Get Mystery Box with random crypto!

እንኳን ለሠላሳ ሺህ ግብጻውያን ሰማዕታት ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ፤ አደረሰን። | ገድለ ቅዱሳን Gedle Kidusan Acts of Saints

እንኳን ለሠላሳ ሺህ ግብጻውያን ሰማዕታት ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ፤ አደረሰን።
†††በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
ወንድሞቻችሁ እና እህቶቻችሁ እንዲያነቡት ተጋሩት(share it)
በዲያቆን ዮርዳኖስ አበበ

<3 ሠለስቱ እልፍ ሰማዕታት <3

ዘመነ ሰማዕታት አርባ ሰባት ሚሊየን ክርስቲያኖችን በአርባ ዓመታት ከበላ በኋላ በ፫፻፭ (፫፻፲፪) ዓ.ም ቢጠናቀቅም ስለ ሃይማኖት መሞት ግን እስከ ምጽዓት ድረስ ይቀጥላል። ለእያንዳንዱ ክርስቲያን ከሚቀርቡ ፈተናዎች ሁሉ እጅግ ከባዱ ይሔው ሰማዕትነት ነውና ሊቀበለው ያለው (ያደለው) ይቀበለዋል።

ቤተ ክርስቲያን በባሕር ላይ ያለች መርከብ ናትና ዘወትር በፈተና ውስጥ መኖሯ የሚጠበቅ ነው። ዘመነ ሰማዕታትን ተከትሎ የመጣው የመናፍቃን ዘመን ሲሆን ለመቶ ሃምሳ ዓመታት ያህል መናፍቃን እንደ አሸን ፈልተዋል። በዚያው ልክ ከዋክብት ቅዱሳን ሊቃውንት ነበሩና በየጊዜው ጉባኤያትን እየሠሩ መናፍቃንን አሳፍረዋል። ምዕመናንንም አጽንተዋል።

በ፬፻፶፩ ዓ.ም የተፈጸመው ድርጊት ግን ዛሬም ድረስ ጠባሳው የሚለቅ አልሃነም። ንጉሡ መርቅያንና ጳጳሱ ልዮን የንስጥሮስን ትምህርት አለባብሰው ሊያስተምሩ ሲሞክሩ ግጭት በመፈጠሩ ቤተ ክርስቲያን ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ ሁለት ተከፈለች።

በጉባኤው የነበሩ ስድስት መቶ ሠላሳ ስድስት ጳጳሳት ስቃይና ሞትን ፈርተው በኑፋቄ መጽሐፍ ላይ በመፈረማቸው "መለካውያን" (ከእግዚአብሔር ይልቅ ለንጉሥ የሚታዘዙ) ተባሉ። ጉባኤውም "ጉባኤ ከለባት" (የውሾች ስብሰባ)፣ "ጉባኤ አብዳን" (የሰነፎች ጉባኤ) ተብሏል።

የወቅቱ የእስክንድርያ ፓትርያርክ ቅዱስ ዲዮስቆሮስ ግን "በኑፋቄው ላይ አልፈርምም።" ከማለቱ አልፎ መናፍቃኑን አወገዛቸው። በዚህ ምክንያት ጽሕሙን ነጭተው ጥርሱንም አርግፈው ወደ ጋግራ ደሴት ከሰባት ደቀ መዛሙርቱ ጋር አሳደዱት።
በዚያም ለሦስት ዓመታት ቆይቶ በ፬፻፶፬ ዓ.ም ዐረፈ።

እግዚአብሔር ፈርዶባቸው ንጉሡ መርቅያን እና ንግሥቲቱ ብርክልያ (ክፉ ሴት ናት።) ድንገት ሞቱ። ፈተናው ግን በዚህ አላበቃም። በዙፋኑ የተተካው ሌላኛው ጨካኝ ልዮን ነበር። መንፈሳዊውን አርበኛ አባ ዲዮስቆሮስን በሞት ያጡት የግብጽ ክርስቲያኖች ደቀ መዝሙሩን "አባ ጢሞቴዎስን እንሾማለን።" ቢሉ ንጉሡ ከለከለ።

የሚሾመው መለካዊ ነው ብሎ አብሩታርዮስ የሚባል መናፍቅ ጳጳስ በላያቸው ላይ ሾመባቸው። ይህንን መታገስ ለሕዝቡና ለካህናቱ ከባድ ነበር። ተኩላ እንኳን በበጐች ላይ በይፋ ተሹሞ ተደብቆም ቢሆን እየነጠቀ መብላት ልማዱ ነው። መናፍቁ ጳጳስ በተለያየ መንገድ ሕዝቡን ለመሳብ ሞክሮ ነበር።

