Get Mystery Box with random crypto!

ለበይክ አላሁመ ለበይክ ~ ሐጅ የኢስላም ልዩ መስህብ የሚሰተዋልበት፣ ድንቅ የአላህ ተዐምር የሚታይ | Ibnu Munewor (ኢብኑ ሙነወር)

ለበይክ አላሁመ ለበይክ
~
ሐጅ የኢስላም ልዩ መስህብ የሚሰተዋልበት፣ ድንቅ የአላህ ተዐምር የሚታይበት፣ የተውሒድ ነፀብራቅ ጎልቶ የሚነግስበት፣ ባእድ አምልኮ ከፍ ባለ ድምፅ ባደባባይ የሚወገዝበት ድንቅ ስርአት ነው። ሴት ወንዱ፣ ነጭ ጥቁሩ፣ መሪው ተመሪው በተመሳሳይ ቦታ እኩል ለአላህ የሚሰለፍበት ትንግርት። ሐጅ - አምስተኛው የኢስላም ምሰሶ።
በሐጅ "በሰዎችም ውስጥ በሀጅ ትእዛዝ ተጣራ" ለሚለው የአላህ ጥሪ “ለበይክ አላሁመ ለበይክ፣ ለበይከ ላሸሪከ ለከ ለበይክ፣…” /አቤት ጌታችን ሆይ አቤት፣ አቤት ጥሪህን ተቀብለን መጥተናል/” እያሉ መልስ በመስጠት ሚሊዮኖች ይተማሉ።
* ከዚያ ጭው ካለ በረሃ “ከአላህ ሀገራት ሁሉ ይበልጥ አላህ ዘንድ የተወደድሽ ነሽ። ከአላህ ሀገራት ሁሉም እኔ ዘንድ የተወደድሽ ነሽ። ህዝቦችሽ ካንቺ ባያስወጡኝ ኖሮ አልወጣም ነበር” የሚለውን የነብዩን ﷺ የቁጭት ንግግር፣ አሜኬላ የበዛበት ህይወታቸውን ልበዎ በሀዘን እየተከፈለ ያስታውሳሉ።

* ከዚያ ጭው ካለ በረሃ አስራ አራት ክፍለ-ዘመናት ወደ ኋላ አጠንጥነው የተውሒድ ጮራ ሲፈነጥቅ በአይነ-ህሊናዎ ይመለከታሉ።
* ከዚያ ጭው ካለ በረሃ የመካ ሙሽ - ሪኮችን ለከት የለሽ ጭካኔና የነዚያን ፈርጥ የሆኑ ሰሐቦች ከብረት የጠነከረ ፅናት እያሰቡ በትዝታ ይነጉዳሉ።
* ከዚያ ጭው ካለ በረሃ የነ ቢላልን ስቃይ፣ የነ ሱመያን የጣር ድምፅ አይነዎ እንባ እያቀረረ በሰመመን ያያሉ። ልበዎ በቁጭት እየደማ ይሰማሉ።
* ከዚያ ጭው ካለ በረሃ የአላህ የመጀመሪያ ቤት አለ - የሙስሊሞች ቂብላ፣ ከአለም ሁሉ ምርጡ ቦታ፣ መካ።
إِنَّ أَوَّلَ بَيْتٍ وُضِعَ لِلنَّاسِ لَلَّذِي بِبَكَّةَ مُبَارَكًا وَهُدًى لِلْعَالَمِينَ (96) فِيهِ آيَاتٌ بَيِّنَاتٌ مَقَامُ إِبْرَاهِيمَ وَمَنْ دَخَلَهُ كَانَ آمِنًا
"በርግጥም ለሰው ዘር (መፀለያ) ሆኖ መጀመሪያ (ምድር ላይ) የተኖረው ቤት ያ በበካህ (በመካ) ያለው የተባረከና ለዓለማት ሁሉ መመሪያ የሆነው ነው። በውስጡ (እንደ) የኢብራሒም መቆሚያ (ያሉ) ግልፅ የኾኑ ተዓምራቶች አልሉ። ወደ ውስጡ የገባም ሰው ደህንነቱ የተጠበቀ ሆኗል።" [ኣሊ ዒምራን፡ 96]

