Get Mystery Box with random crypto!

እንኳን ለቅዱስ እንድርያኖስ ሰማዕትና ለታላቁ አባ ቢጻርዮን ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳ | ገድለ ቅዱሳን Gedle Kidusan Acts of Saints

እንኳን ለቅዱስ እንድርያኖስ ሰማዕትና ለታላቁ አባ ቢጻርዮን ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ፤ አደረሰን።
†††በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
ወንድሞቻችሁ እና እህቶቻችሁ እንዲያነቡት ተጋሩት(share it)
በዲያቆን ዮርዳኖስ አበበ

<3 ቅዱስ እንድርያኖስ ሰማዕት <3

ቅዱሱ በሦስተኛው መቶ ክፍለ ዘመን የነበረ አረማዊ ሰው ሲሆን ከከሃዲው መክስምያኖስ ወታደሮችም አንዱ ነበር። "ሊቀ መሓዛት" ይሉታል፤ የጐበዛዝቱ አለቃም ነበር። ይህ ሰው ምንም ክርስቲያን አይሁን እንጂ በልቡ ቅንነት ተገኝቶበታል። እንደ አሕዛብ ልበ ድንጋይ አልነበረም።

በወጣትነቱም አንዲት ደመ ግቡ ሴት አግብቷል። ይህች ሴት 'ኤልያና' ስትባል የተባረከች ክርስቲያን ናት። እርሱ ግን አያውቅም። ከተጋቡ ከዓመታት በኋላ ጌታ እግዚአብሔር ስለ ሚስቱ ጸሎት በጐ ጐዳና ሊመራው ፈለገ።

እንድርያኖስ ሁሌም በየቀኑ ክርስቲያኖች ደማቸውን ሲያፈሱ ይመለከታል። የትእግስታቸው መጠንም ይገርመው ነበር። በተለይ አብዛኞቹ በመከራው ደስተኞች ነበሩ። ነገሩ ግራ ቢያጋባው ሃያ አራት ባልንጀሮች ሊገደሉ ወደ ታሠሩበት ቦታ ሒዶ ጠየቃቸው።

"ምን ልታገኙ ነው ግን ይህንን ሁሉ ስቃይ በአኮቴት (በምስጋና) የምትቀበሉት?" ቢላቸው "በሰማይ በክርስቶስ ዘንድ የሚጠብቀንን የክብር ሕይወት ሥጋዊ አንደበት አከናውኖ መናገር አይቻለውም። ዝም ብሎ 'ዕጹብ፣ ዕጹብ' እያሉ የሚያደንቁት ነው እንጂ።" አሉት።

እርሱም ተደላድሎ ተቀምጦ "እስኪ በደንብ አስረዱኝ?" አላቸው። ከዓለም መፈጠር እስከ ጌታችን የማዳን ሥራ አልፎም ስለ ፍርድ ቀን በጥዑም አንደበታቸው አስተማሩት። ቅዱስ እንድርያኖስ በቅጽበት ልቡ ወደ ክርስቶስ ፍቅር ሸፈተ።

በፍጥነት ተነስቶ የራሱን ስም ከሰማዕታቱ ሃያ አምስተኛ አድርጐ አጻፈ። ንጉሡ ይህንን ሲሰማ "አብደሃል?" ቢለው ቅዱሱ መልሶ "የለም! ዛሬ ገና ከእብደቴ ተመለስኩ።" በማለቱ ከሃያ አራቱ ቅዱሳን ጋር ታሠረ። ቅድስት ኤልያና (ሚስቱ) ነገሩን ስትሰማ ፈጽሞ ደስ አላት።

ወደ እስር ቤት ሒዳ "አይዞህ በርታ! ስለ ክርስቶስ የሞትክ ቀን ብቻ እኮራብሃለሁ።" ብላ እግራቸውን አጥባቸው ተመለሰች። በሚገደሉበት ቀንም ልሰናበታት ብሎ ቅዱስ እንድርያኖስ ቢመጣ ቅድስት ኤልያና ቤቷን ዘግታ ገሠጸችው። እርሷ ክዶ የመጣ መስሏት ነበር።

እርሱ ግን የሚስቱን የእምነት ጥንካሬ ተረዳ። ቅዱሱና ሃያ አራቱ ቅዱሳን ለቀናት ብዙ መከራን እየተቀበሉ ሰነበቱ። አካላቸውን እየቆራረጡ፣ ደማቸውን እያፈሰሱ፣ ሆዳቸውንም እየቀደዱ መከራን አጸኑባቸው። በመጨረሻው በዚህች ቀን ሲገደሉ ቅድስት ኤልያና "የእኔን ባል አስቀድሙት?" አለች። (የሌሎቹን አይቶ እንዳይደነግጥ ነው።)

