Get Mystery Box with random crypto!

በቂያማ ትርምስ መሀል ድንገት ተጣሪ ስምህን ከሰዎች ለይቶ በጩኸት ይጠራኻል። ትርበተበታለህ፣ ትወለ | HAppy Mûslim

በቂያማ ትርምስ መሀል ድንገት ተጣሪ ስምህን ከሰዎች ለይቶ በጩኸት ይጠራኻል። ትርበተበታለህ፣ ትወለጋገዳለህ፣ እግሮችህ አንተን መሸከም ይሳናቸዋል።

ያሳለፍከውን የአመፅ ህይወት እያወራረድክ በመላዕክት ተቀፍድደህ ከተጠራህበት ስፍራ ላይ ብቻህን እንድትቆም ትደረጋለህ።

ስትፈራ፣ ስትቸር፣ ስትርበተበት አንገትህን አቀርቅረህ የምትገፈተርበትን የጀሀነም ሸለቆ እያሰብክ ሳለ ድንገት ከፊትህ መዛግብት ይዘረጋልኃል።

አንዱ መዝገብ የአይንህን አድማስ ተሻግሮ ትመለከተዋለህ። ጫፉን አታየውም፣ ትደነግጣለህ። የሱ ድንጋጤ ሳይለቅህ ሌላ ተመሳሳይ 99 መዝገቦች ከፊትህ ይዘረጋጋሉ።

ውስጡን እንድታይ ትደረጋለህ፤ ስትመለከተውም ከህይወት ጅማሬ እስከፍፃሜው የቀጠፍካቸው ወንጀሎች በሙሉ ሰፍረው መልካም ስራዎችህን ውጠዋቸው ታገኘዋለህ።

ተስፋ ትቆርጣለህ፣ አፍህ ይሎገማል፣ ጀሀነም ላይ ክፍል እንደተዘጋጀልህ ታስባለህ። ያኔ አፈር ሁነህ ብትቀርም ትልቁ ምኞትህ ይሆናል።

ድንገት የመዝገቦቹ ተሳሳቢህ፦‹‹የምታስተባብለው አለን?›› ሲል ይጠይቅኃል!
ተስፋ በቆረጠ አንደበት፦‹‹አላስተባብልም›› ብለህ በገዛ ነፍስህ ላይ ምስካሪ ትሆናለህ።

‹‹መዝጋቢዎቹስ በድለውኃልን›› ብሎ ዳግም ይጠይቅኃል?
አንገትህን እንዳቀረቀርክ፦‹‹አልበደሉኝም›› ትላለህ ስራህን ስለምታውቅ።

‹‹ታድያ በምን ታስተባብላለህ? ከዚህ ሚታደግህ መልካም ትግበራ ይኖርሃል? ›› ብሎ ይጠይቅኃል።

‹‹የለኝም›› ትላለህ ሁሉ ጨልሞብህ።
‹‹አንድ መልካም ስራ እኛ ዘንድ አለችህ፤ እሷም ትመዘናለች ዛሬ እኛ ዘንድ ማንም አይበደልም›› ይልህ ና አንዲት ብጣሽ ወረቀት ይመዝልኃል።

‹‹ጌታዬ እሷን ባትመዝናትስ? ይኼን ሁሉ የሀፅያት መዝገብ ከዚህች ብጣሽ ወረቀት ልታመዛዝን›› ትለዋለህ።

ንግግርህ ወድያ ተትቶ ሚዛንህ ላይ አድማሳትን ያካለለው የሀፅያት መዛግብትና ይህች ብጣሽ ወረቀት ይጫናሉ። ብጣሿ ወረቀት ያን ሁላ መዛግብት ከመመዘን አልፈም መዛግብቱን ትበታትናቸዋለች በሰማይህም ላይ ይበታተናሉ።

ደስታ ምትሆነውን ያሳጣኃል፣ ተስፋህ ይለመልማል፣ ህይወት ታጓጓኃለች፣ ዕጣፋንታህን ቀይራ ለጀነት የዳረገችህን ወረቀት ስትመለከትም የጌታህን እና የነበይህን ስም ተፅፎበት ታገኘዋለህ።

‹‹ላ ኢላሃ ኢለላህ ሙሐመዱን ረሱሉላህ››

@heppymuslim29