- መስጂደል ሐራም መጤው ካገሬው እኩል የሚሆንበት ተአምራዊ ቦታ። የተውሒድ ቦታ፣ የእዝነት ቦታ። የኢብራሂም፣ የሐጀር፣ የኢስማዒል ትዝታ።
- መስጂደል ሐራም በረከት የበዛበት፣ ሰላም የሰፈነበት፣ እዝነት የነገሰበት፣ ተውሒድ የፈነጠቀበት ቅዱስ ቦታ።
- መስጂደ ልሐራም ልቦች ዘወትር የሚናፍቁት፣ አይኖች አይተውት የማይጠግቡት፣ ያላዩት ሊያዩት የሚቋምጡት ድንቅ ቦታ።
- መስጂደል ሐራም! “የማያውቁት ሀገር አይናፍቅም” የሚለው ሀገርኛ ብሂል ፉርሽ የሚሆንበት ልዩ መስህብ። ለካስ ይናፍቃል! ደካማ አዛውንቶች በሽተኞች ሳይቀሩ ህመም ድካማቸውን ረስተው፣ ስቃይ እንግልቱን ዘንግተው፣ ባላዩት ሀገር ናፍቆት ተብሰክስከው፣ እልፍ አእላፍ ማይሎችን አቋርጠው ይተማሉ።
وَإِذْ بَوَّأْنَا لِإِبْرَاهِيمَ مَكَانَ الْبَيْتِ أَنْ لَا تُشْرِكْ بِي شَيْئًا وَطَهِّرْ بَيْتِيَ لِلطَّائِفِينَ وَالْقَائِمِينَ وَالرُّكَّعِ السُّجُودِ
"ለኢብራሂምም የቤቱን (የካዕባን) ስፍራ መመለሻ ባደረግንለት ጊዜ “በኔ ምንንም አታጋራ፣ ቤቴንም ለሚዞሩትና ለሚቆሙበት ሩኩዕ ሱጁድ ለሚያበዙት ንፁህ አድርግላቸው” (ባልነው ጊዜ አስታውስ)።" [አልሐጅ፡ 26]
ከዕባ፣ ሐጀረል አስወድ፣ መቃም ኢብራሂም፣ ሶፋና መርዋ፣ ሚና፣ ዐረፋ፣ ሙዝደሊፋ፣… የሙስሊሞችን ቀልብ የሚማርኩ ልዩ የዒባዳ አውድማዎች ናቸው። ተልቢያ፣ ጦዋፍ፣ ሶላት፣ ዱዐ፣ እርድ፣ የጠጠር ውርወራ፣… ለፈፀማቸው ቀርቶ ለተነገረው የሚያጓጉ ሐጅ ላይ የሚፈፀሙ፤ ተቅዋን የሚያላብሱ የዚያኛው ዓለም ስንቆች ናቸው። (ذَلِكَ وَمَنْ يُعَظِّمْ شَعَائِرَ اللَّهِ فَإِنَّهَا مِنْ تَقْوَى الْقُلُوبِ)
ቡኻሪና ሙስሊም በዘገቡት ሐዲሥ አላህ አድሎት የተዋጣለት ሐጅ ያደረገ እናቱ ስትወልደው እንደነበረው እንደ ህፃንነቱ ከወንጀል ሙሉ በሙሉ እንደሚፀዳ ነው መልእክተኛው ﷺ ያመላከቱት። በሐጅ ልቦች በኢማን ይታደሳሉ፣ አማኞች ከወንድሞቻቸው ጋር ይተዋወቃሉ፣ ደካሞች ይታገዛሉ፣ ሙስሊሞች ከቅዱሱ ስፋራ፣ ከበረሃው፣ ከሐጁ ስርአት፣ ከተዳሚው ሁኔታ፣ ከዚያ የሚሊዮኖች ስብሰባ ብዙ ተፈኩር ይወስዳሉ።
