም ይመሰል ገባ::

+ከአዳም እስከ ሙሴ (ዘመነ አበው) ምሳሌያት ይበዛሉ:: ከሙሴ እስከ ዳዊት (ዘመነ መሣፍንት) ምሳሌያቱ እየጐሉ መጥተዋል:: ከልበ አምላክ ቅዱስ ዳዊት እስከ ቅዱስ ሚልክያስ ድረስ (በዘመነ ነቢያት / ነገሥት) ግን ትንቢቶች ስለ ክርስቶስና ስለ ማደሪያ እናቱ እንደ ጐርፍ ፈሰዋል::

+ነቢያትም የመሲህን መምጣት እየጠበቁ በጾም: በጸሎትና በትሕርምት ኑረዋል:: እንባቸውንም አፍሰው ቅድመ እግዚአብሔር ደርሶላቸዋል:: መድኅን ክርስቶስም ተወልዶ አድኗቸዋል::

+"አማኑኤል" የሚለው ቃል ከእብራይስጥ ልሳን (ከጽርዕ የሚሉም አሉ) በቀጥታ የተወረሰ ሲሆን ትርጉሙም "እግዚአብሔር ምስሌነ - እግዚአብሔር ከእኛ ጋር ሆነ" እንደ ማለት ነው:: (ኢሳ. 7:14, ማቴ. 1:22) ምሥጢሩ ግን ከዚህ የሠፋ ነው::

+"አማኑኤል" ማለት "እግዚአብሔር ከሥጋችን ሥጋን: ከነፍሳችን ነፍስን ነስቶ በፍጹም ተዋሕዶ እኛን መሰለን" ማለት ነው:: በሌላ አነጋገርም "አምላክ ሰው ሆነ: ሰውም አምላክ ሆነ" እንደ ማለት ነው::

+ይሕንን ሲያደንቁ ቅዱሳን ሊቃውንት "ወዝንቱ ስም ዓቢይ: ወኢይደሉ ፈሊጦቶ-ይህ ስም ታላቅ ነው:: ወደ ሁለት ሊከፍሉት (ሊለዩት) አይገባም" ብለው ምሥጢረ ተዋሕዶን አስረድተዋል:: (ሃይ. አበ. ዘሳዊሮስ)

+ስለዚህም ከሦስቱ አካላት አንዱ ወልድ እኛን ያድን ዘንድ በተለየ አካሉና በከዊነ ቃልነቱ ፍጹም የድንግል ማርያምን ሥጋ ተዋሕዶ የሰውነትንም: የአምላክነቱንም ሥራ ሠርቶ አድኖናል::

+በማሕጸነ ድንግል ከተቀረጸባት ደቂቃ ጀምሮም ፍጹም ተዋሕዶን ፈጽሟልና መቼም መች አምላክም: ሰውም ነው እንጂ ወደ ሁለትነት: ማለትም አምላክን ለብቻ: ሰውን ለብቻ አናደርግም::

+ስለዚህም ዛሬም: ዘወትርም እግዚአብሔር ቃል የተዋሐደው ሥጋችን በዘባነ ኪሩብ ሲሠለስና ሲቀደስ ይኖራል:: እርሱ ጌታችን እስከዚህ ድረስ ወዶናልና::

+ፈጣሪያች በሦስትነቱ:- ሥላሴ (አብ: ወልድ: መንፈስ ቅዱስ): በአንድነቱ:- እግዚአብሔር: ኤልሻዳይ: አልፋ: ወዖ: ቤጣ: የውጣ: ኦሜጋ . . . እያልን እንደምንጠራው ሁሉ በሥጋዌው ምክንያት:- አማኑኤል: መድኃኔ ዓለም: ኢየሱስ: ክርስቶስ እያልን እንጠራዋለን::

+*" ዕለተ ጌና "*+

=>ከሳምንታት በፊት ጀምረን የክርስቶስን የማዳን ሥራ ለመገንዘብ እየሞከርን ቆይተናል:: በተለይ ታኅሳስ 7 ቀን "ስብከት" በሚል ስለ እግዚአብሔር ሰው መሆን ትንቢት መነገሩን: ምሳሌ መመሰሉን: ሱባኤ መቆጠሩን ተመልክተን ነበር::