እንዳለችውም የእርሱንና የባልንጀሮቹን ጭን ጭናቸውን እየሰበሩ ገድለዋቸዋል። ቅድስት ኤልያናንም መሣፍንቱ "ካላገባንሽ?" እያሉ ሲያስቸግሯት ተሰዳ ሒዳ ከሰማዕታቱ መቃብር ላይ አለቀሰች። ጌታም ጠርቷት እዚያው ዐረፈች።

<3 ታላቁ አባ ቢጻርዮን <3

ታላቁ ገዳማዊ ሰው የመጀመሪያ መነኮሳት ከሚባሉ አባቶች አንዱ ሲሆን ዓለምን ንቆ ከመነነ በኋላ ከአባ እንጦንስ ዘንድ መንኩሷል። ከእርሳቸው ዘንድ በረድእነት ለብዙ ዓመታት አገልግሏል። አገልግሎቱን በፈጸመ ጊዜም አስኬማን ተቀብሎ ወደ በርሃ ወጥቷል።

ምንም የራሱን ገዳም ባይመሠርትም በአራተኛው መቶ ክፍለ ዘመን የምናኔ ሕይወት እንዲስፋፋ ካደረጉ አበው እርሱ ዋነኛው ነው። በተጋድሎ ዘመኑም የሚታወቅባቸው ነገሮች አሉ።
ከእነርሱም ጥቂት እንጠቅሳለን።
አባ ቢጻርዮን፦
፩.ጾሙም ሆነ ጸሎቱ በአርባ ቀናት የተወሰነ ነበር። ጾምን ከጀመረ ያለ አርባ ቀን እህል አይቀምስም። ለጸሎት ከቆመም የሚቀመጠው ከአርባ ቀናት በኋላ ነው።
፪.ሁሌም በየበርሃው እየዞረ ያለቅሳል። "ምነው?" ሲሉት "ወገኖቼ አለቁብኝ፤ ደሃም ሆንኩ።" ይላቸው ነበር። እንዲህ የሚለው አጋንንት ብዙ ነፍሳትን እየነጠቁ ሲወስዱ ስለሚመለከት ነው።
፫.በየገዳማቱ እየለመነ ለነዳያን ያከፋፍል ነበር።
፬.ሐፍረቱን ከሚሸፍን ጨርቅ በቀር ምንም ልብስ አይለብስም ነበር።
፭.ውዳሴ ከንቱን አምርሮ ይጠላ ነበር።
፮.በባሕር ላይ ተራምዶ ሲሔድና እግሮቹ ሳይርሱ ሲቀሩ አበው ተመልክተዋል።
፯.መርዝነት ያለውን ውኃም ጣፋጭ አድርጐታል።

ቅዱሱ ድውያንን ፈውሶ፣ አጋንንትን ከአካባቢው አሳዶ፣ ብዙ ፍሬ አፍርቶ ገዳም ውስጥ በገባ በሃምሳ ሰባት ዓመቱ በመልካም ሽምግልና ዐርፏል።

ቸር አምላክ በክብረ ቅዱሳን ይከልለን። ከበረከታቸውም ያብዛልን።

ነሐሴ ፳፭ ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት
፩.ቅዱስ እንድርያኖስ ሰማዕት
፪.ሃያ አራቱ ሰማዕታት (ማኅበሩ)
፫.ቅድስት ኤልያና (ሚስቱ)
፬.ታላቁ አባ ቢጻርዮን ገዳማዊ
፭.ቅዱስ ኤልያኖስና እኅቱ አውዶክስያ (ሰማዕታት)

ወርኀዊ በዓላት
፩.ቅዱስ መርቆሬዎስ ሰማዕት
፪.ቅድስት ቴክላ ሐዋርያዊት
፫.ቅዱስ አበከረዙን ሰማዕት
፬.ቅዱስ ዱማድዮስ ሶርያዊ
፭.አቡነ አቢብ (አባ ቡላ)
፮.ቅዱስ አባ አቡፋና ጻድቅ

"ነገር ግን የሆነው ሁሉ በክርስቶስ ከራሱ ጋር ካስታረቀን የማስታረቅም አገልግሎት ከሰጠን ከእግዚአብሔር ነው። እግዚአብሔር በክርስቶስ ሆኖ ዓለሙን ከእርሱ ጋር ያስታርቅ ነበርና በደላቸውን አይቆጥርባቸውም ነበር። በእኛም የማስታረቅ ቃል አኖረ። እንግዲህ እግዚአብሔር በእኛ እንደሚማለድ ስለ ክርስቶስ መልእክተኞች ነን። ከእግዚአብሔር ጋር ታረቁ ብለን ስለ ክርስቶስ እንለምናለን።"
(፪ቆሮ ፭፥፲፰-፳)
ወስብሐት ለእግዚአብሔር

በቴሌግራምም እንገኛለን።
t.me/GedleKidusan