አላህ አድሎት የሐጅ ስነ-ስርኣት ላይ ለተካፈለ ሰው ልብሳቸው የበሰበሰ፣ ሰውነታቸው የኮሰሰ፣ ኑሮ ያጎሳቆላቸው ስንት አይነት ሰዎችን ከተለያዩ የአለም አፅናፋት ታድመው ይመለከታል። አንዳንዶቹ ለዘመናት አጠራቅመው ለዚህ ስኬት እንደበቁ ሲቃ እየተናነቃቸው ይናገራሉ። በተሽከርካሪ ወንበር የሚገፉ፣ በጀርባ የታዘሉ አዛውንቶችን ሲመለከቱ፣ አቅሙም ጤናውም ተሟልቶ ከሐጅ ስለቀረው ወገን በእጅጉ ያዝናሉ። ሐጅ የወጀበባችሁ ወገኖቼ ሆይ! ጤናን አቅምን ያደላችሁ ጌታ፣ ሐጅን ግዴታ አድርጎባችኋል። ወንድሞቼ እህቶቼ፣ አባቶቼ እናቶቼ ሆይ! ለአላማ እንደተፈጠራችሁ አትዘንጉ። የተሰጣችሁ ገንዘብ ያንን አላማ ማሳኪያ እንጂ መጎረሪያም መባከኛም አይደለም። ሐጁን ብትፈፅሙት ጥቅሙ ለራሳችሁ ነው። ወንጀላችሁ ይረግፋል፣ ልባችሁ ይፀዳል፤ የዒባዳ ወኔያችሁ ይነሳሳል። እመኑኝ አንዴ ቆርጣችሁ ከፈፀማችሁት በያመቱ ገና ጊዜው ሲቃረብ ነው ልባችሁ የሚቆመው። “ወዴት” እንዳትሉኝ። ወላሂ ስንቶች ናቸው ሐጅ አጠናቀው መካን ሲለቁ፣ በእንባ የሚታጠቡት! ባትፈፅሙትስ ማነው የሚጎዳው? በርግጠኝነት አላህ ምንም አይቀርበትም! መቼስ ከሚታረደው እርድ አይደርሰው ነገር! ያበላል እንጂ አይበላምና። ከፍጡር ሁሉ የተብቃቃ ጌታ ነውና።
وَلِلَّهِ عَلَى النَّاسِ حِجُّ الْبَيْتِ مَنِ اسْتَطَاعَ إِلَيْهِ سَبِيلًا وَمَنْ كَفَرَ فَإِنَّ اللَّهَ غَنِيٌّ عَنِ الْعَالَمِينَ
"ለአላህም በሰዎች ላይ ወደርሱ መሄድን በቻለ ሁሉ ላይ ቤቱን መጎብኘት ግዴታ አለባቸው። የካደም ሰው አላህ ከዓለማት ሁሉ የተብቃቃ ነው።" [ኣሊ ዒምራን: 97]
ዱዓቶች ሆይ ሰዎችን ቀስቅሱ። አላህ የጣለባችሁን ሀላፊነት አድርሱ። ተሳክቶላችሁ በናንተ ሰበብ አንድ ሰው ለሐጅ ቆርጦ ቢነሳ የሚኖራችሁን አጅር አስታውሱ። ወገን ወደ ግራም ወደ ቀኝም ተመልከት። ከራሳችን፣ ከቤተሰብ፣ ከጎረቤት ብዙ ሐጅ ያላደረጉትን ፍቀድ። ዘንድሮ ባይደርስ ለቀጣይ አስታውስ። "አስታውስ ማስታወሱ አማኞችን ይጠቅማልና።" [አዛሪያት፡ 55]
ባይሆን አደራ!
ለሐጅ ቆርጠው ከተነሱ፡- በሚገባ ይዘጋጁ። ስለሐጅ ይጠይቁ፣ ይወቁ፣ ያንብቡ፣ የሚያነቡትም ይያዙ። ከተቻለም ቀድሞ ሐጅ ያደረገ የዲን ግንዛቤ ያለው ሰው ጓደኛ ማድረገዎን አይርሱ።
"ወደ ኸይር ያመላከተ (ኸይሩን) እንደሚሰራው ሰው ነው (አጅሩ አለው)" ይላሉ ነብዩ ﷺ።

ለበይክ አላሁመ ለበይክ
ለበይከ ላሸሪከ ለከ ለበይክ
ኢነል ሐምደ
ወኒዕመተ
ለከ ወልሙልክ
ላሸሪከ ለክ!
.
ያ ረሕማኑ ቤትህን ለመጎብኘት አንተ ወፍቀን።
(ኢብኑ ሙነወር፣ ጳጉሜ 3/2006)
=
የቴሌግራም ቻናል
https://t.me/IbnuMunewor