+ቀጥለን ደግሞ ታኅሳስ 14 ቀን "ብርሃን" በሚል አምላካችን እንደ ምን ባለ ጥበቡ ብርሃኑን እንደ ሰጠን: አንድም ወደን ወደ ጨለማ በገባን ጌዜ ሥጋችንን ተዋሕዶ ብርሃን እንደ ሆነልን ለማየት ሞክረናል::

+ታኅሳስ 21 ቀን ደግሞ በበደላችን ምክንያት የነፍሳችንን እረኛ አጥተን ነበር:: ለእኛው በደል እርሱ ክሶ ድጋሚ መልካም እረኛችን ሆኖ በሥጋ ማርያም መለገለጡን አየን:: የዛሬው በዓል ዕለተ ጌና ደግሞ ማሠሪያው ነው::

+"ጌና" ማለት በቁሙ "ዕለተ ልደት ስቡሕ: ማለትም አምላክ ሰው የሆነበት ምስጉን ቀን" እንደ ማለት ነው:: ይህ ቀን ሁሌም በየዓመቱ "አማኑኤል (ጌና)" እየተባለ ይከበራል:: ምክንያቱ ደግሞ ጌታ የተጸነሰ መጋቢት 29 ቀን በመሆኑና ከዚህ ቀን 9 ወር ከ5 ቀናት ብንጨምር ይህ ዕለት ታሕሳስ 29 ቀን ይመጣል::

+ነገር ግን በ4ኛው ዓመት ዘመነ ዮሐንስ ዻጉሜን 6 ስትሆን 9 ወር ከ6 ቀን ስለሚሆን ቀኑን እንዳይለቅ በዘመነ ዮሐንስ ዕለተ ልደቱ ለክርስቶስ ታሕሳስ 28 ቀን ይከበራል:: ያም ሆኖ በዘመነ ዮሐንስ ታኅሳስ 28ን አክብረናል ብለን 29ን አንተወውም:: እርሱም ይከበራል::

+በዚያው ልክ ደግሞ በ3ቱ አዝማናት (በማቴዎስ: በማርቆስና በሉቃስ) ልደቱ በ29 ነው ብለን 28ን አንሽረውም:: "ጌና-አማኑኤል-ዕለተ ማርያም" እያልን እናከብረዋለን እንጂ:: ብዙ ጊዜም በተለምዶ በዓለ ልደትን "ጌና" በማለት ፈንታ "ገና" የምንል ብዙዎች አለን::

+ግን አበው ባቆዩልን ትውፊት "ጌና" ልደቱን የሚመለከት ሲሆን "ገና" ግን ባሕላዊ ጨዋታውን የሚመለከት ቃል ነው::

+*" ዕለተ ማርያም "*+

=>ዳግመኛ ይህ ቀን ዕለተ ማርያም ይባላል:: "ማርያም" የሚለው ቃል ብዙ ትርጉምን ያዘለ የእናታችንና የእመቤታችን: የተስፋችንና መመኪያችን: የድንግል እመ ብርሃን ስም ነው::

+ክርስቶስ ተጸነሰ-ተወለደ ስንል ለዚህ ሁሉ ምሥጢር ማካተቻና የድኅነታችን መጀመሪያ: የመመኪያችን ዘውድና የንጽሕናችን መሠረት ድንግል ማርያም ናትና ከፈጣሪ ቀጥሎ ታላቅ ክብር: ምስጋና: ስግደትና ውዳሴ ለእርሷ ይገባታል:: መድኅናችን ክርስቶስ ያዳነን በእርሷ ምክንያት ነውና::

+ሠለስቱ ምዕት (318ቱ ቅዱሳን ሊቃውንት) ይህንን ምሥጢር ሲያደንቁ እንዲህ ብለዋል:-
*በሥጋ ማርያም ጌታ ተጸነሰ
*በሥጋ ማርያም ጌታ ተወለደ
*በሥጋ ማርያም ጌታ አደገ
*በሥጋ ማርያም ጌታ ተጠመቀ::