2022-08-24 22:30:39
እንኳን ለቅዱሳን አበው አባ መቃርስ፣ ቅዱስ አብርሃምና ቅዱስ ፊንሐስ ዓመታዊ በዓል በሰላም አደረሳችሁ፤ አደረሰን።
†††በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
ወንድሞቻችሁ እና እህቶቻችሁ እንዲያነቡት ተጋሩት(share it)
በዲያቆን ዮርዳኖስ አበበ
<3 ታላቁ ቅዱስ መቃርስ <3
ታላቁ ቅዱስ መቃርስ (መቃሬ) "ጽድቅ እንደ መቃርስ" የተባለለት፣ የመነኮሳት ሁሉ አለቃ፣ ከሰማንያ ዓመታት በላይ በበርሃ የኖረ፣ በግብጽ ትልቁን ገዳም (አስቄጥስን) የመሠረተ፣ ከሃምሳ ሺህ በላይ መነኮሳትን ይመራና ይመግብ የነበረ ፍፁም ጻድቅ ነው።
በአራተኛው መቶ ክፍለ ዘመን አርዮሳውያን ደጉን ታላቅ አባት በሰንሰለት አስረው ከግብጽ ወደ እስያ በርሃ ከጓደኛው ቅዱስ መቃርዮስ እስክንድርያዊ ጋር አሰድደውታል። በዚያ ለሁለት ዓመታት ስቃይን ከተቀበሉ በኋላ በአረማውያን ፊት ድንቅ ተአምር አድርገው አረማውያንን ከነንጉሣቸው አጥምቀዋል።
በተሰደዱባት ሃገርም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ (ስም አጠራሩ ይክበርና።) እመቤታችንን፣ ቅዱሳን ሐዋርያትን፣ አዕላፍ መላእክትን፣ በተለይ ደግሞ ቅዱሳኑን ዳዊትን፣ ዮሐንስ መጥምቁንና ወንጌላዊውን፣ ማርቆስን፣ ጴጥሮስን፣ ጳውሎስን አስከትሎ ወርዶ ተገልጦላቸዋል። በቅዱስ አንደበቱም የምሕረት ቃል ኪዳን ገብቶላቸዋል።
ታላቁ ቅዱስ መቃርስና መቃርዮስ ከሁለት ዓመታት ስደትና መከራ በኋላ ስደት በወጡባት ዕለት መልአኩ ኪሩብ በክንፉ ተሽክሞ ወደ ግብጽ መልሷቸዋል። በወቅቱም ጻድቁን ለመቀበል ከሃምሳ ሺህ በላይ የሚሆኑ ልጆቻቸው መነኮሳት በዝማሬ ወጥተዋል።
ይህች ዕለት ለአባታችን መቃሬ በዓለ ፍልሠቱ ናት።
ይህስ እንደ ምን ነው ቢሉ፦
ታላቁ ቅዱስ መቃርስ ካረፈ በኋላ ከክቡር ሥጋው ብዙ ተአምራት ይታዩ ነበርና የሃገሩ (የሳስዊር) ሰዎች ሊወስዱት ፈለጉ። ሳስዊር ማለት ቅዱሱ ተወልዶ ያደገባት ወላጆቹ (አብርሃምና ሣራ) የኖሩባት ቦታ ናት።
የምትገኘውም ግብጽ ውስጥ ነው።
በምድረ ግብጽ በተለይም በገዳመ አስቄጥስ የአባ መቃርስን ያህል ክቡርና ተወዳጅ የለምና የሃገሩ ሰዎች የነበራቸው አማራጭ መስረቅ ነበር። መሥረቅ ኃጢአት ቢሆንም እነርሱ ግን ስለ ፍቅር አንድም ለበረከት (በረከትን ሲሹ) አደረጉት።