ለምሳሌ አውጣኪን (የክርስቶስን ሰው መሆን ምትሐት የሚል 'የቱሳሔ' አስተማሪ መናፍቅ ነው።) አወገዘው። እነርሱ ግን ተረድተውታልና ቦታ አልሰጡትም። ምክንያቱም አውጣኪ ከቀድሞም የተወገዘ መናፍቅ ነውና። የሚገርመው ከሕዝቡ አንድስ እንኳ ከመናፍቁ ጳጳስ የሚባረክ አልነበረም። ሥጋውን ደሙንም ከእውነተኛ ካህናት በድብቅ ይቀበሉ ነበር።

አንድ ቀን ግን መናፍቁ ጳጳስ አብሩታርዮስ ተገድሎ ተገኘ። (መልአክ ቀሥፎት ነው የሚሉ አሉ። እስካሁን ድረስ የገዳዩ ማንነት አልታወቀም።) ግብጻውያን ክርስቲያኖች ግን የእርሱን ሞት ሲሰሙ ደጉን እረኛ አባ ጢሞቴዎስን ሾሙ። ችግሩ የመጣው ከዚህ በኋላ ነው።

የመናፍቁ ተከታዮች ለንጉሡ ልዮን "አንተን ንቀው የሾምከውን ገደሉ። ሌላ ጳጳስም ሾሙ።" ብለው መልዕክት ላኩለት። በዚህ የተበሳጨው ልዮን ኦርቶዶክሳውያንን ባገኛችሁበት ሁሉ ግደሉ የሚል አዋጅ አወጣ። ይህን አዋጅ ተከትሎ ሠላሳ ሺህ ሰዎች በእስክንድርያ ከተማ ተጨፈጨፉ።

ገዳዮቹ ወንድ፣ ሴት፤ ሕፃን፣ ሽማግሌ ሳይመርጡ የክርስቲያኖችን ደም አፈሰሱ። ለሦስት ቀናትም ግድያው ቀጥሎ እንደ ነበር ይነገራል።
ልበ አምላክ ቅዱስ ዳዊት "ወኀጥኡ ዘይቀብሮሙ" እንዳለ ቀባሪም አጡ።

ገዳዮቹ ቀጥለውም አባ ጢሞቴዎስን አስረው አጋዙት። ለአሥር ዓመታትም አሰቃዩት። ከእነዚህ ዓመታት በኋላ ግን ንጉሡ ተጸጽቶ አባ ጢሞቴዎስን ወደ መንበሩ መልሶታል። ወገኖቻችን የግብጽ ክርስቲያኖች እንኳን ያኔ ዛሬም በጽናታቸው አብነት ልናርጋቸው የሚገቡ ናቸው።

አምላከ ሰማዕታት በቸርነቱ ይጠብቀን። ከበረከታቸውም ያድለን።

ነሐሴ ፳፫ ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት
፩.ሠላሳ ሺህ የእስክንድርያ (ግብጽ) ሰማዕታት
፪.ቅዱስ ድምያኖስ ሰማዕት

ወርኀዊ በዓላት
፩.ልበ አምላክ ቅዱስ ዳዊት
፪.ቅዱስ ጊዮርጊስ ሊቀ ሰማዕታት
፫.ነቢየ ጽድቅ ቅዱስ ሰሎሞን (ንጉሠ እስራኤል)
፬.አባ ጢሞቴዎስ ገዳማዊ
፭.ቅዱስ ዳንኤል ነቢይ
፮.አባ ሳሙኤል
፯.አባ ስምዖን
፰.አባ ገብርኤል

"በጐንም ለማድረግ ብትቀኑ የሚያስጨንቃችሁ ማን ነው? ነገር ግን ስለ ጽድቅ እንኳ መከራን ብትቀበሉ ብጹዓን ናችሁ። ማስፈራራታቸውንም አትፍሩ አትናወጡም። ዳሩ ግን ጌታን እርሱም ክርስቶስን በልባችሁ ቀድሱት። በእናንተ ስላለ ተስፋ ምክንያትን ለሚጠይቋችሁ ሁሉ መልስ ለመስጠት ዘወትር የተዘጋጃችሁ ሁኑ። ነገር ግን በየውሃነትና በፍርሃት ይሁን።"
(፩ጴጥ ፫፥፲፫-፲፮)
ወስብሐት ለእግዚአብሔር