2022-07-05 12:26:30
" በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ::
አሜን:: ""
+* " ቅዱስ ያዕቆብ ዘእልበረዲ (እል-በረዳይ)
(በተለይ በሃገራችን የተዘነጋ የሚመስለው የምሥራቅ ኮከብ -
ኮከበ ጽባሕ)
=>"ያዕቆብ" ለሚል ስም ትርጉምን የሰጡ አበው በ2 መንገድ
ያትቱታል::
1.አኃዜ ሰኮና:: ነገሩ ከወልደ ይስሐቅ ወርብቃው ርዕሰ አበው
ያዕቆብ ጋር የተያያዘ ቢሆንም አበው ግን ለትህትና
ይተረጉሙታል::
2.አእቃጺ / አሰናካይ:: ነገሩ ስድብ (አሉታዊ) ይምሰል እንጂ
በዚህ ስም የተጠሩ አበው ሁሉ ለአጋንንትና ለመናፍቃን ትልቅ
መሰናክል ሆነውባቸው ኑረዋልና አባባሉ ምስጋና እንጂ ነቀፋን
አይወክልም::
+የ6ኛው መቶ ክ/ዘመን ምሥራቃዊ ኮከብ ቅዱስ ያዕቆብም
ለመለካዊ መናፍቃንና ለተዋሕዶ ተገዳዳሪዎች ትልቅ መሰናክል
ሆኖባቸዋል:: የቀናችውን ቀርነ ሃይማኖትንም አጽንቷል::
+ብዙ ጊዜ "ዘ"-እልበረዲ መባሉን ይዘው በ"ዘ" ምክንያት
እልበረዲን እንደ ሃገር የቆጠሯት አልጠፉም:: በረከታቸው
ይድረሰንና ትጉሑ ዻዻስ አቡነ ጐርጐርዮስ ካልዕ ግን ለዚሁ
መላምት "የለም!" ባይ ናቸው::
+'የቤተ ክርስቲያን ታሪክ በዓለም መድረክ' በተሰኝ ተወዳጅ
መጽሐፋቸው "እል-በረዲ" ማለትን በዓረብኛ ከሠጋር በቅሎ :
ከሥሙር ሠረገላ ጋር አነጻጽረው አስቀምጠውታል:: ለምን ቢባል
- እንደ ሠረገላ በተፋጠነ አገልግሎቱ ወዳጅንም ጠላትንም
አስደምሟልና::
+ቅዱስ ያዕቆብ የተወለደው በ6ኛው መቶ ክ/ዘመን መጀመሪያ
(በ500 አካባቢ) ሲሆን ያረፈው ደግሞ በ578 ዓ/ም እንደሆነ
ይታመናል:: ነገሩን ልብ ስንለው ቅዱስ ማኅሌታይ ያሬድን -
ወዲህ በዘመን : ወዲያ ደግሞ በአገልግሎት ይመስለዋል::
እርግጥ ነው ለውለታው የሶርያ ቤተ ክርስቲያን "ያዕቆባዊት"
ስትባል የእኛዋስ ምናለ "ያሬዳዊት" ብትባል የሚል ቁጭትን
ያመጣል::
+ጊዜው (5ኛውና 6ኛው መቶ ክ/ዘመን) ወዲህ ወርቃማ :
ወዲያ ደግሞ ጨለማ ተብሎ ሊጠራ የሚችል ዘመን ነበር::
¤በብርሃንነቱ በተለይ በምሥራቁ ዓለም ያበሩ አበው እነ ያዕቆብ
ዘስሩግ : ሳዊሮስ ዘአንጾኪያ : ያዕቆብ ዘእልበረዲን የመሰሉ
አበው ተገኝተውበታል:: ሲያልፍ ደግሞ ዘይኑንና አንስጣስዮስን
የመሰሉ ደጋግ ነገሥታት በዘመኑ መነሳታቸውን እናስባለን::
+በተቃራኒው ግን ዘመኑ ቤተ ክርስቲያን ለ2 የተከፈለችበት :
መለካውያን የነገሥታቱ ደጀን አላቸውና ተዋሕዶ ሃይማኖትን
ከሥሯ ነቅሎ ለማጥፋት ብዙ የሞከሩበት ዘመን ነውና ጨለማነቱ
ይጐላብናል::
+በእርግጥም ከመርቅያን እስከ ዮስጢኖስ ዳግማዊ ዘመን
ድረስ ለ100 ዓመታት መለካውያኑ የልዮን ልጆች 2 ባሕርይ
ማለትን ሊያሰፉ : ተዋሕዶንም ሊያጠፉ የከፈቱት ዘመቻ ሊሳካ
ጫፍ የደረሰ ይመስል ነበር::
+ግን አማናዊት ቤቱን የማይተው አማናዊው ጌታ መድኃኔ
ዓለም አርመኖቹን ስቦ በ490ዎቹ ወደ መንጋው ቀላቀለ::
በግብጽ አባ ቴዎዶስዮስን : በሶርያ ደግሞ ታላቁን ሊቅ ቅዱስ
ሳዊሮስን አስነስቷል:: ከቤተ መንግስትም ስም አጠራሯ ያማረ
ንግሥት ታኦድራን ማርኯል:: በእነዚህ ቅዱሳን ትጋት
የለመለመችው ተዋሕዶ እንደ ቅዱስ ያዕቆብ ዘእልበረዲ ያለ