ወደ ሳስዊርም ወስደው ቤተ ክርስቲያን በቅዱሱ ስም አንጸው በክብር አኖሩት። በዚያም ለመቶዎች ዓመታት ተቀመጠ። በሰባተኛው መቶ ክፍለ ዘመን ግን ተንባላት (እስላሞች) መጥተው ቤተ ክርስቲያኑን አጠቁ። በዚህ ጊዜም ሕዝቡ የጻድቁን አጽም ይዘው ሸሹ። በሌላ ቦታም እንደ ገና በስሙ ቤተ ክርስቲያን አንጸው በዚያ አኖሩት።
በእነዚህ ሁሉ ዓመታት የመንፈሳዊ አባታቸውን ሥጋ ያጡት የገዳመ አስቄጥስ ቅዱሳን ያዝኑ ይጸልዩ ነበርና ልመናቸውን ፈጣሪ ሰማ። አባ ሚካኤል ሊቀ ጳጳሳት በነበረበት ዘመን ከገዳሙ ለሌላ ተግባር ወደ ሳስዊር የተላኩ አበው ከታላቁ አባት ቤተ ክርስቲያን ሲደርሱ ሰውነታቸው ታወከ።
ይዘው ለመውሰድ ሙከራ ቢያደርጉ ሊሳካላቸው አልቻለም። ምክንያቱም የቤተ ክርስቲያኑ ጠባቂ ደወል ደውሎ ሕዝቡን ሁሉ ጠርቶ ነበርና። ሕዝቡና ሃገረ ገዢው የሆነውን ሲሰሙ "የቅዱሱን ሥጋ ብትነኩ እንገላችኋለን።" ብለው ሰይፍ፣ ዱላ፣ ጐመድና ጦር ይዘው መጡባቸው።
መነኮሳቱ ግን ባዷቸውን ሊመለሱ አልፈቀዱምና ሌሊቱን ሲያለቅሱና ሲጸልዩ አደሩ። መንፈቀ ሌሊት በሆነ ጊዜም ታላቁ መቃርስ በግርማ ወርዶ መኮንኑን "ለምን ወደ ልጆቼ እንዳልሔድ ትከለክለኛለህ?" ሲል በራእይ ተቆጣው። በዚህ ምክንያትም መነኮሳቱ የቅዱሱን ሥጋ ተቀበሉ።
ሕዝቡም በዝማሬና በማኅሌት ከብዙ እንባ ጋር ሸኟቸው። ታላቁ መቃሬ ወደ ገዳሙ ሲደርስም ታላቅ ደስታ ተደረገ። ቅዱሳን ልጆቹ ከመንፈሳዊ አባታቸው ተባርከው በክብር አኑረውታል። ይህ የተደረገው በዚህች ዕለት ነው።
<3 አባታችን ቅዱስ አብርሃም <3
የሃይማኖት፣ የደግነት፣ የምጽዋትና የፍቅር አባት የሆነው አብርሃም ደጉ በዚህች ቀን ይታሠባል። በቤተ ክርስቲያን ትውፊት መሠረት የአብርሃም አባቱ ታራ ጣዖትን ይጠርብና ይሸጥ ነበር። ሽጦ ገንዘብ የሚያመጣለት ደግሞ ልጁ አብርሃም ነበር።
በዚያ ወራት አብርሃም እውነተኛውን አምላክ ፍለጋ ገብቶ ነበር። አንድ ቀን ጣዖቱን ሊሸጥ ወደ ገበያ እየሔደ የተሸከመውን እንጨት ይመራመረው ገባ። "አሁን ይሔ ምኑ ነው አምላክ!" እያለም ያደንቅ ገባ። መንገድ ላይም ደክሞት ካረፈበት "ለምን አልጠይቀውም።" በሚል አናገረው።
"እርቦኛል አብላኝ?" አለው። መልስ የለም። "እሺ አጠጣኝ?" አለው። አሁንም ያው ነው። "ባይሆን እሺ አጫውተኝ?" አለው። ጣዖቱ ተራ እንጨት ነውና መልሱ ዝምታ ነበር። ከዚያ ተነስቶ ወደ ገበያው ሲደርስ "ዓይን እያለው የማያይ ጆሮ እያለው የማይሰማ አምላክ የሚገዛ" እያለ ይጮህ ጀመር።
ይህን ሲሰሙ አንዳንዶቹ "የታራ ልጅ አብዶ" ሲሉ ሌሎቹ ደግሞ "እርሱ ያቀለለውን ማን ይገዛዋል።" ብለውት ሔደዋል። ከገበያ ሲመለስም ጣዖቱን ተመልክቶ አብርሃም እንዲህ አለ። "አንተ ቀድሞውን በዕለተ ሠሉስ የተፈጠርክ ዕፅ ነህ።" ብሎ ሰባበረው።
ወደ ቤቱ ሲመለስም ሁሉንም ጣዖታት ሠባበራቸው። ይህ የተደረገው ከሁለት ሺህ ዓመታት በፊት በዚህች ቀን ነው። የመንግሥተ ሰማያት አበጋዝ የእግዚአብሔር ወዳጅ አባታችን አብርሃም በመጨረሻው በውኃ፣ በነፋስ፣ በእሳትና በፀሐይ ተመራምሮ ፈጣሪውን አግኝቷል።
<3 ቅዱስ ፊንሐስ ካህን <3
ካህኑ ፊንሐስ የብሉይ ኪዳን ዘመን አገልጋይ ከነገደ ሌዊ የሊቀ ካህናቱ የአሮን የልጅ ልጅ ነው። አባቱም ሊቀ ካህናቱ አልዓዛር ነው። ፊንሐስ እስራኤል ከግብጽ ሲወጡ ሕፃን የነበረ ሲሆን አድጐ በመጀመሪያ ካህን አባቱ አልዓዛርና አያቱ አሮን ሲያርፉ ደግሞ ሊቀ ካህንነትን ተሹሟል።
አንድ ቀን በጠንቅ-ዋዩ በበለዓም ክፉ ምክር እስራኤላውያን ከሞዐብ ሴቶች ጋር በኃጢአት በመሳተፋቸው እግዚአብሔር ተቆጥቶ ነበር። ያጠፋቸው ዘንድም መቅሰፍት ተጀምሮ ሳለ ፊንሐስ ወንድና ሴት በደብተራ ኦሪቱ አንጻር የማይገባውን ሲሠሩ አያቸው።
ለፈጣሪው ቀንቶ በአንድ ጦር ሁለቱንም በአንድ ላይ ጥሏቸዋል። ያን ጊዜ ጌታ "አስተንፈስካ ለነፍስየ" ብሎታል። መቅሰፍቱም ተከልክሏል። በዚህም ምክንያት ካህኑ ፊንሐስ የሦስት መቶ ዓመት ዕድሜ ተጨምሮለት እግዚአብሔርን ሲያገለግል ኑሮ በዚህች ቀን ዐርፏል።
(ዘኁ. ፳፭፥፯ ፣ መዝ. ፻፭፥፴)
ለአበው ቅዱሳን የተለመነ አምላክ ለእኛም ይለመነን። ክብራቸውንም በእኛ ላይ ይሣልብን።
ነሐሴ ፲፱ ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት
፩.ተዝካረ ፍልሠታ ለማርያም ድንግል (አራተኛ ቀን)
፪.ታላቁ ቅዱስ መቃርስ (ፍልሠቱ)
፫.አባታችን ቅዱስ አብርሃም (ጣዖቱን የሰበረበት)
፬.ቅዱስ ፊንሐስ ካህን (ወልደ አልዓዛር)
ወርኀዊ በዓላት
፩.ቅዱስ ገብርኤል ሊቀ መላእክት
፪.ቅዱስ ኤስድሮስ ሰማዕት
፫.አቡነ ዓቢየ እግዚእ ጻድቅ
፬.አቡነ ሥነ ኢየሱስ
፭.አቡነ ዮሴፍ ብርሃነ ዓለም
"እግዚአብሔርም ለአብርሃም ተስፋ በሰጠው ጊዜ፦ 'በእውነት እየባረክሁ እባርክሃለሁ። እያበዛሁም አበዛሃለሁ።' ብሎ ከእርሱ በሚበልጥ በማንም ሊምል ስላልቻለ በራሱ ማለ። እንዲሁም እርሱ ከታገሠ በኋላ ተስፋውን አገኘ።"
(ዕብ ፮፥፲፫-፲፭)
ወስብሐት ለእግዚአብሔር
246 views19:30