አርበኛን ግን ያገኘችው በጭንቅ ቀን ነበር::
+ሰው መሆን ሰው በጠፋባቸው ቀናት ነውና : በግብጽና
በቁስጥንጥንያ በትምህርትና ምናኔ ላይ የነበረው ቅዱሱ ታጥቆ
ለአገልግሎት የተሰለፈው በ530ዎቹ አካባቢ ነበር::
+ጊዜው ወዲህ አንበሳው ቅዱስ ሳዊሮስ ከሶርያ ወደ ግብጽ
እንደተሰደደ ያረፈበት ነበር::
ወዲያ ደግሞ ሊቁ አባ ቴዎዶስዮስ የግብጹ ለግዞት የተዳረገበት
ነበርና የተዋሕዶ ምዕመናን ያለ እረኛ ተቅበዘበዙ:: የቤተ
መንግስቱ ተጽዕኖ ደግሞ 2 ባሕርይ በማይሉት ላይ እሥራትና
ግድያን ወደ ማወጅ ተሸጋግሯልና የምእመናን ቁጥር እጅጉን
መመንመኑ ቀጠለ::
+ይህ ዕረፍት የነሳው ቅዱስ ያዕቆብ በበኩሉ ነገሩን በዝምታ
ሊያልፈው አልወደደምና አገልግሎቱን አሰፋ:: ሌሊቱን በጸሎት
ያድራል:: ቀን በቤተ ክርስቲያን አካባቢ ማስተማር ባይችል
በየቦታው እየዞረ ያስተምር ነበር::
+ከትምህርቱ ጣዕምና ከመልእክቱ ሥምረት የተነሳም ምእመናን
እንደገና ተነቃቁ:: እርሱም ከግብጽ እስከ ሶርያ : አልፎም እስከ
ቁስጥንጥንያ ድረስ ያለ ዕረፍት ሲሰብክ 40 ዘመናትን አሳለፈ::
በተለይ አዲስ አማኞችን ያጠምቅ ዘንድ በእሥረኛው ቅዱስ
ቴዎዳስዮስ ኤዺስ ቆዾስነትን ተቀብሏል::
+የሶርያ (አንጾኪያ) የፕትርክና መንበሩ ክፍት ሆኖ እርሱን
ቢጠብቀውም እርሱ ግን የዚህ (የስልጣን) ፈላጊ አልነበረምና
ሌሎች እንዲሾሙበት አድርጉዋል::
+ቅዱስ ያዕቆብ በስብከት አገልግሎት ምሥራቁን ዓለም ሲያበራ
የተባበሩት ደቀ መዛሙርት ቢኖሩም ያሳለፈው ድካምና መከራ
ግን ተወዳዳሪ አልነበረውም:: በተለይ የወቅቱ የአንጾኪያ ኃያላን
መኩዋንንትና ሹመኛ መናፍቃን ብዙ አሳደውታል::
+እርሱ ግን በጥበብና በፈሊጥ እዚያው ደጃቸው ላይ የነበሩ
ምዕመናንን በእረኝነት ጠብቁአል:: ለዚህ ሲባልም ራሱን
እየቀያየረ የመሣፍንቱን አጥሮችና ቅጥሮች አልፏል:: ለቤተ
ክርስቲያን ክብርም እንደ እብድ : እንደ ሴትም መስሎ የወንጌልን
ዘር ዘርቷል::
¤ከብዙ ፈተናና አገልግሎት በሁዋላም በተወለደ በ78 ዓመቱ
(በ578 ዓ/ም) ዐርፎ በክብር ተቀብሯል::
¤ትልቁ መታሰቢያው የሶርያ ቤተ ክርስቲያን "ያዕቆባዊት" :
ምዕመኑ "ያዕቆባውያን" መባላቸው ሲሆን እኛ ደግሞ
በአንገታችን ላይ እንድናስራት ባስተማረን ማዕተብ (ማኅተም)
ዘወትር እናስበዋለን:: ለመጀመሪያ ጊዜ ማዕተብን በአንገት ላይ
ስለ ማሰር ያስተማረ እርሱ ነውና::
¤የምሥራቁን ኮከብ እል-በረዲ ያዕቆብን በየዓመቱ ሰኔ 28 ቀን
በነገረ ቅዱሳን መደበኛ ጉባኤ (ጐንደር) እናከብራለን::
ሶርያውያን ደግሞ July 31 (ሐምሌ 24 ቀን) ያከብሩታል::
=>+"+ እናንተ የምድር ጨው ናችሁ . . . እናንተ የዓለም
ብርሃን ናችሁ:: በተራራ ላይ ያለች ከተማ ልትሠወር
አይቻላትም:: መብራትንም አብርተው በዕንቅብ በታች አይደለም
እንጂ በመቅረዙ ላይ ያናሩታል:: በቤት ላሉት ሁሉም ያበራል::
መልካሙን ሥራችሁን አይተው በሰማያት ያለውን አባታችሁን
እንዲያከብሩ ብርሃናችሁ እንዲሁ በሰው ፊት ይብራ:: +"+
(ማቴ. 5:13-16)
=>አምላከ ቅዱስ ያዕቆብ ተዋሕዶ ሃይማኖታችን ይጠብቅልን::
ከቅዱሱ በረከትም አይለየን::
107 views09:26